CURRENT

አቶ ልደቱ ከሪፖርተር ጋዜጣ ጋር ያደረጉት ውይይት

By Admin

October 19, 2016

አቶ ልደቱ አያሌው፣ የኢዴፓ መሥራችና የቀድሞ ሊቀመንበር

አቶ ልደቱ አያሌው የኢትዮጵያዊያን ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢዴፓ) መሥራችና የቀድሞ ሊቀመንበር ናቸው፡፡ አቶ ልደቱ በ1997 ዓ.ም. ጠቅላላ ምርጫ ለገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ ዋነኛ ተቀናቃኝ የነበረው የቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ (ቅንጅት) ከነበሩት ተፅዕኖ ፈጣሪ መሪዎች አንዱም ነበሩ፡፡ ቅንጅት እንደ ጅማሮው መቀጠል ተስኖት በመሽመድመዱ ከተነሱት ውዝግቦች አንዱ በአቶ ልደቱ ዙሪያ ያነጣጠረ ነበር፡፡ አቶ ልደቱ ስለ ቅድመ ቅንጅት፣ ስለ ቅንጅትና ድኅረ ቅንጅት የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሕይወት ሦስት መጻሕፍትን በማሳተም ትንተና አቅርበዋል፣ ራሳቸውንም ተከላክለዋል፡፡ ከኢዴፓ አመራር ውጪ ቢሆኑም በማዕከላዊ ኮሚቴ አባልነት የሚጠበቅባቸውን ሚና እየተጫወቱ እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ በግላቸው በወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታዎች ላይ ሐሳባቸውን ለማካፈል ሁሌም ፈቃደኛ ከሆኑ እጅግ በጣት ከሚቆጠሩ ፖለቲከኞች በቅድሚያ ተጠቃሽ የሆኑት አቶ ልደቱ አያሌውን ሰለሞን ጐሹ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ አገሪቱ ውስጥ እየተከሰቱ ባሉ ተቃውሞዎችና ተዛማጅ ጉዳዮች ላይ አነጋግሯቸዋል፡፡

ሪፖርተር ፡- በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በተለይ በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች የተነሱት ተቃውሞዎች መነሻቸው ምንድነው?

አቶ ልደቱ፡- በእኔ እምነት ተቃውሞዎቹ አራት መነሻ ምክንያቶች አሉዋቸው፡፡ አንደኛው ምክንያት በአገሪቱ የተዘረጋው የፖለቲካ ሥርዓት በልዩነት ላይ ያተኮረ ከመሆኑ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ አካባቢያዊ ልዩነቶች እንዲጎለብቱ ተደርጓል፡፡ ልዩነት መከበር አለበት፡፡ ነገር ግን አንድ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ማኅበረሰብ ለመፍጠር የጋራ የሆኑ ጉዳዮች ተጠናክረው መውጣት አለባቸው፡፡ በዚህ ረገድ በአጠቃላይ ሥርዓቱ ከፍተኛ ጉድለት አለበት፡፡ ይኼ ከአንድነት ይልቅ ልዩነት ላይ ማተኮር በሕዝብ ዘንድ መቃቃር ሲፈጥር፣ አንድነትን ሲያላላና ግጭት ሲያጭር በተደጋጋሚ ታይቷል፡፡ መንግሥት ግን የፌዴራል አደረጃጀቱ ይበልጥ አንድነት የሚያመጣ ነው፣ ሕዝቡም ተቀብሎታል፣ ችግሮችንም እየፈታ ነው በማለት በተደጋጋሚ ይናገር ነበር፡፡ ይህ እንዳልሆነ ግን አሁን የታየ ይመስለኛል፡፡ ከአሁን በፊትም ሲታይ ነው የነበረው፡፡ አሁን ግን በባሰ ሁኔታ ብዙ አካባቢዎችን የሚያካልሉ ችግሮች እየተከሰቱ ነው፡፡ ይኼ አገር በብዙ ታሪካዊ ሒደቶች ውስጥ አልፎ ነው እዚህ የደረሰው፡፡ በውስጡ ብዙ ልዩነቶች አሉ፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ የጋራ ጉዳዮች አሉ፡፡ አሉ የምንላቸውን ችግሮች አርሞ፣ ጠንካራ ጎኖችን ይበልጥ አጠናክሮ የሚያስቀጥል ሥርዓት ያስፈልጋል፡፡

በአንድ በኩል በአገሪቱ ውስጥ በርካታ ልዩነቶች ስላሉ ልዩነቶች የሚስተናገዱበትን መንገድ መፍጥር ተገቢ ነው፡፡ ከሕገ መንግሥቱ ጀምሮ የፌዴራል አደረጃጀቱ በዋናነት ልዩነትን ለማስተናገድ ያለመ ነው፡፡ በአንድ አገር ውስጥ ልዩነት ብቻ ሳይሆን አንድነትም እንዲጠናከር ካልተደረገ ችግር መፈጠሩ አይቀርም፡፡ ሥርዓቱ ሁለቱን ነገሮች አጣጥሞ በማስኬድ ረገድ ከፍተኛ ጉድለት አለበት፡፡ ከፍተኛ ሚዛን የደፋ ትኩረት ያገኘው የልዩነት ጉዳይ ነው፡፡ የአንድነት ጉዳይ ላለፉት 25 ዓመታት ተረስቶ ነው የቆየው፡፡ እንዲያውም ስለ አንድነት የሚያቀነቅኑ ኃይሎችና ግለሰቦች እንደ ጥፋትና ፀረ ሰላም ኃይል፣ ልዩነትን በፍፁም እንደማይፈልጉ ተደርጎ ነው ሲወቀሱ የነበረው፡፡ ይኼ ጉድለት በሒደት እንዲህ ዓይነት ችግር ሊፈጥር እንደሚችል ቀድሞውንም ግልጽ ነው፡፡ ይኼ ሁኔታ እንዲታረም የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ከፍተኛ ጥረት ሲያደርጉ ነበር፡፡ መንግሥት ግን የእኔ አመለካከት ብቻ ነው ትክክል፣ እናንተ የምትሉት ሁሉ ትክክል አይደለም ብሎ የውስጥ አስተሳሰባቸውን ሁሉ ጥያቄ ውስጥ እያስገባ እያወገዘ ነው የቀጠለው፡፡

ሁለተኛው መነሻ ምክንያት በአገሪቱ ሕገ መንግሥት ውስጥ ያሉ የሰብዓዊ መብትና የዴሞክራሲ ጉዳዮች በተግባር ካለመዋላቸው ጋር የተያያዘ ነው፡፡ የታይታ ነው የሆነው፡፡ በወረቀት ላይ ስለሰብዓዊ መብትና ዴሞክራሲ እየተወራ መሬት ላይ ግን በሕዝብ የዕለት ተዕለት ሕይወት ውስጥ እነዚህ ነገሮች አለመኖራቸው አንዱ ሌላው ምክንያት ነው ብዬ አስባለሁ፡፡

