NEWS

በሽብር ድርጅት ውስጥ ሙሉ በሙሉ በመሳተፍ ወንጀል በተከሰሱ 16 ግለሰቦች ላይ የቅጣት ውሳኔ ተሰጠ

By Admin

June 23, 2017

በሽብር ድርጅት ውስጥ ሙሉ በሙሉ በመሳተፍ ወንጀል በተከሰሱ ግለሰቦች ላይ የቅጣት ውሳኔ ተሰጠ፡፡

ተከሳሾች 1ኛ መቶ አለቃ ጌታቸው መኮንን፣ 2ኛ በላይነህ ሲሳይ፣ 3ኛ አለባቸው ማሞ፣ 4ኛ አወቀ ሞኜ፣ 5ኛ ዘሪሁን በሬ፣ 6ኛ ወርቅዬ ምስጋናው፣ 7ኛ አማረ መስፍን፣ 8ኛ ተስፋዬ ታሪኩ፣ 9ኛ ቢሆነኝ አለነ፣ 10ኛ ተፈራ ፈንታሁን፣ 11ኛ ፈረጄ ሙሉ፣ 12ኛ አትርሳው አስቻለው፣ 13ኛ እንግዳው ዋኘው፣ 14ኛ አንጋው ተገኘ፣ 15ኛ አግባው ሰጠኝ እና 16ኛ አባይ ዘውዱ ናቸው።

የጠቅላይ አቃቢ ህግ ክስ እንደሚያመለክተው ተከሳሾች ከ2004 ዓ.ም በፊት የመኢአድ የፖለቲካ ፓርቲ አባላት የነበሩ ናቸው።

ከ2004 እስከ የካቲት 2006 ዓ.ም ደግሞ ራሱን አርበኞች ግንቦት ሰባት ብሎ የሚጠራው የሽብር ቡድን አባል መሆናቸውም በክሱ ተጠቅሷል።

ተከሳሾች በአማራ ክልል ባህርዳርና ጎንደርን ጨምሮ በሌሎች ከተሞች በመንቀሳቀስ የሃገሪቱን መረጃ ለሽብር ቡድኑ በማቀበልና አባላትን በመመልመል ወደ ኤርትራ መላካቸውም በክሱ ተዘርዝሯል።

ተከሳሾቹ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ የወንጀል ችሎት ጉዳያቸው ሲታይ ቆይቷል፡፡

ችሎቱ ባለፈው ሳምንት በ13ቱ ላይ የጥፋተኝነት ውሳኔ በማሳለፍ የቅጣት ውሳኔ ለመስጠት ለዛሬ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቶ ነበር፡፡

ችሎቱ ተከሳሾቹ የቤተሰብ አስተዳዳሪ፣ ያሉበት የጤና ሁኔታ እና ከዚህ ቀደም ምንም አይነት የወንጀል ሪከርድ የሌለባቸው መሆኑን በቅጣት ማቅለያነት ይዞላቸዋል፡፡

በዚህ መሰረት 1ኛ መቶ አለቃ ጌታቸው መኮንን፣ 4ኛ አወቀ ሞኜ፣ 5ኛ ዘሪሁን በሬ፣ 6ኛ ወርቅዬ ምስጋናው፣ 7ኛ አማረ መስፍን፣ 8ኛ ተስፋዬ ታሪኩ፣ 10ኛ ተፈራ ፈንታሁን፣ 13ኛ እንግዳው ዋኘው እና 15ኛ አግባው ሰጠኝ በነጻ ተሰናብተዋል፡፡

ከዚህ ባለፈም 3ኛ አለባቸው ማሞ፣ 11ኛ ፈረጄ ሙሉ እና 16ኛ አባይ ዘውዱን ደግሞ በአራት አመት ለሁለት ወር ፅኑ እስራት እንዲቀጡ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

2ኛ በላይነህ ሲሳይ፣ 9ኛ ቢሆነኝ አለነ፣ 12ኛ አትርሳው አስቻለው እና 14ኛ አንጋው ተገኘ ደግሞ በአራት አመት ከስድስት ውር ፅኑ እስራት እንዲቀጡ ወስኗል፡፡ FBC

በታሪክ አዱኛ