Artcles

ኢትዮጵያ—ትኩረት እየሳበች ያለች አገር

By Admin

May 02, 2017

ኢትዮጵያ—ትኩረት እየሳበች ያለች አገር/  ዳዊት ምትኩ/

    ኢትዮጵያ ውስጥ የማይመጣ አገር፣ ከአገራችን ጋር አብሮ ለመስራት የማይሻ የውጭ ኩባንያና በጋራ ተጠቃሚነት እጅ ለእጅ ተያይዞ ለማደግ የማይሻ የለም ቢባል ከእውነታው መራቅ አይሆንም። አሜሪካ፣ ቻይና፣ ቱርክ፣ እንግሊዝ፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ የተባበሩት አረብ ኢምሬትስ…ወዘተ. አገራት ከኢትዮጵያ ጋር የሚያደርጉት የሁለትዮሽ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ተጠቃሽ ነው። ዓለም አቀፍ ታላላቅ ኩባንያዎችም እዚህ አገር ውስጥ ሰርተው ራሳቸው ተጠቃሚ ሆነው ሀገሪቱንም ለመጥቀም እየሰሩ ነው። እውነቱን ለመናገር አፍሪካ ውስጥ እንደ ኢትዮጵያ የአገራትንና የታታላቅ ኩባንያዎችን ትኩረት የሳበ አገር አለ ብሎ መናገር የሚቻል አይመስለኝም።

ታዲያ የአገራችን ትኩረት ሳቢነት እንዲሁ የተገኘ አይደለም። ላለፉት 26 ዓመታት ኢትዮጵያ በተከተለችው የውጭ ግንኙነት ፖሊሲና ባከናወነችው ጠንካራ ዲፕሎማሲ መሆኑ አይካድም። እንደሚታወቀው የኢፌዴሪ ህገ- መንግሥት የአካባቢውንና ጎረቤት ሀገሮችን ለጋራ ጥቅምና ሠላም እንዲሰሩ የሚጋብዝ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ መሰረት ጥሏል፡፡ ይህ እንደ ቀድሞዎቹ የውጭ ጉዳይና የደህንነት ፖሊሲዎች የሀገር ውስጥ ጉዳዮችን ቸል በማለትና ወደ ውጭ ያነጣጠረ ሳይሆን፤ በቅድሚያ በሀገር ውስጥ ሠላም በማስፈን በማረጋጋት ላይ ትኩረት በማድረግ  በአካባቢያችን ብሎም በዓለም አቀፍ ደረጃ ዘላቂና አስተማማኝ ሠላም እንዲፈጠርና የጋራ ልማትና ትብብር እንዲጠናከር ማድረግ ነው፡፡  

የውጭ ጉዳይና የሀገራዊ ደህንነት ፖሊሲና ስትራቴጂ ብሔራዊ ጥቅማችንን የማስጠበቅና ሀገራዊ ህልውናችንን የማረጋገጥ ተልዕኮ አለው፡፡ ፖሊሲውና ስትራቴጂው እንደሚያመለክተው ከማንኛውም ሀገር ጋር የሚኖረን ግንኙነት በመሰረታዊ ሀገራዊ ጥቅማችን ደህንነት ላይ የተመሰረተ፣ እንዲሁም የልማትና የዴሞክራሲ ሂደቱ ስር እየሰደደና የሀገራችን ዕድገት እየተፋጠነ በሄደ ቁጥር ለአደጋ ተጋላጭነታችን በከፍተኛ ደረጃ እንደሚቀንስ ያረጋግጣል፡፡

ደህንነታችንን ለማስጠበቅ ዋናው መሣሪያ ልማትና ዴሞክራሲን በሀገር ደረጃ ማረጋገጥ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በዚህ ረገድ ተመስርቶም ዲፕሎማሲያችን በቂ ጥናት በማካሄድ አደጋዎችን ለመቀነስ፣ ግጭቶች ሲፈጠሩ በድርድር እንዲፈቱ ለማድረግ፣ በዚህ ሂደት ሊፈቱ ያልቻሉትን ለመከላከል አቅም መገንባት ተተኪ የሌለው ሚና እንደሚጫወት የውጭ ጉዳይና የደህንነት ፖሊሲና ስትራቴጂው ላይ በግልጽ ተቀምጧል፡፡

