CURRENT

በአርሲ ነጌሌ ወረዳ ሁከት በመፍጠር በሰውና ንብረት ላይ ጉዳት ያደረሱ የጥፋት ሀይል አባላትን ህዝቡ እያጋለጠ ነው

By Admin

October 13, 2016

በኦሮሚያ ክልል ምእራብ አርሲ ዞን አርሲ ነጌሌ ወረዳ ሁከት በመፍጠር በሰውና ንብረት ላይ ጉዳት ያደረሱ የጥፋት ሃይል አባላትን ህዝቡ እያጋለጠ ይገኛል።

በአሁኑ ወቅትም አካባቢው ወደ መረጋጋትና ሰላም የተመለሰ መሆኑን ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በስፍራው ተዘዋውሮ ተመልክቷል።

ምእራብ አርሲ ዞን አርሲ ነጌሌ ወረዳ በሰሞንኛ ሁከት ተጠቂ ከሆኑ አካባቢዎች አንዷ ነች።

በወረዳዋ ሁከት ፈጣሪ ሀይሎች ከፍተኛ የሆነ ውድመት ያደረሱ ሲሆን፥ ከነዚህ ውስጥ ሶስት ወረዳዎችን ተጠቃሚ የሚያደርገው የውሃ ፕሮጀክት ይገኝበታል።

የውሃ ፕሮጀክቱ እስክ 300 ሚሊየን ብር በሚጠጋ ወጪ የተገነባ ሲሆን፥ በቃጠሎው ሊዘረጉ የተዘጋጁ ቱቦዎች፣ የፕሮጄክቱ ማስፈጸሚያ ቢሮዎችና ተሽከርካሪዎች ወድመዋል።

አካባቢው ከፍተኛ የሆነ የንጹህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት ጥያቄ ሲቀርብ የበረ ነው፤ ነገር ግን እነዚህ የጥፋት ሀይሎች ለህብረተሰቡ የተሰራውን የውሃ ፕሮጀክት እንዳልነበር አድርገው አውድመውታል።

ቁጥራቸው በርከት ያሉ የህብዝ ማመላለሻ አውቶብሶች፣ የንግድ ተሽከርካሪዎች እና የግለሰብ መኖሪያ ቤቶች ሁከት ፈጣሪዎቹ ባደረሱት ጥቃት ሙሉ በሙሉ ተቃጥለዋል።

እንዲሁም ከአርሲ ነገሌ ከተማ ውጭ በሚገኙ ሌሎች ቀበሌዎች ላይ የደረሰው ጥቃት ተጠቃሽ ነው።

በአርሲ ነገሌ ወረዳ ውስጥ ከሚገኙ 39 ቀበሌዎች ውስጥ በሁከት ፈጣሪ ሀይሎች 20 ቀበሌዎች ሙሉ በሙሉ ከነሰነዳቸው የወደሙ ሲሆን፥ በአሁኑ ጊዜ ቀበሌዎቹ ለህብረተሰቡ የሚሰጡትን አገልግሎት ለማቆም ተገደዋል።

በአካባቢው ለህብረተሰቡ አገልግሎት የሚሰጡ ሁለት የጤና ኬላዎች በሁከት ፈጣሪ ሀይሎች ሙሉ በሙሉ ወድመዋል።

ከዚህ በተጨማሪም 17 የማዳበሪያ መጋዝኖች፣ 17 የሸማቾች ማህበር መጋዝኖች እና ሌሎች የመንግስት ተቋማት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደርሷል።

በአሁኑ ጊዜ በሁከቱ የተሳተፉ ሀይሎች በህብረተሰቡ እየተያዙ መሆኑም የወረዳው አስተዳዳሪዎች ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ተናግረዋል።

በቀጣይም እንዚህ አካላት ላይ አስፈላጉው ማጣራት ተደርጎ ለህግ እንዲቀርቡ ይደረጋል ሲሉም ነግረውናል።

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከመታወጁ በኋላ በአሁኑ ጊዜ በአካባቢው አንጻራዊ እና የተረጋጋ ሰላምዋን እያገኘት መምጣቷን የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ባልደረባ በአካባቢው ተዘዋውሮ ተመልክቷል።

በስፍራው ወደ ሀዋሳ፣ አዲስ አበባ እና ሌሎች አካባቢዎች የሚንቀሳቀሰሱ ተሽከርካሪዎችም ወደ መደበኛ እንቅስቃሴዎች ተመልሰዋል።