POLITICS

ብአዴን በኪራይ ሰብሳቢነት የተጠረጠሩ አመራሮቹ ላይ እርምጃ ወሰደ

By Admin

March 14, 2017

የብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ /ብአዴን/ ማዕከላዊ ኮሚቴ ባደረገው መደበኛ ስብሰባ ባለፉት 6 ወራት በጥልቀት የመታደስ ንቅናቄ እና መደበኛ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራት አፈፃፀምን ከገመገመ በሗላ በኪራይ ሰብሳቢነት በተጠረጠሩ አመራሮቹ ላይ እርምጃ መዉሰዱን አመለከተ፡፡ የብአዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አለምነው መኮነን ከጉባኤዉ መጠናቀቅ በሗላ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ   ከጥልቅ ተሀድሶው በፊት በአንዳንድ አመራሮች ዘንድ የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብና ተግባር ጐልቶ ይታይ ነበር ብለዋል፡፡

በዚህም የተጠረጠሩ 462 ከፍተኛ እና መካከለኛ እንዲሁም 362 የታችኛው አመራሮች ጉዳያቸው በመጣራት ላይ ያለ ሲሆን ከተጠሩት ጉዳዮች ውስጥ በ1ኛው ላይ ከማዕከላዊ ኮሚቴ አባልነቱ እንዲታገድ በሁለተኛው ላይ ከባድ ማስጠንቀቂያ እንዲሰጠው ማዕከላዊ ኮሚቴው ወስኗል፡፡ ከክልል ኃላፊዎች መካከል 16ቱ ከኃላፊነታቸው እንዲነሱ፣ 11ዱ ደግሞ ከደረጃቸው ዝቅ እንዲሉ መደረጋቸዉን ጠቁመዋል፡፡

ብአዴን ባሳለፋቸው ሂደቶች ብዙ ውጤቶችን ያስመዘገበ ቢሆንም ሂደቱ ደረጃ በደረጃ ህዝቡን ከመምራት ብቃት አኳያ የአስተሳሰብ ድክመትና የአፈፃፀም ጉድለት አጋጥሞታል፡፡ በመሆኑም የተሀድሶው ንቅናቄ የአስተሳሰብ ችግሮችን በመፍታት ለሰላም፣ለልማትና ለመልካም አስተዳደር የተመቸ የአመራር አንድነትና መዋቅራዊ ለውጥ ሊያመጣ የሚያስችል እና የህዝቡን መሰረታዊ ጥያቄዎችን በአጭርና በመካከለኛ ጊዜ ለመፍታት ያለመ  ንቅናቄ እንደነበር አስታዉሰዋል፡፡

በዚህም ማዕከላዊ ኮሚቴው የአስተሳሰብ ግልጽነትና የሃሳብ አንድነት በድርጅቱ አመራሮች ዘንድ መምጣቱን እንደገመገመና  ይህ በመሆኑም ድርጅቱ  ህልውናው ተጠናክሮ ህዝብን መምራት በሚያስችል ቁመና ላይ እንዲገኝ የጥልቅ ተሀድሶው ንቅናቄ ትልቅ አቅም ፈጥሮለታል ብለዋል፡፡

በቀጣይ ብአዴን ህዝብ የመምራት ብቃቱ እንዲረጋገጥ ህዝብን የሚጠቅሙ አስተሳሰቦችን መያዝ፣የህዝቡን ጥያቄዎች ለመመለስ መረባረብ ፣ የግብርና  ምርት እንዲያድግ ህዝብን ማነቃነቅ ፣ በከተሞች የአምራች ኢንዱስትሪ መስኮችን ማስፋት ፣ ህዝባዊ አገልግሎትና ዲሞክራሲያዊ  ግንኙነትን ለማጠናከር ድርጅቱ በቀጣይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራም አመልክተዋል፡፡ አቶ አለምነው መኮነን በመግለጫቸው አያይዘውም በአዲስ አበባ በተለምዶ ቆሸ  በሚባለው አካባቢ በመሬት መንሸራተት ምክንያት በተጐዱ ወገኖች  ድርጅታቸዉ የተሰማቸውን ሀዘን  ገልፀው ለቤተሰቦቻቸውና ለዘመዶቻቸው መፅናናትን¨ተመኝተዋል፡፡.walta