CURRENT

በኦሮሚያ ክልል 950 ሺ የሚደርሱ ሥራ አጥ ወጣቶችን ወደ የተለያዩ የሥራ መስኮች ለማሠማራት መታቀዱን

By Admin

March 12, 2017

በዘንድሮ የበጀት ዓመት በኦሮሚያ ክልል 950 ሺ የሚደርሱ ሥራ አጥ ወጣቶችን ወደ የተለያዩ  የሥራ መስኮች ለማሠማራት መታቀዱን የኦሮሚያ ወጣቶችና ስፖርት ጉዳይ ቢሮ አስታወቀ ።የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ባህሩ ተክሌ ለዋልታ እንደገለጹት በኦሮሚያ ክልል የሥራ አጥ ወጣቶችን

ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ለመፍታት በክልሉ በሥራ አጥነት ከተለዩት አጠቃላይ 1 ሚሊዮን 200 ሺ ወጣቶች መካከል 950  ሺ የሚሆኑትን ወጣቶች በዘንድሮ ዓመት  በተለያዩ የሥራ መስኮች ለማሠማራት ታቅዷል ።የፌደራል መንግሥት ከመደበው አጠቃላይ 10 ቢሊዮን ብር የተዘዋዋሪ ፈንድ ውስጥ 3ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር የሚሆነው ለኦሮሚያ ክልል መመደቡን የጠቆሙት አቶ ባህሩ የክልሉ መንግሥት ለሥራ ዕድል ፈጠራ ማስፈጸሚያ

በተጨማሪ 1 ቢሊዮን ብር መመደቡን ተናግረዋል ።በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮ የበጀት ዓመት ሥራ አጥ ወጣቶቹን  በግብርና፣ በማኑፋክቸሪንግ ፣ በኮንስትራክሽን፣ በንግድ፣ አገልግሎትና በማዕድን ዘርፎች ለማሠማራት መታቀዱን አቶ ባህሩ አያይዘው ገልጸዋል ።ወጣቶች ተደራጅተው እንዲንቀሳቀሱ በክልሉ ከቀበሌ ጀምሮ ንዑስ  ጣቢያዎችን በማቋቋም  ወጣቶች ስለ አዳዲስ የሥራ ፈጠራ ግንዛቤ እንዲጨብጡ እየተደረገ መሆኑን

የገለጹት አቶ ባህሩ ወጣቶች  ለናሙና የቀረቡላቸውን ፕሮፖዛሎችን በማየት የራሳቸውን እንዲያቀርቡ እየተደረገ ነው ብለዋል ።እንደ አቶ ባህሩ ገለጻ በኦሮሚያ ክልል በምስራቅ ሸዋ አካባቢ ወጣቶችን በማዕድን ዘርፍ በማሠማራት ምርጥ  ተሞክሮ መገኘቱንና በሌሎች የክልሉ ዞኖች ነባራዊ  ሁኔታዎችን በመለየት በተለያዩ  ዘርፎች ለወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር እንቅስቃሴው ቀጥሏል ።በአሮሚያ ክልል ለወጣቶች  የሥራ ዕድል  ትኩረት  በመሥጠት በክልሉ ምክትል ፕሬዚደንት የሚመራ ኮሚቴ ተዋቅሮ የክትትል ሥራዎች  እየተከናወኑ ናቸው