ሦስተኛውና ዋናው መነሻ ምክንያት ዜጎች ሐሳባቸውን በነፃነት የሚገልጹበት መድረክ ካለመኖሩ ጋር የተያያዘው ነው፡፡ በየትኛውም አገርና ሁኔታ ሰዎች ሐሳባቸውን፣ ተቃውሟቸውንና ቅሬታቸውን የሚገልጹበት ዴሞክራሲያዊ መንገድ ካጡ ወደ አመፅ፣ አብዮትና ግጭት መሄዳቸው የማይቀር ነገር ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰዎች በሰላማዊ መንገድ፣ በሕጋዊ መንገድ ሐሳባቸውን የሚያቀርቡበት መንገድ እያጡ ነው የመጡት፡፡ በዚህም ፅንፈኛ የሆኑ የፖለቲካ አስተሳሰቦች እየተጠናከሩ ነው፡፡ የፖለቲካ ምኅዳሩ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጠበበ ነው፡፡ አገሪቱ ከቀበሌ ምክር ቤት ጀምሮ እስከ ፓርላማ ድረስ በአንድ ፓርቲ ብቸኛ የበላይነት ቁጥጥር ሥር ውላለች፡፡ ኅብረተሰቡ ብሶቱንና ተቃዋሞውን የሚገልጽበት መድረክ ሙሉ በሙሉ አጥቷል፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሰላማዊ ሠልፍ፣ ስብሰባና የተለያዩ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎች ለማድረግ ሲሞክሩ የተለያዩ ሰበባ ሰበቦች እየተፈጠሩላቸው እንዳያደርጉ ተከልክለዋል፡፡

አራተኛው መነሻ ምክንያት በአገሪቱ ከፍተኛ የሆኑ ከመልካም አስተዳደር ጋር የተያያዙ በደሎች የሚፈጸሙ ከመሆናቸው ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ካድሬዎች ጉልበተኛ ሆነዋል፣ ኅብረተሰቡ ደግሞ አቅመ ቢስ ሆኗል፡፡ ካድሬው የፈለገውን አድርጎ ተጠያቂነት የለበትም፡፡ በየአካባቢው ሕዝቡ በዕለት ተዕለት ኑሮው ከፍተኛ የሆነ ጫናና ብሶት አለበት፡፡

ሪፖርተር ፡- መንግሥት ለተቃውሞዎቹ እየሰጠ ያለውን ምላሽና ማብራሪያ እንዴት አዩት?

አቶ ልደቱ፡- በመንግሥት መገናኛ ብዙኃን በተለይም በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) የሚቀርቡ መረጃዎችን እንዳየሁት መንግሥት በተለመደው የፕሮፓጋንዳ መንገድ እየሄደ ነው፡፡ ነገር ግን ሰሞኑን በአማራ ቲቪ ችግሮች አሉ፣ ችግሮችን ማስተናገድ አለብን፣ ችግሮቹ በወቅቱ ስላልተፈቱ የተፈጠረው ክፍተት ተቃውሞ አስነስቷል በማለት ሲያቀርቡ አይቻለሁ፡፡ ይኼ ለዘብ ያለ አቀራረብ ነው፡፡ ሌሎች የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ግን ችግር የፈጠሩ ኃይሎችን በቁጥጥር ሥር እናውላለን፣ ለፍርድ እናቀርባለን፣ ዕርምጃ እንወስዳለን የሚሉትን ጨምሮ በአብዛኛው የማስፈራሪያ ኃይለ ቃል ያለበት መልዕክት ነው የሚያስተላልፉት፡፡ ይኼ የሚያዋጣ አይመስለኝም፡፡ ግጭቶች ባልተቋረጠ ሁኔታ እየተከሰቱ፣ ሰዎች እየሞቱ፣ ወደማንጠብቀው አቅጣጫ ከምንሄድ መንግሥት ቆም ብሎ ማሰብና መሠረታዊ የሆነው ችግር ምንድነው ብሎ መሠረታዊ የሆነ መፍትሔ ለማምጣት ጥረት ማድረግ አለበት፡፡ አለበለዚያ ግን ዝም ብሎ በምኞት ሰላም እንዲኖር በመፈለግና ዋናው ነገር ሰላም ነው እያሉ በመፎከር ሰላም ሊገኝ አይችልም፡፡ ይህች አገር በምንም ዓይነት ሁኔታ ከዚህ በኋላ ብጥብጥ ወይም የእርስ በርስ ጦርነት ማስተናገድ የምትችል አይደለችም፡፡ በዚያ ደረጃ ችግር ከተፈጠረ አጠቃላይ ህልውናችንን የምናጣበት አደጋ ሊመጣ ይችላል፡፡ የእንደዚህ ዓይነት እንቅስቃሴ ችግሩ የመንግሥት ለውጥ ብቻ አምጥቶ ሊያበቃ መቻሉ ነው፡፡ በዚህም መንግሥት የለሽ ሊያደርገን ይችላል፡፡

ሌላው ሊፈተሽ የሚገባው የመንግሥት ችግር በልማት ለሁሉም ችግር መፍትሔ አመጣለሁ ማለቱ ነው፡፡ ኅብረተሰቡ ልማት መፈለጉ ምንም ጥያቄ የለውም፡፡ መንግሥት ልማት ከሠራንና የምንሠራውን ልማት ለሕዝቡ በተጨባጭ ካሳየነው ወደ አመፅና ተቃውሞ በጭራሽ አይገባም ብሎ ያስባል፡፡ ነገር ግን ኅብረተሰቡ ልማት ቢፈልግም መብቱ ካልተከበረ፣ የሰብዓዊ መብትና የዴሞክራሲ ጥያቄዎች በአግባቡ ካልተመለሱ ወደ መጥፎ ሁኔታ መግባቱ አይቀርም፡፡ መንገድ እየተሠራ፣ ሕንፃ እየተገነባ፣ በርካታ የልማት ሥራዎች እየተሠሩለትም ግጭቶች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ሁሉም የኅብረተሰቡ ጥያቄዎች በልማት ብቻ የሚመለሱ አይደሉም፡፡ ሰብዓዊ መብትና ዴሞክራሲ ካልተከበሩ ልማቱም ዞሮ ዞሮ ችግር ውስጥ የሚገባበት ዕድል አለ፡፡ ልማቱ ብቻ ሳይሆን ችግሩ ሰፋ ካለ የአገር ህልውናም ጥያቄ ውስጥ ሊገባ ይችላል፡፡ ከሰሞኑ የምናየው ነገር በጣም አስፈሪና ጤናማ ያልሆነ ነው፡፡ መንግሥት ከተለመደው አስተሳሰብ ወጣ ብሎ ይኼን ነገር ከምንጩ ማድረቅ የሚቻለው እንዴት ነው ማለት አለበት፡፡ ስህተት አለብን ወይ? እስካሁን ይህን ችግር መፍታት ያልቻልነው ለምንድን ነው? በማለት ጉዳዩ ከሚመለከታቸው የኅብረተሰቡ ክፍሎች ጋር ሰፊ የሆነ፣ ሀቀኛ የሆነ የውይይት መድረክ ከፍቶ መፍትሔ ለማግኘት መጣር አለበት እንጂ ችግሩን እያቃለሉ፣ የጥቂት ግለሰቦችና የፖለቲካ ኃይሎች ጥያቄ ብቻ እንደሆነ አድርጎ እያቀረቡ፣ ችግሩ ጊዜያዊ ነው እያሉ ችግሩን ከመልካም አስተዳደር ጋር ብቻ የተያያዘ እንደሆነ አስመስሎ በቁንፅል እያቀረቡ ዘላቂ መፍትሔ ማግኘት አይቻልም፡፡

