CURRENT

ኢትዮጵያ የ2017 የዓለም ሃይድሮ ፓወር ጉባኤን ታስተናግዳለች

By Admin

April 25, 2017

ኢትዮጵያ የ2017 የዓለም ሃይድሮ ፓወር ጉባኤን በሚቀጥለው ወር ታስተናግዳለች።

ጉባኤው ከግንቦት 1 ቀን 2009 ዓ.ም. ጀምሮ ለሶስት ቀናት “እየተለወጠ በመጣው ዓለም የሃይድሮ ፓወርን ድርሻ ማሳደግ” በሚል መሪ ሀሳብ በአፍሪካ ህብረት መሰብሰቢያ አዳራሽ ይካሄዳል።

ለስድስተኛ ጊዜ የሚካሄደው ስብሰባ በአፍሪካ ሲዘጋጅ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።

የውሃ መስኖና ኤሌትክሪክ ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነትና የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ብዙነህ ቶልቻ ለኢዜአ እንደገለጹት ጉባኤው በዓለም ዓቀፍ ደረጃ የውሃ እና ኤሌክትሪክ ኃይል ሽፋንን ማሳደግ በሚቻልበት ጉዳይ ላይ ያተኩራል።

ሃይድሮ ፓወር በዓለም ዓቀፍ ደረጃ ያለውን ተደራሽነት በማስፋት ለዘላቂ ልማት ግቦች አስተዋጽኦ በሚያደርግበት ሁኔታ ላይ ምክክር እንደሚካሄድም ነው የገለጹት።

ሃይድሮ ፓወር ወደፊት የሚኖረው ሚና ምንድነው?፣ የውሃ ሃብት አጠቃቀም፣ የአየር ንብረት ለውጥና ሃይድሮ ፓወር እንዲሁም ዘርፉ ለዘላቂ ልማት ግቦች በምን አይነት መልኩ አስተዋጽኦ ያደርጋል? በሚሉ አጀንዳዎች ላይ ውይይት እንደሚደረግ ተናግረዋል።

“ኢትዮጵያ በሃይድሮ ፓወር ዘርፍ እያሳየች ያለችው እድገት” ጉባኤውን ለማስተናገድ ተመራጭ አገር እንዳደረጋት ነው አቶ ብዙነህ ያስረዱት።

ኢትዮጵያ በሃይድሮ ፓወር ዘርፍ ያላትን ተሞክሮ በጉባኤው ላይ እንደምታቀርብም ጠቁመዋል።

ጉባኤው አገሪቷ በዘርፉ የደረሰችበትን ደረጃ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለማሳየትና በዘርፉ የተሰማሩ አገር በቀል ፋብሪካዎች ከዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ጋር የልምምድ ልውውጥ ለማድረግ ምቹ አጋጣሚ እንደሚፈጥር ገልጸዋል።

ከተለያዩ አገራት የሚመጡ እንግዶችን ለማስተናገድና ጉባኤውን የተሳካ ለማድረግ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱን ጨምሮ የተለያዩ አህጉራዊና ዓለም ዓቀፋዊ ድርጅቶችን ያካተተ የጋራ ኮሚቴ መቋቋሙንም ነው ያብራሩት።

በጉባኤው ሚኒስትሮች፣ ዓለም ዓቀፍ የፋይናንስ ተቋማት፣ የሲቪክ ማህበራት፣ በዘርፉ የተሰማሩ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎችና ሌሎች የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ይሳተፋሉ ተብሎ ይጠበቃል።

የ2017 የዓለም ሃይድሮ ፓወር ጉባኤ ዓለም አቀፉ የሃይድሮ ፓወር ማህበር፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽንና የውሃ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስቴር በጋራ ያዘጋጁታል።

የመጀመሪያው ዓለም ዓቀፍ የሃይድሮ ፓወር ጉባኤ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2007 በቱርክ አንታሊያ የተካሄደ ሲሆን አምስተኛው ጉባኤ በቻይና ርዕሰ መዲና ቤጂንግ ከሁለት ዓመት በፊት መካሄዱ ይታወሳል።

ዓለም አቀፉ የሃይድሮ ፓወር ጉባኤ በየሁለት ዓመቱ የሚካሄድ ነው።