CURRENT

ካናዳ ኦታዋ የምንኖር ኢትዮጵያዊ እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የሃገራችንን ወቅታዊ ሁኔታ አስመልክቶ የተሠጠ መግለጫ

By Admin

October 28, 2016

ጥቅምት 2009

በካናዳ ኦታዋ የምንኖር ኢትዮጵያዊ እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የሃገራችንን ወቅታዊ ሁኔታ አስመልክቶ የተሠጠ መግለጫ

በካናዳ ኦታዋ የምንገኝ ኢትዮጵያዊያንና ትውልድ ኢትዮጵያዊያን ሁላችንም እንደምናውቀው ኢትዮጵያ ለዘመናት የቤሄር ቤሄረሰቦች ብዙሃነቷ በገዢዎች ተደፍቆ ዜጎች፣ መሰረታዊ መብታቸው ተነፍጎ ኣገሪቱ በድህነትና ኋላቀርነት አረንቋ ተዘፍቃ፣ ለረሃብና ለእርዛት ሲዳረጉ መቆየታቸው የማይካድ ሃቅ ነው። አስከፊውን የደርግ አምባገነን ስርዓት በህዝቦች ተጋድሎ ከወደቀ ማግስት አንስቶ ላለፉት 25 አመታት ሁሉም ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦችን ያሳተፈ ፈዴራላዊ ስርኣት በመመስረት ኣስተማማኝ ሰላም ሰፍኖ የጋራ ጠላታችን በሆነው ድህነት ላይ ጦርነት በማወጅ፣ ኢትዮጵያ የነበራትን የርሃብና ድህነት መጥፎ ገጽታ በመቀየር አመርቂ የልማት ድሎችን እንድታስመዘግብ ኣስችሏታል፡፡ ይሁንና በአሁኑ ወቅት በሀገራችን በአንዳንድ አካባቢዎች በተለይም በኣማራና ኦሮምያ ቤሄራዊ ክልሎች የተከሰቱ የእርስ በርስ ብጥብጥና የንብረት ውድምት እንቅስቃሴ የሃገራችንን አንድነት የሚንዱ, የህዝቦች በሰላም ኣብሮ የመኖር ተስፋ የሚያጨልም ክስተት ሆኖ ኣገንተነዋል፡፡ ጽንፈኞች በተለይም ደግሞ ከኢትዮጵያ ውጭ የሚኖሩ ተቃዋሚ ነን ባዮች የህዝቡን ፍትሃዊ የመልካም ኣስተዳደር ጥያቄ መልኩን እዲቀይር በማድረግ በተለያየ መንገድ ቅሬታ ያለው የወጣቱ ክፍልና ህጻናት በማሰልፍ ወደ ኣመጽ እንዲያመራ በማድረግ የንጹሃን ዜጎች ህይወት በከንቱ መጥፋት፣ የንብረት መውደም እንዲሁም በዘር የጥላቻ ቅስቀሳ ምክንያት ዜጎች ለዘመናት ከኖሩበት መንደር እንዲፈናቀሉ ኣድርጓል። የኢትዮጵያ ህዝቦች፣ የመልካም ኣስተዳደር እጦት ሁሉንም የሃገሪቱ ዜጎች እያማረረ ያለ ኣንገብጋቢ ጥያቄ በመሆኑ መንግስት ግዜ ሳይሰጥ ተገቢውን ምላሽ በወቅቱ መስጠት እንዳለበት እየጠየቅን፣ ህዝቡም በበኩሉ ጥያቄዎቹ በሰከነና በበሰለ ኣኳህዋን በሰላማዊ መንገድ በማቅረብ ለጥያቄዎቻቸው ምላሽ እንዲያገኙ እንጠይቃለን። ከዛ በዘለለ ሃገራችን ኢትዮጵያ ላለፉት 25 አመታት የገነባቻቸው የልማት ተቋማት በማውደም፣ ሰላም በማደፍረስ፣ ዘርን መሰረት ያደረገ የጥላቻ ቅስቀሳ በማሰራጨት የህልውናችን መሰረት የሆነውን ኣብሮነት የሚያጠፋ ብሎም የሁሉም ምሰሶ የሆነውን ህግ መንግስት የሚንድ፣ በውጭ ሃይሎች የተደገፈ የአምጽ ነውጥ ሁሉም ሰላም ናፋቂና ሃገር ወዳድ ዜጎች ሊያወግዙት ይገባል እንላለን። በውጭ ሃገራት የሚኖሩ የዳያስፓራ ጽንፈኞች፣ በዋናነት ጠባቡ ኦነግ እና የትምክህተኞች ስብስብ የሆነው ግንቦት 7፣ እንዲሁም የነሱ መገልገያ የሆኑት ኢትዮጵያ ሳትላይት ተለቪዥን (ESAT) እና የኦሮምያ ሚድያ ኔትወርክ (OMN) የተባሉ የዘር ጥላቻ ፕሮፓጋንዳ የሚያሰራጩ ሚድያዎች ወጣቱን በማደናገርና በማሸፈት የህዝቡን እውነተኛ ጥያቄ ኣቅጣጫ እንዲስት በማድረግ በሃገራችን ኢትዮጵያ ለዘመናት ተፈቃቅረውና ተቻችለው በኖሩ ህዝቦች መካከል ግጭት እንዲፈጠር፣ ኢትዮጵያ እንድትዳከም ብሎም እኔ ከሌለሁ ሰርዶ ኣይብቀል በሚል ፈሊጥ የኢትዮጵያ ውድቅትና መፍረስ ከሚመኙና እየሰሩ ካሉ ግብጽና ኤርትራ ጎን በመሰልፍ ሃገራችን እንድትተራመስ እየሰሩ ይገኛሉ። ይህ አይነቱ አጸያፊ ተግባር ከአንድ ኢትዮጵያዊ የማይጠበቅ ክህደት ሆኖ አግኝተነዋል፣ በመሆኑም ሁሉም ኣገር ወዳድ ዜጋ ሊኮንነው ዪገባል እንላለን። ከዚህ በመነሳት እኛ በካናዳ ረእሰ መዲና በሆነችው ኦታዋ የምንኖር ኢትዮጵያዊያንና ትውልድ ኢትዮጵያዊያን፣ ያወጣነውን የኣቋም መግለጫ እንደሚከተለው አስፍረናል፡፡