ስለዚህ ከሕገ መንግሥቱ ጀምሮ የፌዴራል አደረጃጀቱንና በአጠቃላይ አገሪቱ ውስጥ ያሉ ፖሊሲዎችን ከመሠረታቸው መዳሰስ ያስፈልጋል፡፡ የመንግሥት የፕሮፓጋንዳ ሥልት ጠቃሚነትም መፈተሽ አለበት፡፡ ሃያ አምስት ዓመታት ሙሉ አንድ ዓይነት ፕሮፓጋንዳ ነው ስንሰማ የኖርነው፡፡ በአሁኑ ወቅት መንግሥት እውነት እንኳን ቢናገር የማይታመንበት ደረጃ እየደረሰ ነው፡፡ ምክንያቱም በጣም በሚያሳዝን ሁኔታ ኅብረተሰቡ በመሬት ላይ የሚያያቸው፣ በቅርበት የሚያውቃቸው ነገሮች ሁሉ ተንሻፈውና ተጣመው፣ አንዳንድ ጊዜም ተለውጠውና ተክደው ነው በመገናኛ ብዙኃን የሚቀርቡት፡፡ እየተፈጠረ ያለው ነገር በጣም አሥጊ በመሆኑ መንግሥትን ጨምሮ ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍሎችና የፖለቲካ ኃይሎች አስቸኳይ መፍትሔ መሻት አለባቸው፡፡ ሁላችንም የችግሩ አካል ነን፡፡ መፍትሔውም የሚገኘው ከሁላችንም ነው፡፡ አንዱ አካል ችግር ፈጣሪ፣ ሌላው አካል ደግሞ መፍትሔ ፈላጊ መሆን የለበትም፡፡ በአመፅ የሚገለጽ እንቅስቃሴ ምን መፍትሔ ያመጣል የሚለውም መታየት አለበት፡፡ አሁን እንቅስቃሴው በተደራጀና ኃላፊነት መውሰድ በሚችል ኃይል እየተመራ አይደለም፡፡ በአብዛኛው በፌስቡክ ነው እየተመራ ያለው፡፡ ይህ ዓይነት የሕዝብ እንቅስቃሴ ግቡና መድረሻው ምን ሊሆን እንደሚችል አስቀድሞ ማወቅ አይቻልም፡፡ ይኼንን ኅብረተሰቡ ሊያጤን ይገባዋል፡፡ በቀዳሚነት ኢትዮጵያ ውስጥ ኃላፊነት የሚሰማቸው፣ የሕዝቡንና የአገሪቱን ጉዳይ በሚመለከት ኃላፊነት ሊወስዱ የሚችሉ የፖለቲካ ኃይሎች መጠናከር አለባቸው፡፡ አለበለዚያ የለየለት ብጥብጥ ተፈጥሮ ይህች አገር ወዳልተፈለገ አቅጣጫ ልትሄድ ትችላለች፡፡

ሪፖርተር ፡- በኢትዮጵያ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቱን በአሉታዊም ሆነ በአዎንታዊ መልኩ የሚወስኑ ጉዳዮች ሲታዩ፣ ብሔርን መሠረት ያደረጉት አሥጊ ደረጃ ላይ ደርሰዋል ማለት ይቻላል?

አቶ ልደቱ፡- የሕዝቡ ግንኙነት በብሔር ብቻ ሊወሰን አይችልም፡፡ በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ ብዙ ሌሎች ነገሮች አሉ፡፡ እነዚህ ከጥንት ጀምሮ የነበሩ ናቸው፡፡ ነገር ግን ላለፉት 25 ዓመታት የፖለቲካ ሥርዓቱ በተለይም በመገናኛ ብዙኃን ከሕዝብ ጋር ባለው ግንኙነት ሲሰበክ የነበረው ፕሮፓጋንዳ ሰዎች ግንኙነታቸውን በአብዛኛው በብሔር መነፅር እንዲያዩ የሚያደርግ ነው፡፡ አንድነቱ በኃይል እንደመጣ፣ ይህች አገር የብሔረሰቦች እስር ቤት እንደነበረች፣ ዋናው የፖለቲካ አጀንዳ የማንነት ፖለቲካ፣ የብሔሮች ነፃነትና እኩልነት እንደሆነ ነው የሚነገረው፡፡ ሰዎች ከሌላው ሰው ስላላቸው ልዩነት ነው ሲነገር የነበረው፡፡ ስለዚህ ይህ የ25 ዓመታት ፕሮፓጋንዳ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቱ ባየነው መልኩ እንዲባባስ አድርጎታል ብዬ አስባለሁ፡፡ አሁን የብሔር ማንነት ገዥ እየሆነ ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ግንኙነታቸውን ከብሔር አንፃር ማየታቸው አሁን ጎልቷል፡፡ ነገር ግን ሕዝቡ በሌሎች ጉዳዮችም ይገናኛል፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ለረጅም ጊዜ አብሮ የኖረ ሕዝብ ነው፡፡ ሕዝቡ ከቦታ ቦታ ሲንቀሳቀስ በንግድም፣ በጦርነትም፣ በሥራም ሲገናኝ የነበረና እርስ በርስም ሲጋባና ሲዋለድ የኖረ ነው፡፡ በሃይማኖትም፣ በባህልም የሚያስተሳስሩት ነገሮች አሉ፡፡ እነዚህ ተሟጠው ተበጥሰዋል ማለት አይቻልም፡፡ ነገር ግን ይኼ እየቀነሰ ሰዎች በዋናነት ማንነትን ከብሔር ጋር አያይዘው የማየት አስተሳሰባቸው የበለጠ እየጠነከረና እየጎላ መጥቷል፡፡

ሪፖርተር ፡- በአማራ ክልል የተነሳው ተቃውሞ መነሻ ከወልቃይት የማንነት ጥያቄ ጋር ሲያያዝ ይስተዋላል፡፡ በወልቃይት ጥያቄ ላይ የእርስዎ የግል አቋም ምንድነው?

