NEWS

26ኛው የግንቦት 20 በዓልና የካናዳ 150ኛ ዓመት በታላቅ ድምቀት ተከብሮ ዋለ

By Admin

May 30, 2017

26ኛው የግንቦት 20 በዓልና የካናዳ 150ኛ ዓመት በታላቅ ድምቀት ተከብሮ ዋለ 26ኛው የግንቦት 20 በዓልና የካናዳ 150ኛ ዓመት በዓል እ.ኤ.አ ሜይ 28 ቀን 2017 ከኦታዋ ከተማ ጋር በመተባበር በከተማው ላንስዳውን ፓርክ ተብሎ በሚታወቀው ሥፍራ በሚገኝ አዳራሽ ለመላው የኦታዋ ከተማ ነዋሪዎች ክፍት በሆነ የበዓል ሥነ-ሥርዓት ኢትዮጵያዊያንና ትውልድ ኢትዮጵያዊያን እንዲሁም በርካታ ካናዳዊያን በተገኙበት በተካሄደ የተለያዩ ዝግጅቶችን ያካተተ የሙሉ ቀን ፕሮግራም በድምቀት ተከብሮ ውሏል፡፡ የኦታዋ ከተማ የካናዳን 150ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ Ottawa Welcomes the World በሚል ርዕስ ሚሲዮኖች እንዲሣተፉ ባዘጋጀው መድረክ በኦታዋ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ኤምባሲ የግንቦት 20 በዓልን የንግድ፣ የቱሪዝም፣ የባህል፣ የኢትዮ-ካናዳ ግንኙነት የሚያንፀባርቅ የፎቶ ኤግዚቢሽን እንዲሁም የባህላዊ ውዝዋዜና ፋሽን ሾው የባህላዊ ቡና አፈላል ሥነ-ሥርዓት፣ የባህላዊ ምግብ ዝግጅትና የተለያዩ የልጆች ፕሮግራሞች በማዘጋጀት አጠቃላይ የሃገር ገፅታ ግንባታ ፕሮግራም ለታዳሚዎች አቅርቧል፡፡

በዕለቱ አምስት ሺህ የሚጠጉ የኦታዋ ነዋሪዎች በሙሉ ቀን ዝግጅቱ በተለያዩ ሰዓት ሊጎበኙ መቻላቸው ታውቋል፡፡ ዝግጅቱ በኦታዋ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ኤምባሲ አስተባባሪነት ከሃገራችን ቡና አስመጪ ኩባንያዎች፣ በኦታዋ ከተማ የሚገኙ የኢትዮጵያ ሬስቶራንቶች፣ በጎ ፈቃደኛ ካናዳዊያንና ትውልድ ኢትዮጵያዊያንን በመጋበዝ ያሳተፈ ሲሆን፤ ኢትዮ-ካናዳ ባህላዊ ተቋም የተባለ ዊኒፔግ የሚገኝ የትውልድ ኢትዮጵያዊያን ድርጅት የተለያዩ ብሄር ብሄረሰቦች ባህላዊ ውዝዋዜ በማቅረብ ለበዓሉ ልዩ ድምቀት ሠጥቷል፡፡

በዚሁ ዕለት ለዲፕሎማቲክ ኮሙኒቲውና ለካናዳ ባለስልጣናት በተዘጋጀ የምሽት ሪሴፕሽን ፕሮግራም ላይ የኦታዋ ከተማ ከንቲባ የተከበሩ ጂም ዋትሰን የተገኙ ሲሆን፤ የካናዳ 150ኛ ዓመት በዓልንና የግንቦት 20 በዓልን አስመልክቶ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡ ክብርት አምባሳደር ብርቱካን አያኖ በካናዳ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ መንግስት ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር 26ኛው ዓመት የግንቦት 20 በዓል ምክንያት በማድረግ ባሰሙት ንግግር ሃገራችን ባለፉት 26 ዓመታት በፖለቲካ ኤኮኖሚና ማህበራዊ መስኮች ያስገኘቻቸውን ድሎች እንዲሁም ኢትዮጵያና ካናዳ ግንኙነት ይበልጥ እየተጠናከረ መምጣቱን ገልፀዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ከካናዳ ግሎባል አፌይርስ ተወካይ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

በግንቦት 20 ዕለት በኦታዋ ከተማ በተካሄደው Tamarack Ottawa ማራቶን በሴቶች ኢትዮጵያ ከአንድ እስከ አራተኛ ያለውን የሜዳልያ ደረጃ በአሸናፊነት ያጠናቀቀች ሲሆን፤ አሸናፊዎቹ አትሌቶች አትሌት ጉተኒ ኢማን ወርቅ ሜዳልያ፣ አትሌት ህይወት ገ/ኪዳን ብር ሜዳልያ፣ አትሌት አበራሽ ፈይሳ ነሀስ ሜዴልያ እንዲሁም አበሩ መኩሪያ በምሽት ፕሮግራሙ በመገኘት ለበዓሉ ልዩ ድምቀት ፈጥረዋል፡፡ ግንቦት 21 ቀን 2009 ዓ.ም ኢ.ፌ.ዴ.ሪ ኤምባሲ ኦታዋ