NEWS

ዘመናዊ ቴክኖሎጂ ተጠቅመው ሀብት ያፈሩ አርሶ እና ከፊል አርብቶ አደሮች ሽልማት ተበረከተላቸው

By Admin

March 12, 2017

በግብርና ዘርፍ ተሰማርተው ሃብት በማፍራት ወደ ኢንቨስትመንት የተሸጋገሩ ከ550 በላይ አርሶ እና ከፊል አርብቶ አደሮች ተሸለሙ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በአዳማ ከተማ በተከበረው፥ ስምንተኛው ሀገር አቀፍ የአርሶ እና ከፊል አርብቶ አደሮች በዓል ተገኝተው ለሞዴል አርሶ እና ከፊል አርብቶ አደሮች ሽልማት ሰጥተዋል።

ሞዴል አርሶ እና ከፊል አርብቶ አደሮች በግብርናው ዘርፍ ያገኙትን ልምድና እውቀት በተመሳሳይ ዘርፍ ለተሰማሩ እንዲያካፍሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚህ ወቅት ጠይቀዋል።

አርሶና ከፊል አርብቶ አደሮች በግብርና ዘርፍ ባስመዘገቡት የላቀ አፈጻጸም ከቦንድ ጀምሮ እስከ ዘመናዊ ትራክተር ድረስ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።

ለሽልማት የበቁት አርሶና ከፊል አርብቶ አደሮች የራሳቸውንና የቤተሰባቸውን ጉልበት ተጠቅመው የላቀ ውጤት ያስመዘገቡ መሆናቸውንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።

የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን በሚደረገው ጥረትም የበኩላቸውን ድርሻ በመወጣት ግንባር ቀደም መሆናቸውን በተግባር ማረጋገጣቸውን ነው ያመለከቱት።

በቀጣይም የእነርሱን አርዓያ የሚከተሉ አርሶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮች ቁጥር እንዲጨምር በሚደረገው ጥረት የመሪነት ሚና መጫወት እንደሚጠበቅባቸው ነው የገለጹት።

በሃገሪቷ ካሉት 14 ሚሊየን አርሶ አደሮች መካከል 22 በመቶ የሚሆኑትን ለሞዴልነት ማብቃት መቻሉንም ጠቅሰዋል።

በሌላ በኩል የግብርናው ዘርፍ ባለፉት 15 ዓመታት በአማካይ የዘጠኝ በመቶ እድገት በማስመዝገብ ለሃገሪቷ ምጣኔ ሃብታዊ እድገት መሰረት መጣሉን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።

የእርሻና የተፈጥሮ ሃብት ሚኒስትሩ ዶክተር እያሱ አብርሃ በበኩላቸው፥ ግብርናውን ለማዘመን የቴክኖሎጂ ግብዓቶችን በአግባቡ መጠቀም አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል።

ሽልማት የተበረከተላቸው አርሶ እና ከፊል አርብቶ አደሮች በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊየን ብር በላይ ሀብት ማስመዝገብ የቻሉ ናቸው።

በአሁኑ ወቅት በግብርናው ዘርፍ የሞዴል አርሶ አደሮች ቁጥር እያደገ መምጣቱ ነው የተነገረው።

ተሸላሚዎቹ ሜዳሊያን ጨምሮ የታላቁ ህዳሴ ግድብ የሶስት ሺህ ብር ቦንድና ዘመናዊ ትራክተር ተሸልመዋል።

ስምንተኛው የአርሶና ከፊል አርብቶ አደሮች በዓል “በገጠር የስራ እድል በመፍጠር የግብርና ዘርፍ ቴክኖሎጂዎች የስርጸት ማእከል እንዲሆኑ በማድረግ የወጣቶችንና ሴቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንረባረብ” በሚል መሪ ሀሳብ በአዳማ ከተማ ተከብሯል፡፡