CURRENT

በኦሮሚያ አንዳንድ አከባቢዎች የነበረው ሁከት በመንግስትና በህብረተሰቡ ትብብር በቁጥጥር ስር መዋሉን የክልሉ መንግስት ገለፀ

By Admin

October 11, 2016

በኦሮሚያ አንዳንድ አካባቢዎች ተከሰቶ የነበረው ሁከት በመንግስትና በህብረተሰቡ ትብብር በቁጥጥር ስር መዋሉን የክልሉ መንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ገልፀ።

ቢሮው ዛሬ ረፋድ ላይ በሰጠው መግለጫ፥ ሁከቱ ተከስቶ በነበረባቸው አካባቢዎች ነዋሪው ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ወደ መደበኛ እና ሰላማዊ እንቅስቃሴ መመለሱን ይፋ አድርጓል።

የሁከት እና ብጥብጡ መሪ የነበሩ ግልሰቦችም በህብረሰተቡ ጥቆማ በቁጥጥር ስር እየዋሉ መሆኑንም ቢሮው በመግለጫው አመላክቷል።

የኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ ፍቃዱ ተሰማ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በሰጡት መግለጫ፥ ላለፉት ሶስት እና አራት ቀናት በክልሉ ጥቂት ወረዳዎች በተፈጠረው ሁከት እና ግርግር በሰው ህይወት እና ንበረት ላይ ጉዳት መድረሱን ገልፀዋል።

የጥፋት ሀይሎቹ ኢላማ የነበሩትም የመጠጥ ውሀ ፕሮጀክቶች፣ የጤና ተቋማት፣ የአርሶ አደር ማሰልጠኛዎች፣ ለበርካታ ዜጎች ከፍተኛ የስራ እድል የፈጠሩ ግዙፍ ኢንደስትሪዎች እና የግለሰብ ንብረቶች እንደነበሩም አቶ ፍቃዱ በመግለጫው አብራርተዋል።

ምስራቅ ሸዋ፣ ምእራብ አርሲ፣ ምስራቅ ጉጂና አርሲ እንዲሁም ፊንፊኔ ልዩ ዞን ሰበታ ከተማ ከፍተኛ ሁከትና ብጥብጥ ተከስቶባቸው የነበሩ አከባቢዎች መሆናቸውም ተጠቅሰዋል።

በሁከቱ በምስራቅ ሸዋ በ501 ሄክታር መሬት ላይ የነበረ እና የአካባቢው አርሶ አደሮች ንብረት የሆነ የሸንኮራ ምርት ሙሉ ሙሉ በእሳት መጋየቱንና በፊንፊኔ ዙርያ ሰበታ ከተማ ከውጪ በመጡ አልሚዎች የተቋቋሙ ፋብሪካዎች በእሳት መወደማቸውን ነው አቶ ፈቃዱ የተናገሩት።

የጥፋት ሀይሎቹ ውድመቱን ያደረሱት የሀገሪቱን ሰላም እና መረጋጋት ከማይሹና በውጭ ከሚኖሩ ሀይሎች የሚሰጣቸውን ተልእኮ በመቀበል መሆኑም በቢሮው ሃላፊ ተጠቁሟል።

አሁን በክልሉ ያለውን የፀጥታ ሁኔታ በዳሰሱበት መግለጫቸው፥ ሁከት ተከስቶባቸው የነበሩት አካባቢዎች ወደ ሰላም እና መረጋጋት መመለሳቸውን አመላክተዋል።

ሁከት ተከስቶባቸው የነበሩ ስፍራዎችን ወደ ቀደመ ሰላማቸው በመመለሱ ሂደት ህብረሰተቡ፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና የፀጥታ ህይሉ ከፍተኛ ትብብር መጫወታቸውን ተጠቅሷል።

በአሁኑ ወቅትም ሁከት ተከስቶባቸው በነበሩ አካባቢዎች የሚኖረው ህብረተሰብ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ወደ ዘወትር የተረጋጋ እንቅስቃሴ መመለሱን አቶ ፈቃዱ ይፋ አድርገዋል።

በቡራዩና በሻሸመኔ አንዳንድ አካባቢዎች ላይ በእነዚሁ ሀይሎች እኩይ ድርጊት ለበርካታ ዓመታት ከኖሩበት አካባቢ እንዲወጡ የተደረጉ ዜጎች በአካባቢው ህብረተሰብ እገዛና በመንግስት ድጋፍ ወደ መኖሪያቸው መመለሳቸውንም ነው አቶ ፈቃዱ የተናገሩት።

ድርጊቱ የኦሮሞን ህዝብ አይወክልም ሲሉም ሀላፊው ገልጸዋል።

አቶ ፍቃዱ ህብረተሰቡ አሁን ያለውን ሰላሙን በመጠበቅ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባው አሳስበዋል።

አሁን ላይ የጥፋት ሀይሎቹ በሰውና በንብረት ላይ የደረሱት ውድመቶችንም ተገቢውን ማጣራት በማካሄድ የክልሉ መንግስት በቅርቡ ለህብረተሰቡ ይፋ እንደሚያደረግም ሀላፊው ተናግረዋል።