NEWS

በአዳማ ከተማ ከሙስና ጋር ተያይዞ የማስተካከያ እርምጃ እየተወሰደ ነው

By Admin

May 23, 2017

የአዳማ ከተማ አስተዳደር  ከጥልቅ ተሃድሶው ወዲህ ከሙስናና ከኪራይ ሰብሳቢነት ጋር ተያይዞ  የማስተካከያ እርምጃዎች እየወሰደ መሆኑን ገለጸ፡፡

በህገ -ወጥ መንገድ ተዘርፎ የነበረው ሀብት እንዲመለስና በርካታ ኪራይ ሰብሳቢዎች ከነተባባሪያቸው መያዛቸውም ተመልክቷል፡፡

የአዳማ ከተማ አስተዳደር ማዘጋጃ ቤት ስራ አስኪያጅ አቶ ጁንዲ ዓሊይ ለኢዜአ እንደገለፁት በጥልቅ ተሃድሶው የሙስናና የኪራይ ሰብሳቢነት ምንጮችን በመለየት በተወሰዱት የማስተካከያ እርምጃዎች አመርቂ ውጤት ተገኝቶበታል ።

ከጥቅም ጋር በተያያዘ መንገድ የመንግስትና የህዝብ ሀብት የሆነውን መሬት አለአግባብ የሰጡ መሀንዲሶችና በህገ ወጥ መንገድ መሬት የዘረፉ ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው እየተጣራ ነው ብለዋል ።

በከተማዋ  የኢንቨስትመንት ፈቃድ አውጥተው መሬት ከወሰዱት 538 ባለሃብቶች መካከል ህጋዊ ሆነው የተገኙት ጥቂቶቹ ብቻ መሆናቸውን ስራ አስኪያጁ ገልፀው በ200ዎቹ ላይ በተደረገው የማጣራት ስራ በህገ ወጥ መንገድ ተወስዶ የተገኘ ከ100 ሔክታር በላይ  መሬት  ወደ መሬት ባንክ ገቢ እንዲሆን ተደርጓል

በቀበሌና በኪራይ ቤቶች ስር የሚገኙት የመንግስት ቤቶች የኪራይ ሰብሳቢነት ምንጮች ሆነው መቆየታቸውን ከንቲባው ገልፀው  ቤቶችን  አለአግባብ ለሶስተኛ ወገን ሲያስተላልፉ የነበሩ ለግል ጥቅማቸው ያዋሉ ባለሙያዎችና የስራ ሃላፊዎች በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ተደርጓል ።

አለአግባብ ተይዘው የነበሩ 70 የኪራይ ቤቶች ወደ መንግስት እንዲመለሱ 70 የቀበሌ ቤቶች ደግሞ ለእቅመ ደካሞችና በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች እንዲተላለፉ መደረጉን ስራ አስኪያጁ ተናግረዋል ።

ከኪራይ ሰብሳቢነት ጋር ተያይዞ በህገወጥ ንግድ ላይ ተሰማርተው የነበሩ 4 ሺህ ነጋዴዎች በመለየት ወደ ህጋዊነት እንዲመጡ መደረጉ ጥልቅ ተሃድሶው ያመጣው ውጤት ነው ተብሏል፡፡

በአዳማ ከተማ ከኪራይ ሰብሳቢነትና ከሙስና ጋር ተያይዞ ያለ ቅጥ የተስፋፋው ህገ ወጥ ግንባታ ለማስተካከል የማፍረስ እርምጃ እየተወሰደ ሲሆን በኩሸነን በተባለው አንድ ቀበሌ ብቻ 1ሺህ 400 ቤቶች እንዲፈርሱ ተደርጓል።

በአዳማ ከተማ ቀበሌ 05 ተሰራ የተባለው ድልድይ በመጥፋቱ የግንባታው ህንፃ ተቋራጭና ተቆጣጣሪ መሀንዲሶች በቁጥጥር ስር ውለዋል ።

ከኪራይ ቤቶችና ከቀበሌ ቤቶች ጋር ተያይዞ በተፈፀመው ሙስና ብቻ 34 ሰዎች በቁጥጥር ስር ሲውሉ በኮንስትራክሽን ፣ በህገወጥ ካርታና ፕላን እደላ ። በመሬት ወረራና አሻሻጭነት የተሳተፉ በርካታ መሃንዲሶች ፣ የስራ ሃላፊዎች ፣ ደላሎችና የህንፃ ተቋራጨች በቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በህግ እየታየ መሆኑን ከስራ አስኪያጁ ገለፃ ለማወቅ ተችሏል።

በከተማዋ የቀበሌ 06 ነዋሪ አቶ ፈይሳ መገርሳ በሰጡት አስተያየት በሙስና የተገኘ ገንዘብ ለልማት የማይውልና ድሆችን ለከፋ ችግር የሚያጋልጥ በመሆኑ ከመንግስት ጎን ሆነን መረጃ በማቅረብና ጥቆማ በመስጠት ተጨማሪ ጉልበት እንሆናለን ብለዋል፡፡

በአዳማ ከተማ የተጀመረው የፀረ ሙስናና ፀረ ኪራይ ሰብሳቢነት ትግል ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የከተማዋ ኮሙኒኬሽን ጉዳይ ፅህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሜኤሳ ኤሌማ ገልፀዋል።