Ethiopiaprosperous
Ethiopian News Ethiopian Daily news, Regarding political and social Issues.

ጥልቅ ተሃድሶው ጠንካራ አመራር ለመገንባት የሚያስችል መሆኑን ህወሃት ገለጸ

0 520

Get real time updates directly on you device, subscribe now.

ጥልቅ ተሃድሶው ጠንካራ አመራር ለመገንባት የሚያስችል መሆኑን ህወሃት ገለጸ

የተጀመረው በጥልቅ የመታደስ የትግል አቅጣጫ ህዝብን የሚያገለግልና አመኔታ ያለው ጠንካራ የፖለቲካ አመራር ለመገንባት የሚያስችል መሆኑን ሕዝባዊ ወያኔ ሐርነት ትግራይ /ህወሃት/ አስታወቀ።
የድርጅቱን ከፍተኛ አመራሮች ጥልቅ ተሃድሶ ተከትሎ በትግራይ ደቡባዊ ዞን የመካከለኛ አመራሮች ቀጣይ የተሃድሶ ግምገማ ትናንት በማይጨው ከተማ ተጀምሯል።

የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባልና የክልሉ ትምህርት ቢሮ ሃላፊ አቶ ጎበዛይ ወልደአረጋይ በመድረኩ ላይ እንደተናገሩት ፣ ህወሓት አደረጃጀቱን የማሻሻል አስተሳሰብን የማስተካከልና የጥልቅ ተሃድሶ ልምዱ ካሁን በፊትም የነበረ ነው።

” ከ1977 እስከ 1980 በነበረው ጊዜ ማለትም ከ1977 አጋማሽ ወዲህ በነበረው ተሃድሶ እርስ በራሳችን የማደራጀት ፤አስተሳሰባችንን የማጥራትና አሁን እንደምናደርገው ሁሉ ስልጠና በማካሔድ ሰፊ እንቅስቃሴ ተደርጓል።” ብለዋል፡፡

“ያለፉት የድርጅቱ ተሃድሶዎችም የሁሉም አባላቱና የሰራዊቱን ተልእኮ በማሳደግ ድርብርብ ድሎች ተመዝግበውበታል” ሲሉም ገልጸዋል።

ቀደም ሲልም ደርግን ለመደምሰስ ስትራተጂካዊ እቅድ በመንደፍ ትግሉን የሚያጠናክር የውጭና የሃገር ውስጥ እንቅስቃሴዎችን በማድረግ ድርጅቱ ጠንካራ የሕዝብ ወገንተኛነቱን ማሳየት በመቻሉ በ1983 የትጥቅ ትግሉን በድል አጠናቋል።

ባለፉት 15 ዓመታትም ሕዝቡን ተጠቃሚ ያደረጉ የመሰረተ ልማት ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸው በየዓመቱ ሲመዘገብ የቆየው ባለሁለት አሃዝ እድገትም የድርጅቱ ጥንካሬና ተሳትፎ ጉልህ መገለጫ መሆኑን አስረድተዋል።

በድርጅቱ ውስጥ የታዩት ስልጣንን የግል መጠቀሚያ የማድረግ ዝንባሌ፣ያልተመለሱ የህዝብ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለአሁኑ ጥልቅ ተሃድሶ መካሔድ ዋንኛ ምክንያት መሆናቸውንም አቶ ጎበዛይ ተናግረዋል።

“በድርጅቱ ለተፈጠሩት ችግሮችም ዋነኛ ተጠያቂው ክፍተኛ አመራሩ ነው” ያሉት አቶ ጎበዛይ፣ መካከለኛ አመራሩ ቸግሮቹን ለማስወገድ በሚደረገው ጥልቅ ተሃድሶ ላይ የጎላ ተሳትፎ ማድረግ እንደሚጠበቅበት አሳስበዋል።

ከተሳታፊዎች መካከል የኮረም ከተማ ከንቲባ አቶ ዳርጌ መረሳ እንደገለጹት በዞን ደረጃ ያለው አመራር በተሃድሶ መድረኩ ከጉድለቶቹ ፀድቶ አንድ አስተሳሰብ በመያዝ ከአሁኑ የበለጠ እድገት በማምጣት ህዝቡን ለመካስ መዘጋጀት አለበት።

በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረትም ጥልቅ ተሃድሶው ሕዝብን ማዕከል በማድረግ በግምገማው መጥራት ያለባቸው ችግሮችን ለይቶ በማጋለጥ ወደ ታች ማውረድ ከመድረኩ የሚጠበቅ ጉዳይ ነው
ሌላው ተሳታፊ አቶ ጉዑሽ ሃይሉ በሰጡት አስተየየት፣መድረኩ ባለፉት አመታት ያሳየናቸው የኪራይ ሰብሳቢነት፤ የጠባብነት አስተሳሰብና የግል ጥቅመኝነትን ለማስወገድ ቃል የሚገባበት መሆኑን ገልጸዋል።

ከዚህ ባለፈም የሁለተኛውን የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ በተሳካ መልኩ ለማከናወን ችግሮችን ከወዲሁ ለማረም የሚያስችል እንደሆነም ተናግረዋል።

ለአራት ቀናት በሚቆየው መድረክ ላይ ከተሃድሶ ግምገማው ባለፈ “የጉዟችን ህዳሴና በድርጅታችን ያለው ፈታናዎችና አደጋዎች” በሚል ርዕስ የተዘጋጀ ሰነድና የተቀናጀ የ2009 ዓ.ም የከተሞች እቅድ ላይ ውይይት እንደሚደረግም ተገልጿል።

ምንጭ፡-ኢዜአ-ማይጨው ህዳር 14/2009

Leave A Reply

Your email address will not be published.

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

This website uses cookies to improve your experience. We'll assume you're ok with this, but you can opt-out if you wish. Accept Read More

Privacy & Cookies Policy