የፖሊሲውና የስትራቴጂው አንዱ የትኩረት አቅጣጫ የፖለቲካ ዲፕሎማሲ ነው። በዚህ ስራም ኢትዮጵያ ከተለያዩ ሀገራትና ተቋማት ጋር የምታደርጋቸው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገና እየጎለበተ መጥቷል፡፡ ልማታዊ ዲፕሎማሲውም ተጠናክሯል፡፡ በሰጥቶ መቀበል መርህ ከልዩ ልዩ ሀገሮች ጋር ግንኙነቷን በማጠናከርም በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ የኢንቨስትመንት ፍሰትና ሚዛናዊ የንግድ ትስስር እንዲጨምር እየሰራች ነው፡፡

የሀገሪቱን የውጭ ግንኙነትና በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን ስፍራ ለማጎልበትም ባለፉት 26 ዓመታት ሰፊ ጥረት ተደርጓል፡፡ በዚህም ኢትዮጵያ ለሀገሪቱም ሆነ ለአካባቢው የተረጋጋ የፖለቲካ ሂደት እንዲኖር ግጭቶችና ውዝግቦች በሰላማዊ ጥረት እንዲፈቱ ብቻ ሳይሆን የሠላምና የትብብር አድማሱ እንዲሰፋ እያደረገች ትገኛለች፡፡ በምትከተለው በዚህ የትብብርና የሠላም ዲፕሎማሲ መርህ መሰረትም በዓለም ዙሪያ ካሉት ሀገሮች ጋር ያላት ግንኙነት በጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ ነው፡፡

የፖሊሲው ለሌላኛው ስኬት በሰላም ማስከበር ላይ ያተኮረ ነው። እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ሠላም የማስከበር ተልዕኮ በአህጉር አቀፍ ደረጃ ረዥም ዓመታትን ያስቆጠረ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከአፍሪካ አልፋ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሰላም ለማስከበር ባላት ቁርጠኝነት በተባበሩት መንግስታት ተመርጣ ሠራዊቷን በማሰማራት ቁርጠኝነቷን አሳይታለች፡፡

ፖሊሲው ኢንቨስትመንትን በመሳበ ረገድም ጉልህ ሚና ተጫውቷል። ላችንም እንደምናውቀው አንድ ሀገር ለኢንቨስትመንት አመቺ ናት ለማለት በርካታ ሁኔታዎች ከግምት ውስጥ ይገባሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ሠላምና የተረጋጋ ፖለቲካ፣ የተረጋጋና እያደገ የሚሄድ ኢኮኖሚ፣ የዳበረ የመሰረተ ልማት አውታር፣ ሰፊ የገበያ ዕድል፣ በቂ የሰለጠነና ውጤታማ የሆነ ሰው ኃይል እንዲሁም ኢንቨስትመንትን የሚያሳካ ፖሊሲና ሰፊ የተፈጥሮ ሀብት መኖሩ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ከዚህ አኳያ ሀገራችን ውስጥ ሠላምና የፖለቲካ መረጋጋት በአስተማማኝ ሁኔታ መኖሩ፣ ኢኮኖሚው የተረጋጋና ፈጣን ዕድገት ማሳየቱ እንዲሁም በዝቅተኛ ደረጃ ላይ የነበረው የመሠረተ ልማት አውታር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገና እየተስፋፋ መምጣቱ ሀገሪቱ ለኢንቨስትመንት ምቹ መሆኗን ያሳያል፡፡ እነዚህ ድምር እውነታዎች ሀገራችንን በሁሉም መስኮች ትኩረት እንድትስብ አድርገዋታል፡፡ ሆኖም ይህን ትኩረት ያገኘችው በሀገር ቤት ውስጥ ባከናወነችው ስራዎች መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ አበቃሁ፡፡

 ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲው መስክ በአፍሪካ ብቻ ሳይሆን በአለም አቀፍ መድረኮች ትኩረት እየሳበች ያለች መሆኗን ማጉላትና የትኛዋ አፍሪካዊት አገር ናት እንደ ኢትዮጵያ የውጭ መሪዎችን ትኩረት የሳበችው? የሚል አጀንዳ ፈጥሮ መሥራት