NEWS

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ከጌዲዮና ከሲዳማ ዞኖች የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር ተወያዩ

By Admin

March 15, 2017

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ከጌዲዮና ከሲዳማ ዞኖች ከተውጣጡ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር ዛሬ ተወያይተዋል፡፡በውይይቱም ህብረተሰቡ የኤሌክትሪክ አቅርቦት እጥረት፣ የሴቶች ጤና ተደራሽነት፣ ለሀገር ውስጥ ባለሃብቶች ስለተሰጠው ትኩረት፣ በሁለቱ ዞኖች አዋሳኝ የድንበር ግጭቶችን ለመፍታት መንግስት እያደረጋ ያለውን ጥረት እና የእንስሳት ሃብት አጠቃቀምን በተመለከተ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥያቄያቸውን አቅርበዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት ምላሽ በይርጋለም የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ፓርክ የሚገነባው የኃይል ማሰራጫ ጣቢያ ከፓርኩ ባሻገር የአካባቢውን የኤሌክትሪክ አቅርቦት ችግር በዘላቂነት ይፈታዋል ነው ያሉት፡፡በሁለቱን ዞኖች የድንበር አዋሳኝ የሚፈጠሩ ግጭቶችን ለመፍታትም ህዝቡ ለዘመናት አብሮ የኖረ በመሆኑ ግጭቶችን በመነጋገር ሊፈታው ይገባል ብለዋል፡፡

ግጭት እንዲፈጠር ምክንያት የሚሆኑ አመራሮች ላይም እርምጃ ይወሰዳል ነው ያሉት፡፡ከሴቶች የጤና አገልግሎት ተደራሽነት አንጻር የአምቡላንስ እጥረት አለብን በሚል ለተነሳው ጥያቄም፥ መንግስት ችግሩን ለመፍታት በአንድ ወረዳ በአማካይ ሁለት አምቡላንስ እየሰጠ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ጠቅሰዋል፡፡

መንግስት ከሚያደርገው ድጋፍ በተጨማሪ ህብረተሰቡ የድርሻውን መወጣት እንዳለበት ጠቅሰው፥ በአማራ ክልል በአንድ ወረዳ ስድስት አምቡላንሶች ያሉ ሲሆን ሁለቱ በመንግስት አራቱ ደግሞ በህብረተሰቡ መሟላታቸውን ነው ለማሳያነት ጠቁመዋል፡፡የገጠር መንገዶችን ከመጠገን ባለፈ የግንባታ ጥራታቸውን ለማሻሻል ስርዓት ተዘርግቶ ይሰራልም ብለዋል፡፡መንግስት በሚገነቡ የተቀናጀ አግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ የሃገር ውስጥ ባለሃብቶች ገብተው እንዲሰሩ እንደሚያበረታትም ገልፀዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሃገር ውስጥ ባለሃብቶችን ለማበረታታት የ80 በመቶ የብድር አቅርቦት የሚያመቻች ሲሆን በኢንዱስትሪ ፓርኮች የሚያስፈልጓቸውን የመሰረተ ልማት ማሟላትና ሌሎች አገልግሎቶችን ያቀርባል ነው ያሉት፡፡

የህብረት ስራ ማህበራት፣ አርሶ አደሮች እና ወጣት ባለሃብቶች በተቀናጀ የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ፓርክ ውስጥ ለመስራት ከአሁኑ መዘጋጀት እንዳለባቸውም ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሳስበዋል፡፡ከዚህ ባለፈም የጊዳቦ ግድብን በመጠቀም በአካባቢው ያለውን የእንስሳት ሃብት በአግባቡ ማልማት እንደሚቻል ተናግረዋል፡፡