NEWS

ህብረቱ ዶ/ር ቴድሮስ በመመረጣቸው የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላለፈ

By Admin

May 24, 2017

የአፍሪካ ህብረት ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም የመጀመሪያው አፍሪካዊ የዓለም የጤና ድርጅት ዳይሬክተር ጀነራል ሆነው በመመረጣቸው የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፏል።

የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሙሳ ፋቂ ማሃመት ለዶክተር ቴድሮስ ባስተላለፉት መልእክት፥ “ከአፍሪካ አህጉር የወጣ የመጀመሪያው የዓለም የጤና ድርጀት ዳይሬክተር ጀነራል በመሆን በመመረጥዎ እንኳስ ደስ አለዎት” ብለዋል።

“የዓለም ሀገራት ለዓለም ጤና ድርጅ ዳይሬክተር ጀነራልነት የሚመጥን ትክክለኛውን ሰው ነው የመረጡት” ሲሉም ተናግረዋል።

ዶክተር ቴድሮስ የዓለም የጤና ድርጅትን በሚመሩበት ጊዜም ጤናማ ዓለምን ለመፍጠር የሚሰሩት ስራ የተሳካ እንዲሆንላቸው መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።

ሊቀመንበሩ ለዶክተር ቴድሮስ ሙሉ ድጋፋቸውን ለሰጡ የአፍሪካ ሀገራት የጤና ሚኒስትሮችም ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

“አፍሪካ በአንድ ድምጽ ስትናገር ሁሌም ታሸንፋለች” ነው ያሉት ሙሳ ፋቂ ማሃመት።

ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም የዓለም ጤና ድርጅት ዳይሬክተር ጀነራል ለመሆን በእጩነት በቀረቡበት ወቅት የአፍሪካ ህብረት ሙሉ ድጋፍ መስጠቱ ይታወሳል።

ትናንት በስዊዘርላንድ ጄኔቫ በተካሄደው ምርጫ ኢትዮጵያ እጩ አደርጋ ያቀረበቻቸው ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም የአብላጫ አገራትን ድምፅ በማግኘት መመረጣቸው አይዘነጋም።

133 አገራት ድምፃቸውን ለዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም የሰጡ ሲሆን፥ ለሌላኛው ተቀናቃኛቸው ዴቪድ ናባሮ የ50 ሀገራትን ድምፅ አግኝተዋል።

ዶክተር ቴድሮስ ለጉባኤው ባቀረቡት ንግግር ዛሬ በዓለም ለሰው ልጅ ጤና ፈተና ከሆኑት ኢቦላ ጀምሮ እስከ ዘመን አመጣሹ ውፍረት ድረስ ያላቸውን መፍትሄ አስቀምጠዋል።

የዓለም ጤና ድርጀትን ጊዜው የሚፈልገው ዓለም አቀፋዊ ተቋም እንደሚያደርጉም ቃል ገብተዋል።