NEWS

በኤክስፖርት ዘርፍ የሚስተዋሉ ዋና ዋና ማነቆዎችን ለማስወገድ የሚያስችሉ የመፍትሄ አቅጣጫዎች ተቀመጡ

By Admin

February 06, 2017

የብሔራዊ ኤክስፖርት አስተባባሪ ኮሚቴ በኤክስፖርት ዘርፍ የሚስተዋሉ ዋና ዋና ማነቆዎችን ማስወገድ የሚያስችሉ የመፍትሄ አቅጣጫዎችን አስቀመጠ።

የሚኒስትሮች ምክር ቤት እንደገለጸው፥ ኮሚቴው በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ሰብሳቢነት በዘርፉ በሚታዩ ማነቆዎች ዙሪያ ዛሬ ውይይት አካሂዷል።

በዘርፉ የሚታዩ ዋና ዋና ማነቆዎችን ለመፍታት በመንግሥትና ባለኃብቶች በኩል ምን ምን ተግባራት መከናወን እንዳለባቸውም በሰፊ ተመክሮበታል።

በመሆኑም የአቅርቦት፣ የሎጂስቲክስ፣ የፋይናንስና የቅንጅት ችግሮችን ለማስወገድ የሚያስችሉ የመፍትሄ አቅጠጫዎች ተሰጥተዋል።

በዚህ መሰረት በጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ዘርፍ የሚታየውን ከብክለት የጸዳና ጥራት ያለው ጥጥ በምርምር ተደግፎ የሚቀርብበት ሁኔታ እንዲመቻችና የቫት ተመላሽ ለላኪዎች በሰባት ቀናት እንዲከፈላቸው መግባባት ላይ ተደርሷል።

በተጨማሪም ለማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ከሰነድ ጋር የተገናዘበ ገንዘብ (CAD) ጥሬ ዕቃ ሲጠየቅ ያለምንም ገንዘብ ማስያዣ እንዲያስገቡና በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ለተሰማሩ ባለኃብቶች የቅድመ ጭነት አገልግሎት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሚሰጥ ይሆናል።

ኮሚቴው በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን በኢንዱስትሪ ልማት ዕድገት ማነቆ የሆኑ ችግሮችና ተግዳሮቶችን በማስወገድ የተፋጠነ መዋቅራዊ ለውጥ ያመጣሉ ተብለው ቅድሚያ በተሰጠባቸው ዘርፎችም ውይይት ተካሂዷል።

ከእነዚህ መካከል የጥጥ ልማት መስክን ጨምሮ የጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ቅድሚያ ትኩረት የተሰጠው እንደሆነም ተመልክቷል።

ኮሚቴው የአገሪቱን ኤክስፖርት እንቅስቃሴ ለማሳደግ አዲስ በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት በዘርፉ ቀጥተኛ ተሳታፊ ከሆኑ የአገር ውስጥና የውጪ ባለኃብቶች፣ የማህበራት አባላት፣ ዘርፉን ከሚመሩ አስፈፃሚ አካላትና ከተለያዩ የመንግሥት ኃላፊዎች ጋር ነው ውይይቱን ያደረገው።

ምንጭ፦ ኢዜአ