Ethiopiaprosperous
Ethiopian News Ethiopian Daily news, Regarding political and social Issues.

ባለስልጣኑ የክረምቱን መግባት ተከትሎ ከግንቦት 30 ጀምሮ የመንገድ ቁፋሮ እንዳይከናወን ከለከለ

0 391

Get real time updates directly on you device, subscribe now.

የክረምት ወር መግባትን ተከትሎ ከግንቦት 30  ቀን 2009 ዓ.ም እስከ ጥቅምት ወር 2010 ዓ.ም ድረስ ማንኛውም አካል የመንገድ ቁፋሮ ማከናወን እንደማይችል የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን አስታወቀ።

ባለስልጣኑ በተለይም የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን በተፈቀደለት የጊዜ ገደብ መሰረት ግንባታዎችን አለማከናወኑ በነዋሪዎቹ ዘንድ ቅሬታን እያስከተለ መሆኑን ገልጿል፡፡

ቅሬታ ከሚነሳባቸው መንገዶች መካከል በተለምዶ ሰሜን ማዘጋጃ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ፥ በተለይም በሰሜን ጤና ጣቢያ በኩል በሚያልፈው መንገድ የፍሳሽ ማስወገጃ ቁፋሮ እየተከናወነ መሆኑን ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት መታዘብ ችሏል።

የአካባቢው ነዋሪዎችም የመንገድ ዳር የፍሳሽ ማስወገጃው ቢሰራ የሚፈልጉት ቢሆንም ግንባታው እየተከናወነበት ያለው ጊዜ ግን የዝናብ ወቅት በመሆኑ ለችግር እንደዳረጋቸው ተናግረዋል፡፡

ስራው ከተጀመረ አንድ ወር ቢያስቆጥርም ባለመጠናቀቁ ከመኖሪያቸው ለመውጣት እና ለመግባት አመቺ አለመሆኑንም ገልጸዋል፡፡

በአካባቢው አቅመ ደካሞች እና ህጻናትን ጨምሮ ወደ ጤና ጣቢያው ለህክምና የሚመጡ ተገልጋዮች መንገዱ ምቹ ሁኔታን አልፈጠረላቸውም፡፡

በሌላ በኩል ላዛሪስት ትምህርት ቤት አቅራቢያ በሚገኘው የጋራ መኖሪያ ቤት የፍሳሽ ማስወገጃ ቁፋሮ ቢጀመርም የክረምት ወቅት በመሆኑ ተገቢነት እንደሌለው ነዋሪዎች ይገልጻሉ፡፡

የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ምክትል ዳይሬክተር ኢንጂነር ደመላሽ ገብረማርያም፥ በክረምት ወቅት የሚደረጉ ቁፋሮዎች ነዋሪዎች መንገዱን በአግባቡ እንዳይጠቀሙ እያደረገ መሆኑን መስሪያ ቤታቸው ማረጋገጡን ነው የተናገሩት።

ለአብነት የቀረበው የሰሜን ማዘጋጃ አካባቢ የውሃ እና ፍሳሽ ማስወገጃ ግንባታ እንዲጠናቀቅ የተቀመጠለት ቀነ ገደብ ከህዳር 21 ቀን 2009 ዓ.ም እስከ የካቲት 21 ቀን 2009 ዓ.ም ነበር፡፡

አሁን ላለው ቁፋሮና ግንባታ ባለስልጣኑ ፈቃድ እንዳልሰጠ የጠቀሱት ኢንጅነር ደመላሽ፥ ከተቀመጠለት የጊዜ ገደብ በላይ መጓተቱ ለችግር እየዳረገ ነው ብለዋል፡፡

ምክትል ዳይሬክተሩ እንዳሉት፥ መስሪያ ቤታቸው በከተማዋ ማንኛውም የመንገድ ቁፋሮና ግንባታ ከግንቦት 30 ቀን 2009 ዓ.ም እስከ ጥቅምት ወር 2010 ዓ.ም ድረስ እንዳይከናወን ከልክሏል፡፡

የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ እስጢፋኖስ ብስራት በበኩላቸው ለግንባታው መጓተት የግንባታው ስፍራ አለታማ መሆን እና ግንባታውን የሚያከናውኑት በጥቃቅን እና አነስተኛ የተደራጁ ኢንተርፕራይዞች አቅም ውስንነት መሆኑን ጠቅሰዋል።

የአዲስ አበባ መንዶች ባለስልጣን ከዚህ በኋላ ባስቀመጠው የክልከላ ቀነ ገደብ ውስጥ፥ ማንኛውም ግንባታ እንዳይከናወን እና የተጀመሩትንም ራሱ ተረክቦ እንደሚያጠናቅቃቸው ጠቁሟል፡፡

 

በአልዓዛር ታደለ

Leave A Reply

Your email address will not be published.

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

This website uses cookies to improve your experience. We'll assume you're ok with this, but you can opt-out if you wish. Accept Read More

Privacy & Cookies Policy