Ethiopiaprosperous
Ethiopian News Ethiopian Daily news, Regarding political and social Issues.

ሰማዕታት የተሰውለትን ዓላማ ማስቀጠል እንደሚገባ ተገለጸ

0 434

Get real time updates directly on you device, subscribe now.

በአገሪቷ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እንዲገነባና ኢኮኖሚያዊ እድገት እንዲመዘገብ ሰማዕታት ታግለው የተሰዉለትን ዓላማ ማስቀጠል እንደሚገባ ተገለጸ።

በአዲስ አበባ የሚገኙ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች በ17ቱ የትግል ዓመታት ወቅት የተሰዉትን ሰማዕታትና በሓውዜን በግፍ የተጨፈጨፉ ዜጎች የመታሰቢያ በዓል ዛሬ አክብረዋል።

በበዓሉ የተገኙት አቶ ስብሃት ነጋ በወቅቱ እንደተናገሩት፤ ሰማዕታቱ ሕይወታቸውን የገበሩት ህዝባዊ መሰረት ያለው ስርዓት ለመገንባት ነው።

በወቅቱ ሰማዕታቱ የታገሉት የደርግ ስርዓትን ለመገርሰስ ብቻ እንዳልነበር ያመለከቱት አቶ ስብሃት፤ ታጋዮቹ ህዝባዊ፣ ዲሞክራሲያዊ ስርዓትና ዘላቂነት ያለው ኢኮኖሚያዊ እድገት ማስመዝገብ የምትችል ጠንካራ አገር ለመገንባት መሆኑን ተናግረዋል።

ነገር ግን ሰማዕታቱ ‘የተውት አደራ ከነጭራሹ የለም” ባይባልም አደራው በመሸርሸሩ ምክንያት እየተዳከመ  መምጣቱን አመልክተዋል።

በበዓሉ ላይ የተሳተፈችው ወጣት ገነት ገብረ እንደገለጸችው፤ በዓሉ መከበሩ ወጣቱ ትውልድ ያለፈውን ታሪክና የትግል ጉዞ በመረዳት ሰማዕታቱ የተሰውበትን ዓላማ ተግባራዊ ለማድረግ ያግዘዋል።

ሰማዕታቱ የተሰውበትን ዓላማ በመረዳት ወጣቱ ትውልድ ንቁ ተሳትፎ ማድረግ እንደሚገባውም  ገልጻለች።

ዶክተር ዮሃንስ ገብረሥላሴ በበኩላቸው እንደተናገሩት፤ ሰማዕታቱ ራሳቸውን አሳልፈው የሰጡት ወጣቱ ትውልድ ጊዜውን ‘በጦርነት ማሳለፍ የለበትም’ በሚል ነው።

ስለሆነም የአሁኑ ትውልድ አገሪቷ የጀመረችውን የልማት ተግባራት ከዳር የማድረስ ኃላፊነት እንደሚጠበቅበት ገልጸዋል።

“ሰማዕታቱ ሁሉም ክልሎች በራሳቸው ቋንቋ እንዲማሩና ራሳቸውን በራሳቸው እንዲያስተዳድሩ የሚያደርግ የፌዴራል ስርዓት ፈጥረውልናል። ስለሆነም ይህን ስርዓት መጠበቅ ያስፈልጋል” ያሉት ደግሞ የበዓሉ ተሳታፊ አቶ ሰይፈ ደርቤ ናቸው።

በአገሪቷ ተከስቶ የነበሩ አንዳንድ ችግሮችም ሰማዕታት የተሰዉለት ዓላማ ባለመጠበቁ መሆኑን ነው የገለጹት።

የመታሰቢያ በዓሉ በትግል ወቅት የተሰዉ ሰማዕታትና በ1980 ዓ.ም በሓውዜን በተፈጸመ የአውሮፕላን ድብደባ ሕይወታቸው ላለፉ 2 ሺ 500 ንጹሃን ዜጎችን ለማስታወስ በየዓመቱ ሰኔ 15 ቀን ይከበራል።

Leave A Reply

Your email address will not be published.

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

This website uses cookies to improve your experience. We'll assume you're ok with this, but you can opt-out if you wish. Accept Read More

Privacy & Cookies Policy