NEWS

ሜርክል በሰሜን አፍሪካ ጉብኝታቸው በስደተኞች ዙሪያ መክረዋል

By Admin

March 05, 2017

የጀርመኗ መራሂተ መንግስት አንጌላ ሜርክል የሰሜን አፍሪካ ሃገራትን ሲጎበኙ ህገወጥ ስደተኞችን መከላከል በሚቻልበት ዙሪያ ከሃገራቱ ጋር መክረዋል፡፡

መራሂተ መንግስቷ ባለፈው ሳምንት ወደ ግብፅና ቱኒዚያ ያቀኑበት ዋናው  ምክንያት ሁለት ሚሊዮን ስደተኞች በሀገራቸው ጀርመን እንዲጠለሉ መፍቀዳቸውን ተከትሎ ጫናው እየከበደ በመምጣቱ ነው፡፡

በካይሮ ዩኒቨርሲቲ የዓለም  አቀፍ ግንኙነት ፕሮፌሰር ታሪቅ ፋህማይ እንደገለጹት ስደተኞች በሜዲትራኒያን ባህር  ወደ አውሮፓ ለማቋረጥ በዋናነት ግብፅና ቱኒዚያ ይጠቀማሉ፡፡

ዢንዋ  እንደዘገበው ከሆነ የሜርክል ግብፅና ቱኒዚያ ጉብኝት ወደ  ጀርመንና አውሮፓ የሚገቡትን ስደተኞች ቁጥር ለመቀነስ  ነው፡፡

ሜርኬል የፖለቲካ ዓለመረጋጋት የሚታይባትንና የሁለቱ ሀገራት ጎረቤት የሆነችውን ሊቢያንም ጎብኝተዋል፡፡

በሃገሪቱ ያለውን የፖለቲካ አለመረጋጋትን ተጠቅመው ህገወጥ የሰዎች ዝውውርን ለሚያባብሱትም መፍትሄ በሚበጅለት ዙሪያ መምከራቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡

ሊቢያ  እስካልተረጋጋች ድረስ  በሀገሪቱ  የሚደረገውን ህገወጥ የሰዎች ዝውውር ለማስቆም     እንደማይቻል ሜርክል የተናገሩ ሲሆን ሃገሪቱ እንድትረጋጋም አለምአቀፉ ማህበረሰብ ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ ማቅረባቸውን የዥንዋ ዘገባ ያመለክታል፡፡

መራሂተ መንግስቷ ሽብርተኝነትን በጋራ መዋጋት በሚቻልበት ዙሪያም ከሃገራቱ መሪዎች ጋር በሰፊው ተወያይተዋል፡፡