1. በሃገራችን ኢትዮጵያ በተለያዩ ኣከባቢዎች በተለይም በኣማራ እና ኦሮሚያ ክልሎች በተከሰተው ኣለመረጋጋት ሂወታቸው ላጡ የፖሊስ ኣባላት ና የጸጥታ ኣስከባሪዎች እንደዚሁም ሰላማዊ ዜጎች የተሰማንን ጥልቅ ሃዘን በመግለጽ ለቤተሰቦቻቸው መጽናናትን እንመኛለን።

2. ጽንፈኞች ሆን ብለው በሚረጩት የዘረኝነት ቅስቀሳ በተለይ ደግሞ በትግራይ ወንድምና እህቶቻችን ላይ የደረሰው በደል፣ የንብረት መውደም እንዲሁም ለዘመናት ከኖሩበት ቦታ መፈናቀል አጥብቀን እናወግዘዋልን።

3. ግንቦት 7 እና ኦነግ ለስልጣንና ለገንዘብ ጥቅም ሲሉ የሃገራቸውን ሉዓላዊነትና ህልውና አደጋ ላይ ለመጣል ከታሪካዊ ጠላቶቻችን ግብፅና ኤርትራ ጋር በመሻረክ እያደረሱ ያሉትን በተለያዩ የሃገሪቱ ኣከባቢዎች የሰው ህይወት መጥፋትና የልማት ተቋማት መውደም አጥብቀን እናወግዛለን።

4. ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በየትኛውም የሃገሪቱ ክልሎች የመኖር መብቱ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ህገ መንግስት ያጸደቀው የተፈጥሮ መብት በመሆኑ የፈደራል መንግስት፣ የክልል መንግስታት፣ እንዲሁም የከተሞችና የአካባቢ መስተዳድሮች በፀረ ሰላም ሃይሎች እንዳይናድ ዋስትና ሰጥተው ሊጠብቁት ይገባል እንላለን።