አቶ ልደቱ፡- የተቃውሞው ዋና ምክንያት የወልቃይት ጥያቄ ነው ብዬ አላምንም፡፡ እርግጥ መነሻ ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡ ኢሕአዴግ ሥልጣን ከያዘ ጀምሮ ወልቃይት አካባቢ ጥያቄው ነበር፡፡ አንዳንድ ሰዎች የጎንደር መሬት ያለአግባብ በትግራይ ተወስዷል የሚል አስተሳሰብ ነበራቸው፡፡ ይኼ በተደራጀም፣ ባልተደራጀም መልኩ ይቀርብ ነበር፡፡ አሁን ለየት የሚያደርገው ኮሚቴ ተቋቁሞ ጥያቄ መቅረቡ ነው፡፡ በኮሚቴው ላይ በደረሰው ችግር ምክንያት ነው ነገሩ በዚህ ደረጃ ያደገው፡፡ የተቃውሞው ዋነኛ መነሻ ሥርዓቱ አፋኝ በመሆኑና ከዚህ አምባገነናዊ ሥርዓት ለመውጣት የመፈለግ ባህሪ ነው፡፡ ስለዚህ በአማራ ክልል ተቃውሞ ለማስነሳት የወልቃይት የማንነት ጥያቄ ገዥ ምክንያት ነው ብዬ አላምንም፡፡ በእኔ እምነት የወልቃይት የማንነት ጥያቄ እንዴት እንደሚፈታ የአገሪቱ ሕገ መንግሥት አስቀምጧል፡፡ በዚህ ጥያቄ የተነሳ ሕዝብ ለብጥብጥ መዳረግና ሰዎች መሞት አለባቸው ብዬ አላምንም፡፡ በአጠቃላይ የወልቃይት የማንነት ጥያቄን በተለያዩ መንገዶች መፍታት ይቻላል፡፡ ወልቃይት የማን ነው የሚለውን መፍረድ ያለበት አሠራሩ ነው፡፡ የማንነት ጥያቄው ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ቀርቦ የሕዝብ ጥያቄ መሆኑን ምክር ቤቱ ካረጋገጠ፣ ምርጫ ቦርድ ሪፈረንደም እንዲያካሂድ ይደረግና በሪፈረንደሙ ሕዝቡ የወሰነው ነገር ተግባራዊ ይሆናል፡፡ ስለዚህ አንዱ መንገድ ሪፈረንደም አካሂዶ የሕዝቡን ውሳኔ መቀበል ነው፡፡ ነገር ግን ሪፈንደም ለማካሄድ አስቸጋሪ ሁኔታዎች አሉ ከተባለ ደግሞ ሌሎች አማራጮችን ግምት ውስጥ ማስገባት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ ከወልቃይት ሕዝብ መሀል የተወሰነ ወደ ጎንደር፣ የተወሰነ ወደ ትግራይ መሄድ የሚፈልግ ከሆነ ይህን አማራጭ ማየት ነው፡፡ ይህም ካልሆነ ራሱን ችሎ ወይ በወረዳ አልያም በዞን ደረጃ ልዩ አስተዳደር ሆኖ መቋቋም የሚችል ከሆነና ለአካባቢው ሰላም አስተዋጽኦ ማድረግ የሚችል ከሆነ ይህንም ማየት ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ እነዚህን አማራጮች ግምት ውስጥ አስገብቶ ችግሩን መፍታት ይቻላል፡፡ ነገር ግን ይኼም ችግር ቢፈታ በአማራ ክልል ያለው ችግር የሚፈታ አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም የችግሩ ዋና ምንጭ በሕዝብና በሥርዓቱ መካከል እየተፈጠረ የመጣው መራራቅ ነው፡፡

ሪፖርተር ፡- ከላይ እንደገለጹት በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች የተነሳው ተቃውሞ መሪ የለውም፡፡ በዚህ ሁኔታ የጥያቄዎቹ መጨረሻ ምን ይሆናል? በቅርቡ በኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኦዴግ) እና በግንቦት ሰባት መካከል የተፈረመው የመግባቢያ ስምምነት ይህን ክፍተት ለመሙላት ያለመ ነው መባሉንስ እንዴት አዩት?

አቶ ልደቱ፡- ውጭ አገር ያሉ የፖለቲካ ድርጅቶች መስማማት፣ መፈራረምና አብረው መሥራት መብታቸው ነው፡፡ እሱ ላይ ችግር የለብኝም፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያ ውስጥ አሁን የተፈጠረውን ክፍተት ውጭ አገር ያሉ ፓርቲዎች መጥተው ይሞሉታል ብዬ አላስብም፡፡ ይኼ ክፍተት መሞላት ያለበት ኢትዮጵያ ውስጥ ባሉ ፓርቲዎች ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የሕዝቡ ትግል ትክክለኛ አቅጣጫ ይዞ ለውጤት እንዲበቃ ከተፈለገ ያን ትግል የሚመራው ፓርቲ እዚሁ አገር ውስጥ የሚኖር መሆን አለበት፡፡ ጨቋኙ ሥርዓት ያለው እዚህ ነው፡፡ ተጨቋኙም ሕዝብ ያለው እዚህ ነው፡፡ ስለዚህ ከአትላንቲክ ማዶ ሆኖ የኢትዮጵያን ትግል መምራት ይቻላል ብዬ አላምንም፡፡ በተለይ በትጥቅ ትግል የሚያምኑና ከኤርትራ መንግሥት ጋር ተባብረው ለኢትዮጵያ መፍትሔ እናመጣለን የሚሉ ኃይሎች አዳዲስ ችግር ይወልዱ እንደሆነ እንጂ፣ ምንም ዓይነት የተሻለ ለውጥ ሊያመጡ አይችሉም፡፡

