የኮንስትራክሸን ሚኒስቴር አሰራሩን ባለማስተካከሉ ተገልጋዮች መብታቸውን በገንዘብ መግዛት ቀጥለዋል

By Admin

April 26, 2017

የኮንስትራክሸን ሚኒስቴር ህገ ወጥነትን ከሚያስቀረው ይልቅ ህገ ወጥነትን ከሚያስቀጥል አሰራር ጋር በመቀጠሉ ተገልጋዮች መብታቸውን በገንዘብ መግዛት ቀጥለዋል።

ሚኒስቴሩ በደላላዎች የተወረረውን ተቋም ለማፅዳት እርምጃ ወስድኩ ካለ አራት ወራት ተቆጥረዋል። ይሁን እንጂ አሁንም ተቋሙ ከደላሎች አልፀዳም።

ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ባደረገው ቅኝት በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አካባቢ የስራ ተቋራጮችን እርስ በእርስ እናገናኛለን የሚል ፅሁፍ ያረፈበት፤ በስውር ባለጉዳይ በነፃ ማግኘት የሚገባውን አገልግሎት በገንዘብ እንዲያገኝ የሚያደርጉ ደላሎች ህገ ወጥ ስራቸውን ሲያከናውኑ ተመልክቷል።

ተገልጋዮች በእጅ ካልሄዱ በስተቀር አገልግሎት ማግኘት ያልተቻለበት ሲሉ የተማረሩበት ህገ ወጥ አሰራር በተለይ በሞያ ምዝገባና ፍቃድ አሰጣጥ ስርዓቱ ላይ በጉልህ ይታያል።

ያለቀጠሮና ያለ መንገላታት አገልግሎት ለማግኘት በሚል በሚኒስቴሩ በር ላይ በሚደረደሩ ደላሎች መበዝበዝም ከአሰራሩ የመነጨ ክፍተት መሆኑን ቀደም ሲል በሰራናቸው ዘገባዎች ማሳየታችን ይታወሳል።

በእርግጥ ደላሎቹ ስራውን የሚሰሩት ከተቋሙ ሰራተኞች ጋር ለመሆኑም ራሳቸው ምስክር ናቸው።

ለማይሰሩ የግንባታ መሳሪያዎች ብቃት መስጠት፣ አንድ ባለሞያ ለተለያየ ተቋራጭ በተመሳሳይ ጊዜ ቅጥር መፈጸምና በባለሙያው ፍቃድ ሞያ የሌለው ሰው በስራው ላይ መሰማራት ከሚፈጸሙ ህገ ወጥ ድርጊቶች ውስጥ ተጠቃሽ ናቸው።

ይህ ደግሞ በግንባታ ጥራት መጓደልና በጊዜ አለመጠናቀቅ ላይ አሉታዊ ተጽእኖ እንደሚፈጥር ይታወቃል።

ሚኒስቴሩ ይህንን ችግር ለመቅረፍ ከሰው ንክኪ የራቀ በኮምፒውተር የታገዘ ዘመናዊ ስርዓት ለመዘርጋት ዝግጅት ማጠናቀቁን ከስድስት ወራት በፊት ገልፆ ነበር።

ቴክኖሎጂው አገልግሎት ፈላጊዎች ባሉበት ሆነው በሚኒስቴሩ ድረ ገጽ ተራ የሚይዙበትና የራሳቸውን የይለፍ ቁጥር በመያዝ አገልግሎቱን ማግኘት የሚችሉበትን ቀን በዚያው አውቀው እንዲመጡ የሚያስችላቸው አሰራር ሲሆን፥ ተደጋጋሚ ምዝገባና ፍቃድ የሚያወጡ ባለሞያዎችንም ይገድባል።

ከስድስት ወራት በፊት ይህንን ያለው ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ዝግጅቱ ተጠናቆለታል የተባለለት ቴክኖሎጂው በዚህም አመት ተግባራዊ መሆን እንደማይችል ይፋ አድርጓል።

በሚኒስቴሩ የኮንስትራክሽን ባለሞያዎች ብቃት ማረጋገጥና ምዝገባ ዳይሬክተር አቶ ቴዎድሮስ ተገኝ፥ ከስድስት ወር በፊት ዝግጅቱ ተጠናቆለታል የተባለው ዘመናዊ አሰራር አስፈላጊ ቆሳቁሶቹ አልተገዙለትም ብለዋል።

ግዢውም ስምንት ወራትን የሚፈልግ በመሆኑ ተግባራዊ ሊሆን የሚችለው በሚቀጥለው አመት አጋማሽ ላይ ነው የሚል ሀሳብ ሰንዝረዋል።

ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በአንድ ጉዳይ ከሰጠው ሁለት የተምታታ ሃሳብ ሁለት ነገሮች ይመዘዛሉ።

ሚኒስቴሩ ህገ ወጥ አሰራርን ከሚያስቀረው አሰራር ይልቅ ህገ ወጥነት የቀጠለበትን አሰራር ቀጥሏል።

ባለጉዳዮችም መብት የሆነ አገልግሎትን በገንዘብ ከማግኘት አልተላቀቁም።fbc