Ethiopiaprosperous
Ethiopian News Ethiopian Daily news, Regarding political and social Issues.

ለአማኑኤል የአዕምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ግንባታ ከኮንትራት ውጭ 82 ሚሊየን ብር ተጨማሪ ክፍያ ተፈፅሟል

0 457

Get real time updates directly on you device, subscribe now.

የፌዴራሉ ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት በአዲስ አበባ ኮተቤ አካባቢ የተገነባው የአማኑኤል የአዕምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ከኮንትራት ውል በላይ የ82 ሚሊየን ብር ተጨማሪ ክፍያ መፈጸሙ ከመመሪያ ውጭ ነው በሚል ያቀረበውን ሪፖርት ተከትሎ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ጉዳዩን የሚያጣራ ኮሚቴ አቋቁሚያለሁ ብሏል።

ኮሚቴው በማጣራቱ ሂደት ለችግሩ ምክንያት የሆኑ አካላትን ተጠያቂ የሚያደርግ መሆኑም ነው የተገለጸው።

ከፈዴራሉ ዋና ኦዲት መስሪያ ቤት ያገኘው መረጃ እንደሚያመላክተው በ2002 ዓ.ም የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በአዲስ አበባ ኮተቤ አካባቢ የአማኑኤል የአዕምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የግንባታ ስራ ለማከናወን ከሳንታ ኮንስትራክሽን ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ጋር ውል ፈጽሟል።

በውሉ መሰረት የተጨማሪ ዕሴት ታክስን ጨምሮ 12 ሚሊየን 541 ሺህ 417 ብር ክፍያ ተፈጽሟል።

ይሁንና ሪፖርቱ በግዥ መመሪያው መሰረት ለሆስፒታሉ ተጨማሪ ግንባታ የሚደረግ ከሆነ ከመጀመሪያው ውል ላይ ከሰፈረው መጠን ከ30 በመቶ መብለጥ የሌለበት ቢሆንም ዳግም በተደረገው ውል ላይ ይህን መመሪያ በሚጥስ መልኩ 120 በመቶ ጭማሪ የታየበት ውል በድጋሚ ተፈጽሟል።

ከዚህ በተጨማሪ ግንባታው ከተያዘለት ጊዜ በእጅጉ የተጓተተ መሆኑን በመግለጽ ኦዲት ተደርጎ ችግሩ ከተረጋገጠ በኋላ ክዋኔው ክትትል ተደርጎበት በድጋሚ ለተቋሙ ተልኳል ነው ያሉት የዋናው ኦዲተር የውጭ እና የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ አወቀ ጤናው።

በድጋሚ መላክ ያስፈለገውም በመጀመሪያው ዙር ለቀረበው ሪፖርት የተሰጠው ምላሽ አጥጋቢ ባለመሆኑ ነው ብለዋል።

በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የአማኑኤል ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ፕሮጀክትን የሚያስተዳድረው የመሰረተ ልማት ዳይሬክተር አቶ ታደሰ የማነ፥ የሆስፒታሉ ግንባታ መዘግየትም ሆነ ተጨማሪ 82 ሚሊየን ብር ወጪ የተደረገው ግንባታው ከመጀመሩ በፊት የቅድመ ዝግጅት፣ የመሬት እና የዲዛይን ጥናት ባለማደረጉ መሆኑን ተናግረዋል።

ከመጀመሪያው ውል ላይ ከሰፈረው ከ30 በመቶ የበለጠ ውል መፈፀሙ እና ፕሮጀክቱ የወሰደው ጊዜም የአሰራር ክፍተት እና መመሪያ የመጣስ አሰራር የታየበት ነው ብለዋል ሀላፊው።

ችግሩ በወቅቱ በነበሩ ሃላፊዎች ትዕዛዝ የተፈጠረ መሆኑንም ነው ያነሱት።

በዚህም ተጠያቂ አካላትን የማጣራት ስራ መጀመሩን የተናገሩት አቶ ታደሰ፥ ከሶስት ዳይሬክቶሬት የተዋቀረ አጣሪ ኮሚቴ ተቋቁሟል ብለዋል።

ሆስፒታሉ ዘግይቶ ቢጠናቀቅም የተለያዩ ተጨማሪ የኦፕሬሽን እና የህጻናት ህክምና መስጫ ማስፋፊያዎች ተደርጎለት ከሁለት ሳምንት በፊት የሙከራ ስራ መጀመሩንም ገልፀዋል።

ከእቅድ ውጪ አራት አመት የዘገየው ሆስፒታሉ ለግንባታ ወጪ በአጠቃላይ 156 ሚሊየን ብር ፈጅቷል።

ሆስፒታሉ የተለያዩ ከፍተኛ የቀዶ ጥገና ስራ ማከናወን የሚያስችል ከውጪ ተገዘተው የገቡ ማሽኖች ተተክለውለት ነው የሙከራ ስራውን የጀመረው።

የአማኑኤል የአዕምሮ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በቀጣይ ሁለት ወራት በይፋ ስራውን ይጀምራል ተብሏል።

 

 

 

 

Leave A Reply

Your email address will not be published.

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

This website uses cookies to improve your experience. We'll assume you're ok with this, but you can opt-out if you wish. Accept Read More

Privacy & Cookies Policy