ነገር ግን ሰፊ የአመራር ክፍተት አለ፡፡ አሁን አገር ውስጥ የሕዝቡን ትግል በአግባቡ መምራት የሚችል ተቃዋሚ ፓርቲ አለ ብዬ አላምንም፡፡ ይህም በሁለት ምክንያቶች ነው፡፡ አንዱ ገዥው ፓርቲ ላለፉት 25 ዓመታት በፈጠረው አፈናና ተፅዕኖ ጠንካራ የሆነ ሕዝቡን መምራት የሚችል ተቃዋሚ ፓርቲ እንዳይፈጠር ሆን ብሎ በሠራው ሥራ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ ተቃዋሚ ፓርቲዎች እየተዳከሙና ቦታ እያጡ ነው የሄዱት፡፡ በዚህም ምክንያት አብዛኛው የኅብረተሰብ ክፍል በተቃዋሚዎቹ ተስፋ የቆረጠበት ሁኔታ አለ፡፡ ሁለተኛው ግን በራሳቸው በተቃዋሚዎቹና እነሱን በሚደግፈው የኅብረተሰብ ክፍል ድክመት የመጣ ነው፡፡ አንድ ተቃዋሚ ፓርቲ ጠንካራ ነው የሚባለው ገዥው ፓርቲ የሚያሳድርበትን ተፅዕኖ በብቃት መቋቋም ሲችል ነው፡፡ ሕዝቡ ደግሞ ተቃዋሚ ፓርቲዎችን መከተል ብቻ ሳይሆን ጠንካራ ተቃዋሚ እንዲፈጠር የራሱን አስተዋጽኦ ማበርከት አለበት፡፡ በገንዘብ፣ በዕውቀት፣ በጉልበትና በጊዜ መርዳት አለበት፡፡ ሕዝቡ ካልረዳ ከየትም መጥቶ ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ ሊፈጠር አይችልም፡፡ ራሳቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ውስጣዊ ዴሞክራሲ ኖሯቸው፣ ጠንካራ የሆነ የፖለቲካ ሥራ ሠርተው ማደራጀትና ሕዝቡን በዙሪያቸው ማሰባሰብ አልቻሉም፡፡ ስለዚህ ደካሞች ናቸው፡፡ በዚህ ምክንያት የአመራር ክፍተት ተፈጥሯል፡፡ አሁን አንገብጋቢ ጥያቄ ሆኗል፡፡ ሁሉም በየአካባቢው እየተነሳ የፈለገውን ነገር በሚያደርግበት ሁኔታ ሒደቱ ብቻ ሳይሆን በትግሉ የሚመጣው ውጤት ጥሩ ሊሆን አይችልም፡፡ ከኅብረተሰቡ ትግልና ከገዥው ፓርቲ ማንነት ጋር ሊመጥን የሚችል ተቃዋሚ ፓርቲ መኖር አለበት፡፡

ሪፖርተር ፡- የተፈጠረውን ችግር ለማርገብ ምሁራን፣ ተፅዕኖ ፈጣሪና ታዋቂ ሰዎች፣ የሃይማኖት ድርጅቶች፣ ሲቪል ማኅበራትና የሙያ ማኅበራት የሚጠበቅባቸውን እያደረጉ ነው ብለው ያስባሉ?

አቶ ልደቱ፡- የሚጠበቅባቸውን እያደረጉ ነው ብዬ አላስብም፡፡ እነዚህ አካላት ግጭትን በመፍታትና ውጥረትን በማርገብ ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ ሊያደርጉ ይገባ ነበር፡፡ ይኼ በአገራችንም በተወሰነ ደረጃ የነበረ ነው፡፡ በሌሎች ዓለማት ደግሞ በሰፊው የምናየው ነገር ነው፡፡ አሁን አስተዋጽኦዋቸው በጣም ደካማ ነው፡፡ ይህች አገር ወዴት ትሄዳለች እያሉ ዝም ብለው እያዩ ነው፡፡ በፍርኃትና በግርታ ተውጠው እያዩ ነው፡፡ ይህ ጉዳይ ከቁጥጥር ውጭ ከመሆኑ በፊት ኃላፊነት አለብን ብለው ሲንቀሳቀሱ አይታዩም፡፡ በግለሰብ ደረጃ አንዳንድ ጥረቶችን አያለሁ፡፡ የሲቪልና የሙያ ማኅበራቱ ግን ይህን ጥረት እያደረጉ አይደለም፡፡ ምክንያቱም የፖለቲካ ፓርቲዎቹ ሲዳከሙ እነዚህም ተቋማት አብረው ተዳክመዋል፡፡ ገዥው ፓርቲ በተቀናቃኝነት የሚያያቸው ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ብቻ አይደለም፡፡ የሲቪልና የሙያ ማኅበራትንም ጭምር እንደተቀናቃኝ ያያል፡፡ ስለዚህ እነሱም ተዳክመዋል፡፡ በዚህ ረገድም ያለው ትልቅ ክፍተት ነው፡፡

ሪፖርተር ፡- ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ዕድገት እየታየበት ነው፡፡ ለዚህ አንዱ ቁልፍ ምክንያት የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት አስተዋጽኦ ነው፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ለመግባት ዕቅድ ባላቸው ላይ እነዚህ ግጭቶች በዘላቂነት ምን ዓይነት ተፅዕኖ ይኖራቸዋል?

አቶ ልደቱ፡- ከፍተኛ ተፅዕኖ ይኖራቸዋል፡፡ ተፅዕኖው በውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ላይ የተገደበ ግን አይሆንም፡፡ ቱሪዝሙ በከፍተኛ ሁኔታ ይጎዳል፡፡ ተፅዕኖው ከአሁኑ እየታየ ነው፡፡ ከውጭ አገር ወደ አገር ውስጥ መጥተው ማልማት የሚፈልጉ ሰዎች ብቻ ሳይሆኑ፣ አሁን እያለሙ ያሉ በከፍተኛ ደረጃ ጭንቀት ውስጥ ገብተዋል፡፡ የዚች አገር ዕጣ ፈንታ የሚታወቅ አይደለም፣ አደጋ ያዘለ ነው ብለው ወደኋላ እያሉ ነው፡፡ የአገር ውስጥ ባለሀብቱም አሁን ከማልማት ወደኋላ እያለ ነው፡፡ ከሰሞኑ ችግርም በፊት ለምሳሌ ኦሮሚያ አካባቢ ችግር መፈጠር ከጀመረ በኋላ አብዛኛው ባለሀብት ሰፊ ኢንቨስትመንት ማከናወን ቀርቶ ቤትና መሬት እንኳን ለመግዛት ፈርቷል፡፡ ይኼ በአጠቃላይ ኢኮኖሚያችንን ትልቅ ችግር ውስጥ የሚያስገባ ነው፡፡ የወደፊቱ የአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታም ላይ ትልቅ የሆነ ተፅዕኖ የሚያሳድር ነው፡፡ በእኔ እምነት የልማቱ መቀጠል ለኢትዮጵያ ህልውና ወሳኝ ነው፡፡ ድህነት ኢትዮጵያ ውስጥ ከተንሰራፋ፣ የኢኮኖሚ ዕድገቱ ከተገታ የፖለቲካ ችግራችንም በዚያው መጠን እየተባባሰ ነው የሚሄደው፡፡ ኢኮኖሚው እያደገ ከሄደ ግን የኅብረተሰቡ ኑሮም እየተሻሻለ ወደ ጤናማና የተረጋጋ የፖለቲካ ሁኔታ የመግባት ዕድሉ እየሰፋ ነው የሚሄደው፡፡ መሠረተ ልማት ሲስፋፋ የአገሪቱ አንድነት እየተጠናከረ ነው የሚሄደው፡፡ እየተሠራ ያለው መሠረተ ልማት ዳር አካባቢዎችን ሁሉ መሀል እያደረጋቸው ነው፡፡ አገሩን በሙሉ እያጠበበው ነው፡፡ ይኼ ለኅብረተሰቡ መስተጋብርና አንድነት ቀላል የማይባል አስተዋጽኦ አለው፡፡ ስለዚህ ይኼ አምባገነናዊ ሥርዓት ሥልጣን ላይ እያለም ቢሆን ይህች አገር መልማትና ማደጓ አስፈላጊ ነው፡፡ መካከለኛ ገቢ ያለውና የተማረ ማኅበረሰብ ሲፈጠር ነው የበሰለ የፖለቲካ ሁኔታ ኢትዮጵያ ውስጥ ሊኖር የሚችለው፡፡ ስለዚህ ሥርዓቱን ስለምንቃወም ብቻ ልማቱ ገደል ይግባ ልንል አንችልም፡፡