5. ኢትዮጵያ ድህነትና ኋላቀርነትን ዋና ጠላቶቿ አድርጋ በመነሳት ህዝቦቿን ኣስተባብራ አስደናቂ የልማት ውጠቶችን በማስመዝገብ ላይ ባለችበት ወቅት፤ ከዛም በዘለል ድህነትን ለአንዴና ለመጨረሻ ግዜ ታሪክ ለማድረግ የውሃ ሃይል አስፈለጊ በመሆኑ ለዘመናት የግብፆች ሲሳይ ሆኖ የኖረውን ከጉያችን የሚፈልቀው የአባይ ወንዝ ተፋሰስ በመገደብ በኛ ትውልድ ታሪክ ለመስራት ግንባታ ላይ ባለችበት ወቅት እኛም ሲጀመር ጀምሮ እንደ ደገፍነው ሁሉ አሁንም በየትኛውም መንገድ ከኛ የሚጠበቅ አስተዋጾ ለማበርከት ዝግጁ መሆናችን እናረጋግጣለን።

6. በሃገራችን ኢትዮጵያ ሰላምና ዴሞክራሲ የበለጠ እንዲያብቡና የሁሉም ያገባኛል የሚሉ ሰላማዊ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተሳታፊ ያደረገ ሂደት እንዲኖር ኢህአዴግ መራሹ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ መንግስት የፖለቲካ ምህዳሩን በማስፋት ጤነኛና ብቁ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ድጋፍ የማድረግ ሃላፊነት እንዳለበት በማመን፣ በተመሳሳይ መልኩ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች/ድርጅቶች በበኩላቸው በመወንጃጀል የተመሰረት በጠላነት የመፈራርጅ የፖለቲካ ስልት ነጻ ወጥተው ለሁሉም ኢትዮጵያዊያን የሚሰራ አጀንዳ በመቅረጽ ኣማራጭ የፖለቲካ ድርጅት በመሆን ብቁ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ የድርሻቸውን እንዲወጡ እያሳሰብን፣ በተጓዳኝ ሃገራችንና ህዝቦችዋ ለብጥብጥና ለአደጋ በሚዳርጉ የጥፋት ሃይሎች እኩይ ተግባር እንድትኮንኑ እንጠይቃለን።

7. በአሜሪካ መሽገው የጥላቻና የዘረኝነት ፕሮፓጋንዳ የሚቀሰቅሱ ሚድያዎች የኢትዮጵያ ሳትላይት ተሌቭዥን (ESAT) እና በኦንግ የሚመራው የኦሮሚያ ሚድያ ኔትዎርክ(OMN)፣ እንዲሁም በአሜሪካና በጀርመን ግብር ከፋዮች ድጎማ የሚተዳደሩት ራድዮ ጣብያዎች የኣሜሪካ ድምጽ (VOA) እና የጀርመኑ ዶቸ ቨለ፣ ህዝብን በማቀራረብ ፈንታ በኣንጻሩ በኢትዮጵያ የውስጥ ፖለቲካ ጣልቃ በመግባት ህዝቦችዋ በማለያየትና ግጭት በመቀስቀስ ሲኳትኑ ይስተዋላሉ፣ ስለሆነም የኢትዮጵያ መንግስት ከአሜሪካና ጀርመን መንግስታት ጋር ተነጋግሮ ኣመጽ በመቀስቀስ ወንጀል እንዲከሰሱ እና ህጋዊ እርምጃ እንዲወሰድባቸው ኣጥብቀን እንጠይቃለን።

8. ሃገራችን ኢትዮጵያ፣ የረጅም ግዜ ኣኩሪ ታሪክ ያላት፣ ብዙ ቤሄር ቤሄረ ሰቦች በስምምነት እና በፍቅር የሚኖሩባት፣ የተለያዩ ሃይማኖቶች በመቻቻል የሚስተናገዱባት ኣገር ከምሆኗ ባሻገር ልዩነታቸው እንደተጠበቀ ሆኖ የውች ወራሪን ብህብረት የተዋጉባት፣ ወንድ ሴት ሳይሉ ኣጥንታቸው በመከስከስ፣ ደማቸው በማፍሰስ ኣኩሪና ነጻ የሆነችውን ኢትዮጵያ እንዳቆዩልን ሁሉ፣ እኛም የኣሁኑ ትውልድ በፓለቲካ፣ በኢኮኖሚና በማህበራዊ ኑሮ የበለጸገች እና ያደገች ኣገር ገንብተን ለመጪው ትውልድ የማስረከብ ሃላፊነት እንዳለብን እናስገነዝባለን።

