NEWS

በስትራቴጂክ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ የዓባይ ተፋሰስ አገሮች የመሪዎች ጉባዔ በኢንቴቤ ተካሄደ

By Admin

June 22, 2017

በስትራቴጂክ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ የዓባይ ተፋሰስ አገሮች የመሪዎች ጉባዔ በኡጋንዳ ኢንቴቤ ተካሄደ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝን ጨምሮ ሌሎች የተፋሰሱ አገሮች መሪዎች ውይይቱ ላይ ተገኝተዋል።

የዓባይ ተፋሰሱ አገሮች ስብሰባ ከሦስት ቀናት በፊት የተጀመረ ሲሆን፤ በእነዚሁ ቀናት የውሃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስትሮች እንዲሁም የውሃ ዘርፍ ባለሙያዎች በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ መክረዋል።

‘የአካባቢ መራቆትና የደን መጨፍጨፍ፣ የሕዝብ ቁጥር መጨመር፣ የኢንዱስትሪ መስፋፋት’ በሚሉት ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የተፋሰሱ አገሮች መሪዎች ዛሬ ተወያይተዋል።

የተፋሰሱ አገሮች ችግሮቹን ተቋቁመው በጋራ ተጠቃሚ በሚሆኑባቸው ስልቶች ላይ መምከራቸውን ውይይቱን የተከታተሉት የውሃ፣ መስኖና ኤሌክትሪክ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ ገልጸዋል።

የናይል ተፋሰስ አገሮች የትብብር ማዕቀፉን በፓርላማቸው ያላጸደቁ አገሮች እንዲያጸድቁም ሀሳብ ቀርቧል።

ከተፋሰሱ አገሮች መካከል ኢትዮጵያ፣ ኬኒያ፣ ኡጋንዳ፣ ሩዋንዳ፣ ታንዛኒያ እና ቡሩንዲ የትብብር ማዕቀፉን መፈረማቸው ይታወሳል።

በቀጣይም የናይል ተፋሰስ አገሮች ስብሰባ በመሪዎች ደረጃ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ከመግባባት ላይ መደረሱን ሚኒስትሩ መግለጻቸውን ኢዜአ ከኡጋንዳ ኢንቴቤ ዘግቧል።

ቡሩንዲ፣ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ግብፅ፣ ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ሩዋንዳ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሱዳን፣ ታንዛኒያና ኡጋንዳ የናይል ተፋሰስ አገሮች ትብብር አባላት ሲሆኑ፤ ኤርትራ በታዛቢነት ትሳተፋለች።

አገሮቹ የናይልን ወንዝ ፍትሃዊ በሆነ መልኩ ለመጠቀም በተደጋጋሚ ውይይቶችን ማካሄዳቸው ይታወቃል።