CURRENT

በባህር ዳር ከተማ የሚገኘው የአባይ ድልድይ እድሳት ሊደረግለት ነው

By Admin

March 11, 2017

በባህር ዳር ከተማ የሚገኘው የአባይ ድልድይ እድሳት ሊደረግለት ነው።

እድሳቱ የሚደረገው በ23 ሚሊየን ብር ሲሆን ወጪውን የሚሸፍነው የኢትዮጵያ መንግስት ነው።

የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ሳምሶን ወንድሙ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንደተናገሩት፥ የድልድዩ ጥገና በሶስት ወራት ውስጥ ይጠናቀቃል።

የድልድዩ ግንባታ የሚከናወነው የከተማዋን የትራፊክ እንቅስቃሴ ጨምሮ ከተለያዩ አካባቢዎች የሚመጡ ተሽከርካሪዎችን ጉዞ በማያደናቅፍ ሁኔታ ነው ብለዋል።

በመሆኑም ከመተማና ከሱዳን አጠቃላይ ከሰሜን ጎንደር የሚነሱ ተሽከርካሪዎች የዱርቤቴ ሻውራ ጎለጎን መስመር፣ ከደሴ፣ ከኮምቦልቻና ከከሚሴ የሚነሱ በኮምቦልቻ መካነ ሰላም መርጦ ለማርያም መስመርን መጠቀም ይችላሉ ብሏል ባለስልጣኑ።

ይህንን አማራጭ መጠቀም የማይችሉ ከባድ ተሽከርካሪዎች ከምሽቱ 3 ሰዓት እስከ ጠዋቱ 12 ሰዓት በድልድዩ ግማሽ ክፍል ያልፋሉ ያሉት የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተሩ፥ የባህር ዳርና አካባቢዋ ተሽከርካሪዎች ከተማ አስተዳደሩ በሚያወጣው ጊዜያዊ ስምሪት እንዲጠቀሙም ጥሪ አቅርበዋል።

በቀጣይ ግን እየጨመረ ያለውን የተሽከርካሪ ቁጥር ከግምት ውስጥ ያስገባ አዲስ ድልድይ ለማስገንባት የመነሻ ዲዛይን እየተከናወነ መሆኑን ባለስልጣኑ አስታውቋል።

በዚህም መሰረት በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ጨረታው የሚወጣ ሲሆን በያዝነው ዓመት መጨረሻ ኮንትራት እንደሚፈረም ተገልጿል።