DEVELOPMENT

የስራ ቅጥርና የደመወዝ አከፋፈል ከህግ ውጭ በፈጸሙ አካላት ላይ እርምጃ ይወሰዳል

By Admin

March 04, 2017

በመመሪያ የተደገፈ የደመወዝ አከፋፈልን፤ የደረጃ እድገት አሰጣጥን ዝውውር ቅጥርና የመሳሰሉትን ስራዎች ከህግ ውጭ የፈጸሙ አካላት ላይ እርምጃ ይወሰዳል ተባለ።የፐብሊክ ሰርቪስ እና የሰው ሃብት ልማት ሚኒስቴር በሰው ሀብት አያያዝና ህጎች ዙሪያ፥ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እና ከፌደራል መንግስት የሰው ሃብት ልማት ባለሙያዎች እና ሃላፊዎች ጋር በአዳማ ምክክር እያደረገ ነው።በመድረኩ ከአሰራር ጋር ተያይዞ በተለያዩ ተቋማት ላይ ፍተሻ መደረጉ ተገልጿል።በሚኒስቴሩ የኢንስፔክሽን ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ አበበ ሰይፉ እንዳሉት፥ በ2008 ዓ.ም በስልሳ እንዲሁም በ2009 ደግሞ ከሃያ በላይ ተቋማት ላይ ፍተሻ ተደርጓል።የስራ መደቡ ከሚጠይቀው በላይ የሰው ሃይል መመደብ እና ከደረጃ በታች ሰው መቅጠር በተቋማቱ የተለዩ ችግሮች መሆናቸውንም ተናግረዋል።ከዚህ ባለፈም የደመወዝ አከፋፈል መመሪያን አለመከተልና ተመሳሳይ ባልሆኑ ስራዎች ላይ በዝምድና ዝውውር መፈጸምም በችግርነት ተለይተዋል።የተቀመጡ ህጎች ተግባራዊ አለመደረግ፣ የትምህርት ደረጃን ለስራ ፈተና ማዋል እና የሰራተኞች መረጃ አለመገኘትም በፍተሻ ወቅት የተለዩ ችግሮች መሆናቸውን ነው የተናገሩት።በቀጣይም ተቋማት ህጉን በማክበር መስራት እንዳለባቸው በመጥቀስ፥ የማያሰሩ ህጎች ካሉም ጥያቄ በማቅረብ ማስተካከል ይገባል ብለዋል።የፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት ሚኒስትሩ አቶ ታገሰ ጫፎ በበኩላቸው፥ በተቋማት ላይ በሚደረጉ ፍተሻዎችና ምርመራዎች ድርጊቶቹ ከህግ ውጭ እየተፈጸሙ መሆኑን ገልጸዋል።በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ችግር የፈጠሩ እነዚህን አካላትም በህግ ተጠያቂ እንደሚሆኑ አስረድተዋል።ከዚህ ጋር ተያይዞ የሰው ሃብት አስተዳደር ክፍልም የሰነድ ፍተሻዎችን በማድረግ ችግሮችን መከላከል አለበትም ነው ያሉት።በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አካባቢ አፋጣኝ ውሳኔ የሚሹ ጉዳዮች በቦርድ አመራሮች ይፈቱ በሚል የሚስተዋለው መጓተትም፥ በክፍሉ ውሳኔ በመስጠት መፍታት ይገባልም ብለዋል ሚኒስትሩFBC