9. በውጭ ሀገር በድሎት የምንኖር የዳያስፖራ አባላትና ተቃዋሚዎች፣ በማህበራዊገጾች፣ ሬዲዮና ቴሌቭዥን የሚተላለፉ የዘር ጥላቻ ስብከቶች የሃገራችን ህልውና ለአደጋ የሚጥሉና የህዝባችን የዘመናት የመቻቻልና ኣብሮ የመኖርን ባህል የሚንዱ ስለሆኑ ሁላችንም ልናወግዛቸው ይገባል። በኣንፃሩ የሰላምዊ እና የዲሞክራሲያዊ ስርኣት መስፈን ልዩነቶቻችን በሰለጠነ መንገድ ኣስታርቀን የበኩላችንን ገንቢ አስተዋጾ በማበርከት የሰላም ዋስትና ያላት ሃገር እንድትኖረን “ድር ቢያብር አንበሳ ያሰር” ነውና በልማት ግንባታ ላይ ካሉት የሃገራችን ህዝቦችና መንግስት ጎን ተሰልፈን እየተደረገ ባለው የልማት ዘመቻ ተሳታፊ በመሆን ድህነት ላንዴና ለመጨረሻ ግዜ ታሪክ በማድረግ ሁላችንም የምንኮራባትና የምንኖርባት ሃገር በኣንድነት እንገነባ ዘንድ ጥርያችንን እናቀርባለን።

10. ጽንፈኛ ዳያስፖራ ተቋዋሚዎችና ደጋፊዎቻቸው፣ የሃገራቸው ልማትና እድገት በሚደግፉ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን በተለይም የህዳሴ ግድባችን ድጋፍ ለማድረግ በሚደርጉት የገንዘብ መዋጮ እና የሞራል ድጋፍ ለማስቆም በተለያዩ የኣለማችን ክፍሎች የሚኖሩ ሃገር ወዳድ ወገኖቻችን ላይ የማስፈራራት ብሎም በኣካል ሃይል በመጠቀም ጉዳት በማድረስ በሃገራቸው እድገት ተሳታፊ እንዳይሆኑ ሁውከት እየፈጠሩ ይገኛሉ። እንደዚሁም የኢትዮጵያ መንግስት የሚልካቸው ልኡካን ከዳያስፖራው ጋር በውይይት እንዳይግባቡና ልጥያቄዎቻቸው ኣግባብ ያለው መልስ እንዳያገኙ በማድረግ በየስብሰባ ኣዳራሹ እየተገኙ መረብሽ ስራቸው ኣርገው ይዘውታል። ለዚህም፣ የየሃገራቱ መንግስታት ለሰላም ወዳዱንና ሃገር ኣፍቃሪው የዳያስፖራ ማህበረሰብ ኣስፈላጊውን የጥበቃ ዋስትና እንዲደርግላቸው እንጠይቃለን።

11. በመቻቻልና በመፈቃቀር ለዘመናት ኣብረው የኖሩትን የሃገራችን ህዝቦች በዘር፣ በሃይማኖት በመከፋፋል የሃገራችን ልእላዊነትና ኣንድነት ለኣደጋ የሚጥሉ ማንኛቸውም የውጭና የውስጥ ሃይሎች መሰሪ ተግባር ኣጥብቀን የምናወግዘውና የማንደራደርበት ጉዳይ መሆኑ ሁሉም ወድጅ ጠላቶቻችን ሊያውቁት ይገባል።

12. በመጨረሻም ሃገራችን የጀመረችው ድህነትን ታሪክ የማድረግ ያላሰለሰ የልማት ዘመቻ በመደገፍ በማንኛውም ረገድ ተሳታፊ ለመሆን ዝግጁነታችን በመግለጽ፣ በተለይም ደግሞ ለድህነታችን መቛጫ ከፍተኛ ኣስተዋጾ የሚያበረክተው የህዳሴ ግድባችን ፍጻሜ ለማድረስ ከኢትዮጵያ ህዝብና መንግስት ጎን በመሆን እስከ የመጨረሻዋ ደቂቃ ድረስ በገንዘብና በቁሳቁስ፣ እንዲሁም በሞራልና ከኛ የሚጠበቀብንን ሁሉ ለማበርከት ቁርጠኝነታችና ኣጋርነታችን እናረጋግጣለን።

ብዙሃነታችን ዉበታችን፣ ኣንድነታችን ጥንካርያችን ነው!!!

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!!

በካናዳ ኦታዋ የምንኖር ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን. ጥቅምት, 2009.