NEWS

የስሎቫኪያ መንግስት ለዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም ድጋፉን እንደሚሰጥ አስታወቀ

By Admin

May 19, 2017

ለዓለም ጤና ድርጅት ዳይሬክተር ጄኔራልነት የሚወዳደሩት ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም እንዲመረጡ ድጋፍ እንደሚያደርግ የስሎቫኪያ መንግስት ገለጸ።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው የፕሬስ መግለጫ እንዳስታወቀው፤ የስሎቫኪያ ሪፐብሊክ መንግስት ለዓለም አቀፍ ጤና ደርጅት ዳይሬክተር ጄኔራልነት በመወዳደር ላይ ያሉትን ዶክተር ቴድሮስ እንዲመረጡ ድጋፍ ያደርጋል።

በቅርቡ የአፍሪካ ካሪቢያንና ፓስፊክ ቡድን አባል አገሮች ሙሉ በሙሉ ድጋፋቸውን ለዶክተር ቴድሮስ መስጠታቸው የሚታወስ ነው።

በእናቶችና ሕጻናት ሞት ቅነሳ፣ የወባና የልጅነት ልምሻ በሽታዎችን ከአገሪቷ ለማጥፋት ባደረጉት ያላሰለሰ ጥረት በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ተደማጭነትን አግኝተዋል። በዚህ ምክንያትም የተለያዩ ሽልማቶችን ተበርክቶላቸዋል።

ዶክተር ቴድሮስ በዚህ ምርጫ አሸናፊ ከሆኑ ለኢትዮጵያ ብሎም ለአፍሪካ እንዲሁም ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ አስቸጋሪ የሆኑትን የዓለም ጤና ችግሮችን ለመፍታት የሚያስችሉ ሁኔታዎችን ይፈጥራሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ምርጫው ግንቦት 15 ቀን 2009 ዓ.ም በስዊዘርላንድ ዋና ከተማ ጄኔቫ የሚካሄድ ሲሆን፤ ድጋፍ ለማጠናከር የኢትዮጵያ የልዑካን ቡድን በቅርቡ ወደዚያው ያቀናል።

ዶክተር ቴድሮስ በምርጫው ካሸነፉ የመጀመሪያው አፍሪካዊ የዓለም የጤና ድርጅት ዳይሬክተር ጄኔራል ይሆናሉ።

የኢትዮ – ስሎቫኪያ የሁለትዮሽ መደበኛ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የተጀመረው እንደ አውሮፓዊያን አቆጣጠር በ1947 ሲሆን፤ ፋሺስት ኢጣሊያ ኢትዮጵያን ስትወር ድርጊቱን ካወገዙ አገሮች መካከል ስሎቫኪያ አንዷ ነች።

የሁለቱን አገሮች የንግድና ኢንቨስትመንት ግንኙነት ለማጠናከር ተደራራቢ ቀረጥ ለማስወገድና የኢንቨስትመንት ጥበቃ አስመልከቶ መስከረም 2009 ዓ.ም ስምምነት መፈራረማቸው ይታወሳል።