ሪፖርተር ፡- በዚህ ዓይነት ጊዜ ላይ በአገሪቱ ያሉ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ያላቸው አማራጭ ፖሊሲ ለሕዝቡ ቀርቧል ብለው ያምናሉ? አንዳንዶች መኖራቸውንም እየተጠራጠሩ ነው፡፡

አቶ ልደቱ፡- መኖሩን አሉ፡፡ የሚጠበቅባቸውን ግን እየሠሩ አይደሉም፡፡ ይኼ ያው ከላይ እንዳየነው የአመራር ክፍተት እንዲፈጠር አድርጓል፡፡ እኔ ያለሁበትን ኢዴፓን ጨምሮ አንድ ጠንካራ ሊባል የሚችል ተቃዋሚ ፓርቲ አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ አለ ማለት አይቻልም፡፡ ኅብረተሰቡ ውስጥ ብዙ ብሶት አለ፡፡ ሥርዓቱ በብዙ ችግሮች ውስጥ ተዘፍቋል፡፡ ግን በዚህ ወቅት ተቃዋሚ ፓርቲዎች እንዳሉ አይቆጠርም፡፡ እርግጥ ጥረት የሚያደርጉ ፓርቲዎች አሉ፡፡ አንዳንዶቹ በአቅም ማነስ ሚናቸው በጣም የተገደበ ነው፡፡ ሌሎቹ ችግሩን በትክክለኛው አቅጣጫ ከመምራት ይልቅ ለማባባስ ጥረት ሲያደርጉ ይታያሉ፡፡ አሁን በተቃዋሚ ፓርቲዎች ዙሪያ ያለው ችግር ጎልቶ የወጣበት ነው፡፡ ችግሩ ግን የተቃዋሚ ፓርቲዎች ብቻ ሳይሆን የሕዝቡና የመንግሥትም ነው፡፡ ገዥው ፓርቲም ሰከን ብሎ ለአገር ደኅንነት ማሰብ ካለበት የተቃዋሚ ፓርቲዎች መዳከም ለእሱም የሚጠቅም አይደለም፡፡ በዋናነት ያዳከማቸው እሱ ነው፡፡ አሁን በሰሞኑ ግርግር እንኳን በተቃዋሚ ፓርቲ ዙሪያ ተሳትፎ ያላቸው ሰዎች አስቀድመው በየወረዳውና በየቀበሌ ገበሬ ማኅበሩ በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ ተደርጓል፣ ማስፈራራትም እየደረሰባቸው ነው፡፡ ሥርዓቱ መቶ በመቶ አሸንፌያለሁ ሲል የመድበለ ፓርቲ ሥርዓት እዚህ አገር እንደሌለ በግልጽ ታይቷል፡፡ የብዙኃን ፓርቲ እንዲመጣ መንግሥት ፍላጎት እንደሌለውም ግልጽ ሆኗል፡፡ ወረቀት ላይ አስቀምጦ ለአምባሳደሮችና ለውጭ መንግሥታት ማሳመኛ ካልሆነ በስተቀር በተግባር ለዚህ አገር ሕዝብ የብዙኃን ፓርቲ ሥርዓት ያስፈልገዋል ብሎ እንደማያምን አሳይቷል፡፡ ይኼ ግን አደጋ አለው፡፡ በአገሪቱ ውስጥ እየተፈጠረ ያለውን ግጭት ዛሬ የፀጥታ ኃይሉ ጠንካራ ስለሆነ ሊቆጣጠረው ይችላል፣ እየተቆጣጠረውም ነው፡፡ ሁልጊዜ ግን እየተቆጣጠረው አይኖርም፡፡ ነገር ግን በአንድ ወቅት ከአቅም በላይ ሊሆንና ከቁጥጥር ውጪ ሊሆን ይችላል፡፡ ያኔ ከአንድ ሥርዓት መውደቅ በላይ የአገርን ህልውና የሚያፈርስ ችግር ሊመጣ ይችላል፡፡ ይህ ዓይነት ሁኔታ ለአገር እንደማይጠቅም ከሌሎች አገሮች መማር አለብን፡፡ ካልተቻለ ደግሞ ከራሳችን ታሪክና ሒደት መማር አለብን፡፡ በአብዮትና በነውጥ የሚለወጥ መንግሥት ለአገር የሚጠቅም ቢሆን እስካሁን እናገኘው ነበር፡፡ ምክንያቱም በአመፅም፣ በጦርነትም፣ በአብዮትም መንግሥት ለውጠናል፡፡ ግን የምንፈልገውን ሥርዓት አላገኘንም፡፡ ተመሳሳይ ታሪክ እንዳንደግም መጠንቀቅ አለብን፡፡

ሪፖርተር ፡- በቅርብ ጊዜ ከተነሱት ተቃውሞዎች አንዱ ጥያቄ የሕወሓት የበላይነትን የተመለከተ ነው፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች በትግራይ ተወላጆች ላይ የደረሰው ጥቃት የዚህ ጥያቄ የተሳሳተ መገለጫ መሆኑ ታይቷል፡፡ በሕወሓትና በትግራይ ሕዝብ መካከል ልዩነት እንደሌለ አድርጎ የሚያየው አስተሳሰብ በአገሪቱ እንዲዳብር ተቃዋሚ ፓርቲዎች የራሳቸውን ሚና ተጫውተዋል በሚል ትችት ይቀርባል፡፡ በዚህ ይስማማሉ?

