Ethiopiaprosperous
Ethiopian News Ethiopian Daily news, Regarding political and social Issues.

ጃንሆይ እርስዎ ብቻ ሳይሆኑ ኢትዮጵያም እኮ አሟቷል

0 1,124

Get real time updates directly on you device, subscribe now.

በኢትዮጵያ አቆጣጠር 1960 ዎቹ አካባቢ ኢትዮጵያ አገራችን በብዙ ችግሮች በተወጠረችበት ወቅት ጃንሆይ ከልጅነታቸው ጀምሮ አብሮ አደጋቸው ከነበሩት ከራስ እምሩ ኃይለስላሴ ጋር በጃንሆይ ታላቁ ቤተመንግስት አብረው ተቀምጠው ሳለ የጃንሆይ ፊት፣ መልክ፣ አኳኋን አላማራቸውምና “ጃንሆይ ምን ሆነዋል በሰላም ነው? ፊትዎ ጠቁሯል ” አሏቸው። ጃንሆይም ” ጤንነት አይሰማንም አሞናል።” ሲሏቸውራስ እምሩ ኃይለስላሴም እንቅልፍ የነሳቸው ነገር የጃንሆይ ህመም ሳይሆን የአገራቸው የየዕለቱ ሁኔታ ነበርና ” ጃንሆይ እርስዎ ብቻ ሳይሆኑ ኢትዮጵያም እኮ አሟቷል።” ሲሉ ያገሪቷን ችግር ሕመም በጥበብ ነገሯቸው። ይባላል።

አዎን እውነት ነው በዛሬው በዚህ ዘመን ለመሪዎቻችን የሚነግርልን፣ የሚያሳስብልን ትልቅ ሰው አጣን እንጂ ኢትዮጵያ አሟቷል። የኢትዮጵያ ሕመም ደግሞ የሁላችንም ሕመም ነው የኢትዮጵያችን ደስታ ደግሞ የሁላችንም ደስታ ነው። ወደድንም ጠላንም ሕመማችንም ደስታችንም ከአገራችን ጋር፣ ከወገኖቻችን ጋር የተያያዘ ነው። አሁን ግን ኢትዮጵያ ለያውም በችግር ምክንያት ችግር አስገድዷቸው ቆሻሻን ተደግፈው የሚኖሩ ንጹሐን ልጆቿን በቆሻሻ ተቀብረውባት ሞተዋልና ሐዘን ላይ ነን ሕመም ላይ ነን።

አዎን በዓለም ፀባይ ከሐዘን በኋላ መፅናናት አለ። ከሕመም በኋላ ፈውስ አለ። የእኛ ሐዘን ግን የእኛ ሕመም ግን ማቆሚያ ያለው አይመስልም። በተለያዬ ምክንያት በየጊዜው ዜጎች እየሞቱ መሆናቸውን ስናይ በእርግጥም ኢትዮጵያ አሟታል እንላለን። የአንዳችን ሐዘን ለሌላችን ሐዘን ካልሆነ ራስ በራሳችን መተዛዘን ካልቻልን በእርግጥም ኢትዮጵያ ታምማለች።

የሚያፅናና የኃይማኖት መሪ፣ የሚያስተምር ካሕን፣ የሚመክር ሽማግሌ፣ የሚያስታርቅ ትልቅ ሰው አጥታ ኢትዮጵያ ታማለች።ከአገር ቤት እስከ ውጪ ሐገር እየተነካከስን አገር ያልቻለው ፀባያችን በውጪ ሐገርም መሳቂያ እያደረገን መሆኑን ስታዩ፣ ስትመለከቱ በእርግጥም ኢትዮጵያ ታምማለች ትላላችሁ።አዎን ጃንሆይ የራሳቸውን እንጂ የኢትዮጵያን ሕመም አልተረዱምና ነጋሪ አስፈልጓቸዋልና እኛም እንናገራለን። አገራችን አሁን ሕመም፣ ሐዘን ላይ ናት ሕመሟን የሚፈውስ፣ ከሐዘኗ የሚያፅናናት የአገር መሪ፣ የኃይማኖት መሪ፣ ሽማግሌ ትልቅ ሰው ትፈልጋለች።

ኢትዮጵያ ከሕመሟ እንድትፈወስ ካስፈለገ ራስ በራሳችን መባላታችንን፤ መወቃቀሳችንን፤ ዘራፍ ዘራፍ ማለታችንን ትተን በፆም፣ በፀሎት፣ በምህላ መፍትሔ ወዳለው ወደ አምላካችን እንመለስ። ሐዘኑ ለቅሶው ሰቆቃው በቃችሁ ይለን ዘንድ ወደ እርሱ እናመልክት

Kibrom Adhanom Ghebreyesus

Leave A Reply

Your email address will not be published.

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

This website uses cookies to improve your experience. We'll assume you're ok with this, but you can opt-out if you wish. Accept Read More

Privacy & Cookies Policy