CURRENT

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም በጥልቅ ተሃድሶ የተለዩ የመልካም አስተዳደር ግቦች ተፈጻሚ እንዲሆኑ አሳሰቡ

By Admin

May 22, 2017

የመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በጥልቅ ተሃድሶ የተለዩ የመልካም አስተዳደር ግቦችን ተረባርብው ተፈጻሚ እንዲያደርጉ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ አሳሰቡ።

የመለስ ዜናዊ የአመራር አካዳሚ ለ471 የመንግሥት ከፍተኛ አመራር አባላት ለ35 ቀናት ሲሰጥ የቆየው ሥልጠና ዛሬ ተጠናቋል።

ሥልጠናው በአብዮታዊ ዴሞክራሲ፣ በድርጅት ግንባታ፣ በአመራር ሳይንስ፣ በልማታዊ ኮሙኒኬሽን፣ በሁለተኛው የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ እንዲሁም በታላቁ መለስ ዜናዊ አስተምህሮ ላይ ያተኮረ ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም እንደተናገሩት፤ ሥልጠናው በተሃድሶ ግምገማ ተለይተው ከሚሰራባቸው ተግባራት መካከል አንዱ በመሆኑ ልዩ ሥፍራ ሊሰጠው ይገባል።

“ሥልጠና በራሱ አንድ ውጤት ነው” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ትክክለኛ ውጤታማነቱ የሚረጋገጠው ደግሞ ኅብረተሰቡን ለልማትና ለዴሞክራሲ እንዲነሳ በማድረግ መሆኑን ገልጸዋል ።

በተለይም በጥልቅ ተሃድሶ የተለዩ ግቦችን እንዲሳኩ መረባረብ እንዳለባቸው አሳስበው፤ ኅብረተሰቡ ለሚያነሳቸው ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት ትኩረት እንዲያደርጉ አቅጣጫ አስቀምጠዋል።

በሥልጠናው የታዩት መልካም ሥነ-ምግባሮች አመራር አባላቱ ወደ ሥራ ገበታቸው ሲመለሱ በተመሳሳይ ተግባራዊ በማድረግ የላቀ አፈጻጸም ማስመዝገብ እንዳለባቸውም አስረድተዋል።

ይህንም በማድረግ የሁለተኛው የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ ማሳካት እንደሚቻል ጠቁመው፤ ለዚህም ኢህአዴግ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።

የአዲስ አበባ ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ ዶክተር ታቦር ገብረ መድህን ሠልጣኞቹን ወክለው እንደተናገሩት፤ ሥልጠናው ኅብረተሰቡን በላቀ ደረጃ ለማገልገል የሚያስችል አቅም የተገኘበት ነው።

“በተሃድሶ የተለዩትን ሥራዎችም ዳር ለማድረስ የሚያስችል የአመለካከት ጥራትና የተሻለ እውቀት እንድናገኝ ያስቻለ ሥልጠና ነው” ብለዋል።

በሥልጠናው የተገኙትን የአመለካከትና የእውቀት ግብዓት ወደ ተግባር በመቀየር “የኅብረተሰቡን እርካታ ለማረጋገጥ ርብርብ ለማድረግ ቃል ገብተናል” ሲሉም ተናግረዋል።

ሠልጣኞቹ ያወጡት ባለ ሰባት ነጥብ የአቋም መግለጫም ተነቧል።