CURRENT

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሐይል በአፍሪካ የሀይል አቅርቦት አሸናፊ ሆነ

By Admin

May 23, 2017

በአፍሪካ በውሃና በሐይል አቅርቦት ኢንዱስትሪ ከፍተኛ ተግባር ላከናወኑ ተቋማት የሚሰጠውን የአፍሪካ ዩቲሊቲ የኢንዱስትሪ ሳምንት ሽልማት በሐይል አቅርቦት የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሐይል ማሸነፉን ኤች ቲ ኤክስ ቲ አፍሪካ የተሸኘ ድረ ገጽ አስነብቧል፡፡

የሽልማት ስነ ስርአቱ በደቡብ አፍሪካዋ ኬፕታውን ከተማ መከናወኑ ተገልጿል፡፡

በአራተኛው ዙር የሽልማት ፕሮግራሙ ላይ 750 የአፍሪካ ታዋቂ የውሃና የሐይል አቅርቦት ባለሙያዎች ታድመውበታል፡፡ የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ መሪ ኔልሰን ማንዴላ የግል አማካሪ የነበሩት ዜልዳ ላ ግራንጌ የመክፈቻ ንግግር አድርገዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሐይል ዋና ኦፊሰር የሆኑት አቶ አበበ ካህሳይ በኩባንያው ስም ከፍተኛ የተባለውን ሽልማት ከተቀበሉ በኋላ“ እዚህ ተገኝቼ ይህንን ሽልማት መቀበሌ ታላቅ ክብር ነው፡፡ሽልማቱ ላገኘነው ስኬት ታላቅ ምልክት ነው፡፡ በመጪው ጊዜ ጠንክረን በመስራት የህዝባችንን ችግር ለመፍታት ሐይል ይሆነናል .” ማለታቸውን ድረ ገጹ አስነብቧል፡፡

ኢትዮጵያ በአህጉሪቱና ከአህጉሪቱ ውጭ የሐይል አቅርቦት መዳረሻ ለመሆን በታላቅ ተግባር መጠመዷን ያመለከተው ዘገባው በአሁኑ ወቅት ጅቡቲና ሱዳን ከዋናው ማከፋፋያ ጋር በተገናኘ መስመር የሐይል አቅርቦት እያገኙ ነው ብሏል፡፡

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሐይል አስራ ሁለት የውሃ ሀይል ማመንጫና ሶስት የንፋስ ሐይል ማመንጫ ጣቢያዎችን የሚያስተዳድር ሲሆን በአጠቃላይ 4 ሺ 290 ሜጋ ዋት ሐይል ወደ አገሪቱ ሐይል ማከፋፋያ ቋት ያስገባል፡፡

የጊቤ 3 ሐይል ማመንጫ 1 ሺ 870 ሜጋ ዋት በማመንጨት ከፍተኛውን ድርሻ ይዟል፡፡ በመገንባት ላይ የሚገኙት ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ 6 ሺ 450 ገናሌ ዳዋ 254 ሜጋ ዋት ሐይል ማመንጫ ግንባታቸው ሲጠናቀቅ የአገሪቱን የሐይል ፍላጎት የመሸፈን ብቃት እንዳላቸው ይታመናል፡፡

በውድድሩ በተለያዩ ዘርፎች አሸናፊ የሆኑ የኬንያ፣የኡጋንዳ ፣ማላዊ፣ ናይጀሪያ፣ደቡብ አፍሪካና ሴኔጋል ድርጅቶች ሽልማት እንደተበረከተላቸው በመጻፍ ድረ ገጹ ዘገባውን ደምድሟል፡፡