Ethiopiaprosperous
Ethiopian News Ethiopian Daily news, Regarding political and social Issues.

የህብረተሰቡን ጤና፣ ስነ-ልቦና፣ ወግና ባህል ከማስጠበቅ አንፃር የማስታወቂያ ስራን ሊቆጣጠር የሚችል ረቂቅ ፖሊሲና ስትራቴጂ ተዘጋጀ።

0 709

Get real time updates directly on you device, subscribe now.

የህብረተሰቡን ጤና፣ ስነ-ልቦና፣ ወግና ባህል ከማስጠበቅ አንፃር የማስታወቂያ ስራን ሊቆጣጠር የሚችል ረቂቅ ፖሊሲና ስትራቴጂ ተዘጋጀ።

ረቂቁ በአገሪቱ ክትትልና ድጋፍ አልባ የሚባለውን የማስታወቂያ ስራ የሚያስተካክል ነው ተብሏል።

በኢፌዴሪ መንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት በተዘጋጀው ረቂቅ ላይ ከማስታወቂያ ስራ ድርጅቶች፣ ከመገናኛ ብዙሃንና ከማስታወቂያ አሰሪዎች ጋር ውይይት ተደርጓል።

የጽህፈት ቤቱ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ዛዲግ አብርሃ እንዳሉት የማስታወቂያ አዋጅ በ2004 ቢወጣም የዘርፉን አጠቃላይ አቅጣጫ የሚያመላክት ፖሊሲ ባለመኖሩ የዘርፉ ዕድገት በሚፈለገው መልኩ መጓዝ አልቻለም።

ዘርፉ ምቹ ሁኔታ ከተፈጠረለት ብዙዎችን የሚቀጥርና ከፍተኛ መዋዕለ-ነዋይ የሚያንቀሳቅስ ምርታማ ኢንዱስትሪ መሆን የሚችል ነው ብለዋል።

ይህ ካልሆነና አሁን ባለበት ከቀጠለ ተጠያቂነትን ማዕከል ያላደረጉና ፍትሃዊ ያልሆኑ ሂደቶች ተበራክተው በማህበረሰቡና በመገናኛ ብዙሃን ላይ የሚያሳድሩት ተፅዕኖ ከባድ መሆኑን ገልፀዋል።

እየተሰሩ ያሉ ማስታወቂያዎች የህብረተሰቡን ጤና፣ ወግና ባህል፣ ብሄር፣ ፆታና ሃይማኖት ያለገናዘቡ ከመሆናቸው በተጨማሪ በማዕከላዊነት የማይመሩና ፍትሃዊነት የጎደላቸው በመሆናቸው ይህን ረቂቅ ማዘጋጀት አስፈልጓል ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው።

አስተያየት ሰጪዎችም በአገሪቱ መገናኛ ብዙሃን የሚቀርቡ ማስታወቂያዎች ስነ-ምግባርን ያልተከተሉ፣ የህፃናትና ወጣቶችን አመለካከት በአሉታዊ የሚበርዙ፣ የመገናኛ ብዙሃን ይዘት ላይ ተፅዕኖ የሚፈጥሩ ናቸው ሲሉ ገልፀዋል።

ከዚህ በተጨማሪ አልኮል መጠጣትን የሚያበረታቱ፣ ስነ-ልቦናን የሚጎዱ፣ ከእውነታ የራቁ፣ ግነት የበዛባቸው፣ ከአገሪቱ ባህልና ወግ ጋር የማይሄዱ ናቸው ሲሉም አክለዋል።

በተጨማሪም ዘርፉን ከማሳደግና ህዝቡን ማስታወቂያ እንዲያገኝ ከመስራት ይልቅ “የአገሪቱን ታሪክና እሴት ያለአግባብ በመጠቀም ለራሳቸው የግል ጥቅም የሚያውሉ ናቸው” ይላሉ ።

የሰንደቅ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ አቶ ፍሬው አበበ “የዘገየ ቢሆንም ጥያቄያችን መሰረት ተደርጎ ረቂቁ በመዘጋጀቱ ደስ ብሎኛል፤ ቶሎ ወደ ስራ መግባቱ ልማዳዊ የሆነውን የማስታወቂያ ስራ የሚለውጥ ነው” ብለዋል።

ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትን የወከሉት አቶ አሸናፊ ጅማ በበኩላቸው በሌላ አገር ማስታወቂያ ከመሰራጨቱ በፊት የስነ ልቦና፣ የጤናና የማስታወቂያ ባለሙያዎች ቅድሚያ እንዲያዩት ይደረጋልና ተሞክሮ መወሰድ ቢችል በማለት ሃሳብ ሰንዝረዋል።

የማስታወቂያ ባለቤቶች ግነት ስለሚወዱ መገናኛ ብዙሃን ማስተናገድ ያለባቸውን ለይተው ቢያሰራጩ ጥሩ ነው ሲሉም ተናግረዋል።

ፖሊሲው ፀድቆ ወደ ስራ ሲገባ የተባሉትን ችግሮች ለመቅረፍ ያስችላል ያሉት ደግሞ ረቂቁን ያቀረቡት በመንግስት ኮሙኒኬሽን የሚዲያ ልማትና ብዝሃነት ዋና ዳይሬክተር አቶ ታምራት ደጀኔ ናቸው።

እንደ ረቂቅ ፖሊሲና ስትራቴጂው የህፃናትና ወጣቶችን ተጋላጭነት ለመከላከል የአልኮል ማስታወቂያ ከአራት ሰዓት በፊት አይተላለፍም።

ማስታወቂያዎች በመገናኛ ብዙሃን ይዘትና የጊዜ ሰሌዳ ላይ ተፅዕኖ እንዳይኖራቸው ያላቸውን ሰዓት የመቀነስ ስራም ይሰራል።

የማስታወቂያ ዘርፍ ብሔራዊ ካውንስል በማቋቋም ተዋናዮች ሙያዊ ስነ-ምግባር ጠብቀው እንዲሰሩም ያደረጋል።

ከጤና፣ ከምግብና ከህክምና ጋር የተገናኙ ማስታወቂያዎች ከተቋማቱ ጋር በመሆን የክትትልና ቁጥጥር ስራ ይደረግባቸዋል።

የገበያውን ተዋዳዳሪነት ከማሳደግ ጎን ለጎን አቅም ላልገነቡ መገናኛ ብዙሃን የተለየ ማበረታቻ እንደሚደረግላቸውም ነው የተገለጸው።

ሌላው ፖሊሲና ስትራቴጂው ከሚያስተካክላቸው ሁኔታዎች መከካከል ማስታወቂያዎች በአገር ውስጥ ቋንቋ ይዘጋጁ የሚለው አንዱ ነው፡፡

Leave A Reply

Your email address will not be published.

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

This website uses cookies to improve your experience. We'll assume you're ok with this, but you can opt-out if you wish. Accept Read More

Privacy & Cookies Policy