Ethiopiaprosperous
Ethiopian News Ethiopian Daily news, Regarding political and social Issues.

ታዳሽ ሃይል የማመንጨት ስራው ለአፍታም አታቆምም ፡- ጠ/ሚ/ር ኃይለማርያም

0 537

Get real time updates directly on you device, subscribe now.

ታዳሽ ሃይል የማመንጨት ስራው ለአፍታም አታቆምም ፡- ጠ/ሚ/ር ኃይለማርያም

ታህሳስ 8፣ 2009

ኢትዮጵያ ታዳሽ ሃይል የማመንጨት ስራዋ ለአፍታም እንደማታቆም ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ አስታወቁ።

በአንድ ነጥብ አምስት ቢሊዮን ዩሮ የተገነባው ጊቤ ሶስት የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ግድብ ዛሬ ተመርቋል፡፡

ከ20 አመት በፊት 180 ሜጋ ዋት ከፍላጎታችሁ በላይ ነው የተባልን ህዝቦች ዛሬ 5ሺህ ሜጋ ዋት ማመንጨት የቻልን ቢሆንም አሁንም የሃይል ፍላጎታችን እጅግ ልቆ ይገኛል ያሉት ጠቅላይ ሚንስትሩ በከፍተኛ ፍጥነት እያደገች ላለች ኢትዮጵያ የልማት ፍላጎቷን ለማርካት ተጨማሪ ታዳሽ ሃይል  ማመንጨታችንን ለአፍታም አናቆምም ብለዋል።

የግድቡ ግንባታ ኢትዮጵያ ለታዳሽ ሃይል የሰጠችውን ትኩረት እንደሚያሳይም ገልጸዋል።

ጠቅላይ ሚንስትሩ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ አካል የሆነው የጊቤ 3 ግንባታ አንዱ ስኬታችን ነው ብለዋል፡፡

በዚህም በኢትዮጵያ ከአንድ ከፍታ ወደ ሌላ ከፍታ መሸጋገር ባህል መሆኑን ማሳያ እንደሆነ  ጠቅሰዋል፡፡

ኢትዮጵያ የምትከተለው ለአየር ንብረት የማይበገር የአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂ ለሌሎች ሀገራትም በተሞክሮነት የሚጠቀስ መሆኑን ጠቅላይ ሚንስትሩ አስታውቀዋል፡፡

የግድቡ ግንባታ ከሌሎች ሀገሮች ገር ለመተሳሰርና በአገሪቱ ያለውን ዝቅተኛ የነፍስ ወከፍ የሃይል አቅርቦት ለማሳደግ ይረዳል ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያን በምስራቅ አፍሪከ የታዳሽ ሃይል ማእከል ለማድረግ የተጀመረው ስራም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡

የመነጨውን ሃይል ለማስተላለፍና ለማከፋፈል በከፍተኛ ትኩረት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው በገጠር የሃይል አቅርቦትን ለማስፋፋትም እንደሚሰራ ተናግረዋል፡፡

ጠቅላይ ሚንስትር ኃይለማርያም ጊቤ ሶስት በርካታ ፈተና ያለፈ የሀገራችን ስኬት መሆኑን ጠቁመዋል።

ፕሮጅክቱ  ወደ ፊት ለምንሰራቸው ታላቅ ፕሮጀክቶች ተሞክሮ ሆኖናል ያሉት ጠቅላይ ሚንስትሩ  የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታም ከማጋመስ አልፈን ወደ ማገባደጃው እየገሰገስን እንገኛለን ብለዋል፡፡

ለአካባቢ ጥበቃም ሆነ ለህብረተሰቡ ጥቅም ከመስጠቱም በላይ ግድቡ በኤልኒኖ ምክንያት የሃይል ችግር እንዳይከሰት በማድረግ የቁርጥ ቀን ደራሽ ፕሮጀክት ሆኗል፡፡

የአዲትዮጵያ ኤለክትሪክ ሃይልዋና ስራ አስፈሚ ኢንጂነር አዜብ አስናቀ ግድቡ በብዙ መስፈርቶች ተመርጦ ወደ ስራ የተገባ መሆኑን ገልጸው የሀገሪቱንም የሃይል አቅም ወደ 94 በመቶ ያሳድገዋል ብለዋል።

የግድቡ የሲቪል ስራ በሳሊኒ ኮንስትራክሽን የተሳራ ሲሆን የኤሌክትሮ ሜካኒካል ስራው ደግሞ ባቻይናው ዶንግፋንግ ኤልክትሪክ መሰራቱን ጠቁመዋል፡፡

በስራው ላይ ከ32 አገራት የተወጣጡ ሠራተኞች የተሳተፉ ሲሆን ለኢትዮጵያዊያንም ከፍተኛ የዕውቀትና የክህሎት ሽግግር የተገኘበት መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የሳሊኒ ኢምፔርሎጂ ስራ አስኪያጅ  በስራው ላይ የተሳተፉ በሙሉ ጅግኖች ናቸው ካሉ በኋላ በስራው ህልማችንን አሳክተናል ሲሉ አስታውቀዋል፡፡

ግድቡ  ኢትዮጵያ የጀመረችውን የዕድገት ጉዞ ለማስቀጠል ከማገዙም በላይ ፕሮጀክቱ ህብረተሰቡን ለመጥቀም መሰራቱን አስታውቀዋል፡፡

በስራው ወቅት ለአካባቢ ጥበቃ ከፍተኛ ትኩረት መሰጠቱን ስራ አስኪያጁ  አስታውቀዋል፡

የቻይናው አምባሳደር ሊ ፋን በበኩላቸው በመንግስት ቁርጠኝነት አገሪቱ ያስቀመጠችውን ራዕይ ለማሳካት እየሰራች ነው ብለዋል፡፡

የግድቡ ስራ የአገሪቱን የሃይል ፍላጎት ለማማሏት ትልቅ ሚና ከመጫወቱም በላይ ወደ ኢንዱስትሪ ለመሸጋገር በምታደርገው ጥረት ውስጥ ሚናው ትልቅ ነው ብለዋል።

በስራ ላይ እያሉ ህይወታቸው ላለፉ ግለሰቦች የህሊና ጸሎት በማድረግና በአገር ሽማግሌዎች ምርቃት የተጀመረው የግቤ ሶስት የምረቃ ስነስርዓት በስራው ላይ ለተሳተፉ አካላት ሽልማት በመስጠት ተጠናቋል፡፡

ግንባታው በ1998 ዓ.ም የተጀመረውና 1 ሺህ 870 ሜጋ ዋት የሚያመነጨው የጊቤ ሶስት የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ግድብ 40 በመቶ የግንባታ ወጪው በኢትዮጵያ መንግስት፤ ቀሪው 60 በመቶ ከቻይናው ኢንዱስትሪያል ንግድ ባንክ በተገኘ ብድር ተሸፍኗል።

የሲቪል ስራውን የኢጣልያው ኩባንያ ሳሊኒ ኮንስትራክሽን የኤሌክትሮ መካኒካል ስራውን ደግሞ  በቻይናው ዶንግፋንግ ኤሌክትሪክ ኮርፖሬሽን   ተከናውኗል።

ግድቡ  በዓመት 6500 ጌጋ ዋት ሃይል ያመርታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ሪፖርተር:-ወጌኔ አለማየሁ

Leave A Reply

Your email address will not be published.

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

This website uses cookies to improve your experience. We'll assume you're ok with this, but you can opt-out if you wish. Accept Read More

Privacy & Cookies Policy