Ethiopiaprosperous
Ethiopian News Ethiopian Daily news, Regarding political and social Issues.

ሲ አይ ኤ በስልኮች እና በቴሌቪዥኖች አማካኝነት የግለሰቦችን ሚስጢር እየሰለለ ነው – ዊኪሊክስ

0 745

Get real time updates directly on you device, subscribe now.

ዊኪሊክስ የአሜሪካው የስለላ ማዕከል (ሲ አይ ኤ) ከስለላ ወሰኑ ያለፈ የግለሰቦችን ሚስጥር በስልካቸው እና በቴሌቪዥናቸው አማካኝነት እየሰለለ መሆኑን አጋለጠ፡፡

ሲ አይ ኤ የእጅ ስልኮች፣ ዘመናዊ ቴሌቪዠኖች እና ተሽከርካሪዎችን ተጠቅሞ የዓለምን ህዝብ እየሰለለ መሆኑን ነው ዊኪሊክስ ይፋ ያደረገው።

ዊኪሊክስ በ943 ጥራዞች አያይዞ ይፋ ባደረጋቸው 7 ሺህ 818 ሰነዶች ሲ አይ ኤ ባለብዙ ተግባር የመረጃ መጥለፊያ መሳሪዎች እንዳሉት አጋልጧል።

በፈረንጆች 2013 ለመጀመሪያ ጊዜ ትልቁ የዓለማችን የኤሌክትሮኒክስ ኩባንያ ሳምሰንግ ኤፍ8000 ሬንጅ ጠፍጣፋ ቴሌቪዥኖችን አስተዋውቆ ነበር።

በፈረንጆች 2014 ሰኔ ወር ላይ ሲ አይ ኤ ከእንግሊዙ የስለላ ድርጅት ኤም አይ ፋይፍ( MI5) ጋር ዊፒንግ ኤንጅል የሚባል እነዚህም የሳምሰንግ ጠፍጣፋ ቴሌቪዥኖች መሰለያ ሶፍትዌር ሰሩ።

ሶፍትዌሩ ከሲ አይ ኤ የመረጃ ማዕከል የኢንተርኔት መረብ ጋር እንዲገናኝ ተደርጎ ነው የተሰራው፡፡

የሳምሰንግ ተለጣፊ ስልኮችም በዊፒንግ ኤንጅል አማካኝነት የባለቤቶቹን የቤተ ውስጥ ሚስጥር በመቅዳት ወደ ሲ አይ ኤ የስለላ የመረጃ ማዕከል ይልካሉ፡፡
ይህም የሚሆነው ቴሌቪዥኑ ሲከፈት የስለላ መሳሪያዎቹ በገመድ አልባ ኔትዎርካቸው አማካኝነት ከሲ አይ ኤ የመረጃ ማዕከል ጋር ይገናኛሉ።

ለዚህም ይረዳ ዘንድ በቴሌቪዥኖች ላይ የተገጠሙ ረቂቅ የድምፅ መቅረጫዎች የሚወራውን ሁሉ ቴሌቪዥኑን በመቆጣጠሪያ የጠፋ በማስመሰል ይቀዳሉ፡፡

በዚህም ሰዎች በቤት ውስጥ የሚያወሩት ሁሉ በሲ አይ ኤ የስለላ መረብ እየተመረመረ ያልፋል ማለት ነው።

የብሪታኒያው የስለላ ተቋምና ሲ አይ ኤ በጋራ ሆነው የአፕል ምርት የሆኑትን የአይፎን ተንቀሳቃሽ ስልኮችንና አይፓዶችን እንዲሁም ጎግልን የሚተገብሩ የስማርት ስልኮችን ሰብሮ የሚገባ አንድሮይድ የማልዌር ሶፍትዌር አበልፅገው ሲሰልሉ ከርመዋል፡፡

ሲ አይ ኤ የአፕል ስልኮችን የሚጠልፉ 14 መተግበሪያዎችንና ማንኛውንም የአንድሮይድ ስልክ የሚጠልፉ 24 ሶፍትዌሮችን ሰርቶ ሲሰልል ቆይቷል።

ሲ አይ ኤ በሰራቸው የመረጃ መጥለፊያ መሳሪያዎች አማካይነት የአይፎን ስልኮች የዋትስአፕ መልዕክቶችን፣ የስልክ የመረጃ ልውውጦችን በመቅዳት ወደ መረጃ ማዕከሉ መላካቸውን ነው ዊኪሊክስ የገለፀው።

ይህ ሲሆን ታዲያ የቴሌቪዥን እና የስማርት ስልክ አምራች ኩባንያዎቹ ሲ አይ ኤ MI5 ሲ በሶፍትዌሮች የደንበኞቻቸውን ሚስጥር ሲሰልሉ የሚያውቁት ምንም ነገር አልነበረም፡፡

በጥቅሉ እስካሁን እያንዳንዷን የዕለት ተዕለት መጠቀሚያ የኤሌክትሮኒክስ ውጤቶችን ሰብሮ ገብቶ ለመሰለል ሲ አይ ኤ ከ1 ሺህ በላይ የኮምፒውተር ቫይረሶችንና የመረጃ መጥለፊያ ሶፍትዌሮችን እንደሰራ በዊኪሊክስ ይፋ የሆኑት መረጃዎች ያሳያሉ።

ሲ አይ ኤ የወደፊት እቅዱ ደግሞ ተሽከርካሪዎችን ከኮምፒውተር መረብ ጋር አገናኝቶ በስለላ መቆጣጠር ሲሆን ለዚህም ጥናት እያደረገ መሆኑን የዊክሊክስ መረጃዎች ይፋ አድርገዋል።

የስለላ ማዕከሉ ይህን ለማድረግ ያሰበው ግለሰቦችን በድብቅ ሰልሎ ከያዘ በኋላ ለመግደል እንዲመቸው ነው ሲሉ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡

አንዳንድ ስማቸው ከሲ አይ ኤ ጋር የተያያዙ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ጉዳዩን እንዳሳሰባቸው ሲገልጹ አፕል እና ሳምሰንግ ያሉት ነገር የለም፡፡

የስለላ መሳሪያዎቹ በአሜሪካ መንግስት ስር ለሚሰሩ የመረጃ ጠላፊ ቡድኖች መዳረሱም ስለላው በሲ አይ ኤ የተቀነባበረ ስለመሆኑ ነው የተነገረው፡፡

ይህን ሁሉ መረጃ ዊኪሊክስ ይፋ ሲያደርግ ታዲያ የሲ አይ ኤው ቃል አቀባይ ጆናታን ሊዩ የመረጃውን ትክክለኛ መሆን አለመሆን ሲጠየቁ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡

ሲ አይ ኤ በስለላ ስራዎቹ በሚቀርቡበት ወቀሳ ከባድ ፈተና ገጥሞታል እየተባለ ነው።

የዊክሊክሱ መስራች ጁሊያን አሳንጄ ከ2012 ጀምሮ በለንደን የኢኳዶር ኤምባሲ ውስጥ በጥገኝነት እንደሚገኝ ይታወቃል።

ምንጭ፡- ቢቢሲ እና ኒውዮርክ ታይምስ

Leave A Reply

Your email address will not be published.

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

This website uses cookies to improve your experience. We'll assume you're ok with this, but you can opt-out if you wish. Accept Read More

Privacy & Cookies Policy