NEWS

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም በሳዑዲ ያለሕጋዊ የመኖሪያ ፈቃድ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ወደ አገራቸው አለመመለሳቸው እንዳሳሰባቸው ገለጹ

By Admin

May 19, 2017

በሳዑዲ ዓረቢያ ያለሕጋዊ የመኖሪያ ፈቃድ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን ወደ አገራቸው ለመመለስ ያሳዩት ቸልተኝነት እንዳሳሰባቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ገለጹ።

ለሥራ ጉብኝት ቻይና የሚገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም የሳዑዲ መንግስት ህጋዊ የመኖሪያ ፍቃድ የሌላቸው ዜጎች አገር ለቀው እንዲወጡ ባስቀመጠው ጊዜ ገደብ መሰረት ኢትዮጵያዊያኑ በሚፈለገው ልክ ወደ አገራቸው አለመመለሳቸው እንዳሳሰባቸው ገልጸዋል።

የአገሪቷ መንግስት የሰጠው የ90 ቀናት የምህረት ቀነ ገደብ ሊጠናቀቅ ጥቂት ቀናት የቀረው በመሆኑ መውጣት የሚገባቸው ዜጎች በቶሎ ወደ አገራቸው እንዲመለሱ ጥሪ አቅርበዋል።

”ጊዜው ካለፈ በኋላ የሳዑዲ መንግስት በግዳጅ እንዲመለሱ ማድረጉ ስለማይቀር ባለችን አጭር ጊዜም ቢሆን ያለ ውጣ ውረድና ችግሮች ከመከሰታቸው በፊት ዜጎቻችን በተሰጣቸው እድል ተጠቅመው ወደ አገር ቤት ቢመለሱ የተሻለ ነው” ብለዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም እንደገለጹት፤ ዜጎችን በህገ ወጥ መንገድ ከአገራቸው እንዲወጡ ያደረጉ ደላሎች ሀሰተኛ መረጃ በመስጠት እንዳይመለሱ እያደረጉ ይገኛል።

እነዚህ ደላሎች አሁንም ሌሎች ዜጎችን ወደ እዚያው ለመውሰድ እየሰሩ መሆኑን የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ “ሁሉም ዜጋ በአንድ ላይ ሊታጋላቸው ይገባል” ብለዋል።

በሳዑዲ ያለህጋዊ ፈቃድ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን የተሰጣቸውን የምህረት ጊዜ ተጠቅመው በሰላም ወደ አገራቸው እንዲመለሱ መንግስት “በአገሪቷ በሚገኙ ሚሲዮኖች በኩል ጥረት እያደረገ ነው” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የጊዜ ገደቡ ከመድረሱ በፊት እንዲመለሱ ቤተሰቦችና ሁሉም ዜጋ ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።

ተመላሾቹ በአገር ቤት የራሳቸውን ስራ ፈጥረው ኑሯቸውን እንዲመሩ መንግስት ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑንም ገልጸዋል።