NEWS

ጅቡቲ በአፍሪካ ዘመናዊ ወደብ ለአገልግሎት ክፍት አደረገች

By Admin

May 25, 2017

ጅቡቲ በአፍሪካ ዘመናዊ የተባለውን ወደቧን ለአገልግሎት ክፍት አደረገች፡፡

“ዶራሌህ መልቲ ፐርፐዝ ፖርት” የሚል ስያሜ ያለው ይህ ወደብ ሀገሪቱ ለዓለም አቀፋዊ የመርከብ አገልግሎት ተደራሽነት የምታደርገው ጥረት አካል ነው ተብሏል፡፡

ዶራሌህ ባለብዙ አገልግሎት የወደብ መሰረተ ልማት ለጅቡቲ ለአፍሪካ የንግድ እምብርት መሆኗን ማረጋጋጫ ነው ሲሉ የጅቡቲ ወደቦች እና ነጻ ቀጠና ባለስልጣን ሃላፊው አቡበከር ኦማር ሃዲ ተናግረዋል፡፡

ዶራሌህ ወደቡ በ690 ሄክታር ላይ ያረፈ ሲሆን፥ ለግንባታውም ከ590 ሚሊየን የአሜሪካ ዶላር በላይ ወጪ ጠይቋል፡፡

ወደቡ 752 ኪሎ ሜትር ከሚረዝመው ከአዲስ አበባ ጅቡቲ የባቡር መስመር ፕሮጀክት ጋር በተመሳሳይ ጊዜ ነው ለአገልግሎት ዝግጁ የሆነው፡፡

ጅቡቲ እስያን፣ አፍሪካን፣ እና አውሮፓን በማስተሳሰር የዓለም የንግድ መስመር ማዕከል ሆናለች፡፡

አዲሱ ወደቧም ከተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች የሚመጡ 30 ሺህ መርከቦችን ተቀብሎ የማሳረፍ አቅም አለው፡፡

በዚህም ከእስያ ሀገራት 59 በመቶ፣ ከአውሮፓ 21 በመቶ ከአፍሪካ ደግሞ 16 በመቶ የንግድ እቃዎችን ያስተናግዳል፡፡

ምንጭ፡-ሲጂቲኤን