አቶ ልደቱ፡- በተወሰነ ደረጃ እስማማለሁ፡፡ ሥርዓቱም ራሱ ለዚህ ችግር ተጠያቂ ነው፡፡ ሥርዓቱ ራሱ ሕወሓትና የትግራይ ሕዝብ ተለያይተው እንዲታዩ አይፈልግም፡፡ የትግራይ ሕዝብ ሙሉ በሙሉ የሕወሓት ደጋፊ እንደሆነ፣ ትግራይ ውስጥ ተቃዋሚ እንደሌለ አድርጎ ነው ማሳየት የሚፈልገው፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ ደግሞ አብዛኛው የተቃዋሚ ጎራ የትግራይን ሕዝብና ሕወሓትን ለይቶ ማየት አይፈልግም፡፡ ይኼ ስህተት ነው፡፡ በእኔ እምነት የትግራይ ሕዝብና ሕወሓት በሚገባ የተለያዩ ናቸው፡፡ ሕወሓት አንድ የፖለቲካ ኃይል ነው፡፡ ከትግራይ ሕዝብ ውስጥ በድህነት የሚኖር፣ የፖለቲካ ብሶት ያለው፣ በተፅዕኖ ሥር የሚኖር የኅብረተሰብ ክፍል አለ፡፡ ይህን የኅብረተሰብ ክፍል ዕውቅና መንፈግ ትልቅ ጉድለትና ችግር ነው፡፡ አብዛኞቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ይህ ችግር አለባቸው፡፡ ይኼ አስተሳሰብ ለሚያራምዱት ትግልም የሚጠቅም አይደለም፡፡ ይኼ የጠቀመው ትግሉን ሳይሆን ራሱን ሕወሓትን ነው፡፡ ተቃውሞና ብሶትም እያላቸው የትግራይ ተወላጆች ከተቃዋሚው ጋር እንዳይቆሙ አድርጓቸዋል፡፡ የትግራይ ሕዝብ ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ችግር አካል ነው፡፡ ስለወደፊቱ የኢትዮጵያ የፖለቲካ መፍትሔ ስናስብም የትግራይ ሕዝብ የመፍትሔው አንድ አካል ነው፡፡ የትግራይን ሕዝብ የችግሩ ምንጭ ብቻ አድርጎ ማየት ተገቢ አይደለም፡፡

ሪፖርተር ፡- የክልል ፖሊስ፣ የፌዴራል ፖሊስ፣ መከላከያና ሌሎች የፀጥታ ኃይሎች ሥልጣንና ኃላፊነት በሕግ ማዕቀፉ በግልጽ ተቀምጧል፡፡ በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የተነሱትን ግጭቶችና አለመግባባቶች ለማብረድ እነዚህ ኃይሎች የተሰማሩበት ሁኔታ በሕጉ መሠረት በግልጽ ልዩነቶች እየታዩ የተከናወነ ነው ማለት ይቻላል?

አቶ ልደቱ፡- ልዩነታቸው በግልጽ አይታይም፡፡ አይደለም በተቀመጠላቸው የሕግ አግባብ ሊሠሩና ማን እንደሚመራቸው የሚታወቅ አይመስለኝም፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች የሚታየው ነገር በጣም ቅጥ ያጣ ነው፡፡ በአካባቢው ፖሊስ መፈታት የሚችል አንዳንድ ጥቃቅን ነገር ውስጥ መከላከያ ገብቶበት ታያለህ፡፡ በአንዳንድ ቦታ ደግሞ ፖሊስም መከላከያም ጠፍቶ የአካባቢው ሚሊሺያዎች የድሮ ረሽና ቤልጂግ ይዘው ችግሩን ለመፍታት ይሞክራሉ፡፡ መሬት ላይ የምናየው ሁኔታ ሕጉን የተከተለ አይደለም፡፡ እኔ አሁን ነው ከላሊበላ የመጣሁት (ነሐሴ 11 ቀን 2008 ዓ.ም.)፡፡ ረፋድ ላይ በከተማው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ታውጇል፡፡ የዜጎች መብት ተገትቶ በወታደራዊ ኃይል ቁጥጥር ሥር ውሏል፡፡ በአደባባይ ብቻ ሳይሆን በየቤቱ እየተገባ የሚደረገው ማስፈራሪያና ማስጠንቀቂያ በጣም የሚገርም ነው፡፡ በአገሪቱ ውስጥ ትልቅ ጦርነት እንዳለ የሚያስመስል ነበር፡፡ በከፍተኛ ሁኔታ ከተማዋን ወረዋት ያሉት የገበሬ ታጣቂ ሚሊሺያዎች ናቸው፡፡ በተለያዩ የአማራ ክልል አካባቢዎች እንዳየሁት በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ያሉ ሰዎች በአግባቡ አመራር እየሰጡ አይደለም፡፡ ማነው መሪው? ማነው ተመሪው? ትዕዞዞችና ውሳኔዎች ከየትኛው አካል ነው የሚመጡት? የሚለው ግልጽነት ያለው አይመስለኝም፡፡ ይኼም አንድ ትልቅ አደጋ ይመስለኛል፡፡

ሪፖርተር ፡- መንግሥት ብሔርን መሠረት ያደረገውን የፌዴራል ሥርዓት በድጋሚ ሊያጤነው እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን ይህ የሥርዓቱ ምዕላድ ከመሆኑ አኳያ በኢሕአዴግ ተቀባይነት ይኖረዋል ብለው ይገምታሉ?

