NEWS

በክልሉ ዘንድሮ በየዘርፉ ውጤታማ ስራዎች ተከናውነዋል — ርዕሰ መስተዳድር ገዱ አንዳርጋቸው

By Admin

March 13, 2017

በአማራ ክልል የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራትን ለመፈጸም በተደረገ ጥረት  ውጤታማ ስራዎች መከናወናቸውን  ርዕሰ መስተዳድር ገዱ አንዳርጋቸው ገለጹ።የክልሉ ምክር ቤት ስድስተኛ መደበኛ ጉባኤ የአስፈጻሚው የስድስት ወራት የእቅድ አፈጻጸም ሪፖርት አድምጧል።

ርዕሰ መስተዳድሩ ሪፖርቱን ባቀረቡበት ወቅት እንደገለጹት በተደረገው ርብርብ ባለፈው ዓመት ኢሊኒኖ ባስከተለው ድርቅ ችግር ውስጥ የነበሩ አካባቢዎች ፈጥነው እንዲወጡ ያስቻለ ውጤት ተገኝቷል።በዚህም ባለፈው የመኸር ወቅት ከዋና ዋና ስብሎች ብቻ 93 ነጥብ 3 ሚሊየን ኩንታል ምርት መገኘቱ የስኬቱ ማሳያ አድርገው አቅርበዋል።

ይህም ፈጻሚውና አስፈጻሚው በአንዳንድ የክልሉ አካባቢዎች የተፈጠረው አለመረጋጋት ሳይገድበው በተጠናከረ ሰራዊት ቁመና አበይት ተግባራትን መፈጸም መቻሉን ያሳየበትነው፡፡

ለተገኘው የምርት ውጤትም በቴክኖሎጂ፣ በግብዓትና አዳዲስ አሰራሮች የመጠቀም ልምዱ  እየዳበረ መምጣትና የተስተካከለ የዝናብ ስርጭት መኖር ዋናው እንደሆነ ርዕሰ መስተዳድሩ በሪፖርታቸው ላይ አመልክተዋል፡፡

ይህንን ውጤት  በመስኖና በበልግ ስራዎች ከመድገም ባሻገር በምርቱ ላይ እሴት በመጨመር አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ማድረግ ብሎም የክልሉን ኢንዱስትሪና የአገልግሎት ዘርፉን ለማነቃቃት ማዋል እንደሚገባም አስገንዝበዋል።

በበጋው ወቅት የሚካሄደው የተፈጥሮ ሃብት ልማት በውሃ ሃብት አያያዝ በማጎልበት ለእንስሳት ምርታማነት ማሳደግና ለስራ እድል ፈጠራ ማዋልም እንዲሁ።

ርዕሰ መስተዳደሩ እንዳመለከቱት የአርሶ አደሩን ምርት በአግባቡ ጥቅም ላይ ለማዋልም ከ4ሺህ በላይ መሰረታዊ ህብረት ስራ ማህበራትን አደረጃጀት፣ አቅምና አፈጻጸም የማሳደግ ስራ ተከናውኗል።

የገጠር መሬት አስመልክቶ የሚነሱ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት በተደረገ ጥረት የ1ሺህ 288 ግለሰቦች መሬት በህዝበ ውሳኔ ተጣርቶ ከህገ ወጦች በመንጠቅ ለትክክለኛ ተጠቃሚዎች መሰጠቱንም ጠቅሰዋል።በጣና ሃይቅ ላይ እምቦጭ በተባለው መጤ አረም ከተሸፈነው 24ሺህ ሄክታር ውስጥ አንድ ሺህ 200 ሄክታር በላይ የሚሆነውን መጽዳት ተችሏል።

ከ600ሺህ ኩንታል በላይ ሰሊጥና ቦሎቄ መሰብሰቡን የገለጸው ርዕሰ መስተዳድሩ ከዚህም ውስጥ  ከ448 ሺህ ኩንታል በላይ  ለኢትዮጵያ ምርት ገበያ በማቅረብ የውጭ ምንዛሬ እንዲገኝ  ክልሉ የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ መሆኑን ጠቁመዋል።

በግማሽ ዓመቱ የተፈጠረው አለመረጋገት ሳይገድበው 17 ቢሊየን ብር ካፒታል ላስመዘገቡ ከ1ሺህ በላይ ፕሮጀክቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መሰጠት መቻሉ አበረታች ተግባር ነው ብለዋል።

አምራች ኢንዱስትሪዎችን በክልሉ ለማስፋፋትም በአክስዮን መልክ በመደራጀት የሚካሄደው እንቅስቃሴ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የክልሉ መንግስት ይደግፋል።

የክልሉ ቁልፍ ችግር የሆነውን የስራ አጥነት ችግር ለመፍታት በተካሄደ እንቅስቃሴም በግማሽ ዓመቱ ከ201ሺህ 800 በላይ የከተማና ገጠር ወጣቶች  የስራ እድል መፈጠሩም በሪፖርቱ ላይ ተመልክቷል።

የከተማና ገጠር የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦትን ከ65 ወደ 75 በመቶ በላይ በማሳደግ ከ2 ሚሊዮን የሚበልጥ ህዝብ  ተጠቃሚ ለማድረግ የቀጠለው ርብርብ በጥሩ ደረጃ ላይ እንደሚገኝም ተጠቅሷል።በመንገድ ልማት ላይ  ጨምሮ ዘንድሮ በየዘርፉ የተከናወኑ ውጤታማ ስራዎች መሆናቸውን  በርዕሰ መስተዳድሩ ሪፖርት ተብራርቷል፡፡ምክር ቤቱ ከሰዓት በኋላ ባለው ጊዜ የቋሚ ኮሚቴዎች ሪፖርት ላይ እንደሚወያይ ተመልክቷል፡