NEWS

በአማራ ክልል የሙስና ወንጀል የፈጸሙ 211 ግለሰቦች ተቀጡ

By Admin

May 12, 2017

በህዝብና በመንግስት ሃብትና ንብረት ላይ ሙስና ፈጽመዋል ያላቸውን 211 ግለሰቦች በፅኑ እስራትና በገንዘብ እንዲቀጡ ማድረጉን የአማራ ክልል የስነ-ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን አስታወቀ።

የኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነር አቶ እውነቴ አለነ እንደገለጹት ግለሰቦቹ የተቀጡት ባለፉት ዘጠኝ ወራት በተደረገ ጠንካራ የክትትልና የቁጥጥር ስራ ጥፋተኛ ሆነው በመገኘታቸው ነው።

በ121 መዝገቦች ክስ ተመስርቶባቸው ተገቢውን ማስረጃ በማሰባሰብ ቅጣቱ የተወሰነባቸው 182 ወንድና 29 ሴቶች መሆናቸውንም ተናግረዋል።

ግለሰቦቹ በተመሰረተባቸው በስልጣን ያለ አግባብ መጠቀም፣ በግዢና ጨረታ ሙስና፣ በተጭበረበረ ሰነድ መገልገል፣ በግብር መሰወርና መሰል የወንጀል ክስ ጥፋተኛ ሆነው መገኘታቸውንም አስረድተዋል።

ግለሰቦቹ በፈፀሙት ወንጀል ጥፋተኛ ሆነው በመገኘታቸውም ከሦስት ወር አስከ 14 ዓመት የሚደርስ ፅኑ እስራትና ከ300 እስከ 30 ሺህ ብር የሚደርስ የገንዘብ ቅጣት የተጣለባቸው መሆኑን ገልፀዋል።

በእጃቸው የተገኘና የሙስና ፍሬ የሆነ ከ14 ነጥብ 1 ሚሊየን ብር የሚበልጥ ገንዘብና 1 ሺህ 400 ካሬ ሜትር ቦታም ለመንግስት ገቢ መደረጉን አስታውቀዋል።

ከዚሁ ጎን ለጎን በተሰራ የአስቸኳይ የቅድመ ሙስና መከላከል ተግባርም በጨረታ፣ በእቃ ግዢ፣ በምግብ ዋስትናና በሌሎች እንቅስቃሴዎች ሙስና ሊፈፀምበት የነበረ 18 ሚሊየን ብር ማስቀረት እንደተቻለ አብራርተዋል ።

ለሙስና በተጋለጡ የከተማ መሬት፣ የንብረት ግዢና ጨረታ፣ የግንባታ፣ የግብር አሰባሰብና አወሳሰን፣በሰነድና መሰል ተግባራት ዙሪያ በተለየ ትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝም ማብራራታቸውን የኢዜአ ዘገባ ያሳያል።