አቶ ልደቱ፡- ይህን ለመለወጥ ከባድ ነው፡፡ ምክንያቱም ዋና አጀንዳ ተደርጎ ከትጥቅ ትግሉ ጊዜ ጀምሮ ሲቀነቀን የነበረ አጀንዳ ነው፡፡ ስለዚህ ይኼን አጀንዳ ኢሕአዴግ በቀላሉ መለወጥ ይችላል ብዬ አላምንም፡፡ ነገር ግን የአገሪቱን ህልውና የሚፈታተን አጀንዳ እየሆነ ነው፡፡ ከባድነቱ ለኢሕአዴግ ብቻ አይደለም፡፡ ለ25 ዓመታት ሙሉ ለአዲሱ ትውልድ ሲሰበክ የኖረውን ፖለቲካ ካየን ይኼን ሁኔታ ለመቀየር ሲታሰብ በከፍተኛ ጥንቃቄ መያዝ እንዳለበት ይገባኛል፡፡ ምክንያቱም አንዳንድ ነገሮች እንዳይመለሱ ሆነው ባለፉት ዓመታት የተቀየሩ አሉ፡፡ ስለዚህ ብሔርን መሠረት ያደረገው የፌዴራል ሥርዓት በአዲስ አደረጃጀት ይተካ ማለት ቀላል ነገር አይደለም፡፡ ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚያስፈልገው ነው፡፡ ነገር ግን የውይይት መድረክ መከፈት አለበት፡፡ ሥርዓቱ አንድ ዓይነት አስተሳሰብ ሁልጊዜ እያሰበ የተለየ ውጤት ማግኘት አይችልም፡፡ የውስጥ ችግር ቢሆን ኖሮ በኢሕአዴግ ደረጃ ብቻ ተወያይቶ ሊፈታው ይችል ነበር፡፡ ይኼ ግን የአገር ችግር ነው፡፡ የሚመለከታቸው አካላትና ሕዝቡ ተሳትፎ ሊያደርጉ ይገባል፡፡ አንድ ሥርዓት በተገቢው ጊዜና ወቅት ለውጦች ማድረግ ካልቻለ የሚያስተናግደው አብዮትና የትጥቅ ትግል ነው፡፡ ከ25 ዓመታት በፊት በነበረው የደርግ አስተሳሰብ ወይም የንጉሡ ዘመን አስተሳሰብ የኢትዮጵያን ችግር መፍታት አይቻልም፡፡ ስለዚህ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም በኢሕአዴግ በኩል ያለውን ሥጋት ማጤን አለባቸው፡፡ የእነሱም አመለካከት የመፍትሔው አካል ሆኖ መቅረብ አለበት፡፡ ኢዴፓ ብሔራዊ መግባባት የሚያስገኝ ብሔራዊ እርቅ ይኑር ብሎ ሲጠይቅ ሥርዓቱ ማን የተጣለ አለ እያለ ሲያሾፍ ነበር፡፡ አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ሁኔታ ግን እንዲህ ዓይነት ነገር አስፈላጊ መሆኑን አጉልቶ እያሳየ ነው፡፡

ሪፖርተር ፡- ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ገዥው ፓርቲ ባለፉት 15 ዓመታት የተጓዘበትን መንገድ በጥልቀት ገምግሞ ማሻሻያ ለማድረግ መዘጋጀቱን አስታውቀዋል፡፡ በእርስዎ ግምገማ ማሻሻያ የሚያስፈልጋቸው አንኳር አጀንዳዎች የትኞቹ ናቸው?

አቶ ልደቱ፡- ኢሕአዴጎች መወያየታቸው አስፈላጊ ነው፡፡ ነገር ግን ከኢሕአዴግ ያልመጣ ለውጥን ሁልጊዜም መቀበል አይፈልጉም፡፡ ሰፊ መሠረት ያለው መፍትሔ ግን ይፈለጋል፡፡ ስለዚህ የሁላችንም ተሳትፎ ያለበት መድረክ ያስፈልጋል፡፡ ከኢሕአዴግ ጋር ያለንን ሁሉንም ልዩነት ማስታረቅ አንችልም፡፡ ልዩነት በአግባቡ ሲስተናገድ ለአገር ይጥቅማል፡፡ ዋናው ችግር ኢሕአዴግ ሥልጣን ሲይዝ አስተሳሰቡን በሕገ መንግሥቱ አማካይነት መዋቅር ከማድረጉ የሚነሳ ነው፡፡ ከመጀመሪያው ሰፊ መሠረት ያለው ውይይት ተደርጎ የጋራ የሆነ ሕገ መንግሥት እንዲወጣ አልተደረገም፡፡ የብዙ የኅብረተሰብ ክፍሎችን ጥያቄ ያላካተተ ሕገ መንግሥት ነው ያለን፡፡ ይኼን በደንብ አድርጎ በድጋሚ ማየት ያስፈልጋል፡፡ ነገር ግን ይህን ለውጥ የምናመጣው በነውጥ አይደለም፡፡ ራሱ ሕገ መንግሥቱን ለማሻሻል የሚያስፈልጉ ነገሮችን አስቀምጧል፡፡ ዋናው የለውጥ አጀንዳ መሆን ያለበት የፖለቲካ ምኅዳሩን ለሁላችንም ምቹና እኩል እንዲሆን የማድረግ ጉዳይ ነው፡፡ ተቋማትን ገለልተኛና ነፃ በሆነ ሁኔታ ማቋቋም፣ ነፃ ሚዲያ ማቋቋም ላይ ከተስማማን የትኛው አስተሳሰብ አሸናፊ ሆኖ ይወጣል የሚለውን ሕዝብ ይፈርዳል፡፡

ሪፖርተር ፡- አንዳንድ ሪፖርቶች በቅርቡ ከተከሰቱት ተቃውሞዎች የኢሕአዴግ አባል ፓርቲዎች ከፓርቲ ዲሲፕሊን አፈንግጠው ነፃነታቸውን ለማግኘት እየጣሩ ስለመሆኑ ማሳያዎች ተገኝተዋል በማለት ጠቁመዋል፡፡ በዚህ ሐሳብ ይስማማሉ?

አቶ ልደቱ፡- ወሬውን እኔም ሰምቼዋለሁ፡፡ ትክክለኛ ስለመሆኑ ማረጋገጫ የለኝም፡፡ በቂ ምልክትም አላየሁም፡፡ አንዳንዱ የኅብረተሰብ ክፍልም እንዲሆን የሚፈልገውን ይመስለኛል የሚያወራው፡፡ ለእኔ የኢሕአዴግ መፍረስ የሚያስደስት ነገር አይደለም፡፡ ኢሕአዴግ እንደ አንድ የፖለቲካ ፓርቲ መቀጠል አለበት፡፡ ኢሕአዴግ ትልቅ ድርጅት እንደመሆኑና የአገሪቱን አጠቃላይ ህልውና ተቆጣጥሮ የያዘ በመሆኑ እሱን የመፍትሔ አካል ሳናደርግ ወደ መፍትሔው መሄድ እንችላለን ብዬ አላምንም፡፡ ኢሕአዴግ የሁላችንንም መብት እንዲያከብርና የሌሎች ፓርቲዎችንም ነፃነት እንዲያከብር ጥረት ማድረግ ነው እንጂ፣ የእሱ መከፋፈልና መፍረስ ምናልባት ችግሩን የበለጠ ያባብሰውና ቅጥ ስለሚያሳጣው ለአገሪቱ ጠቃሚ ነው ብዬ አላምንም፡፡

ምንጭ – ሪፖርተር