NEWS

የአዲስ አበባ ባቡር የሀይል መቆራረጥ ችግር እያጋጠመው መሆኑ ተገለጸ

By Admin

June 02, 2017

የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ትራንዚት በአገልግሎት አሰጣጡ አልፎ አልፎ የመብራት መቆራረጥና የተሽከርካሪ ትራፊክ አደጋ እያጋጠመው በመሆኑ መቸገሩን ገለፀ፡፡

አሽከርካሪዎች በባቡር ሀዲዱ ላይ በሚያደርሱት ጉዳት፣ በኤሌክትሪክ ሀይል መቆራረጥ፣ አገልግሎት የሚሰጡ የባቡር ቁጥሮች ማነስና በሌሎችም ምክንያቶች የባቡር አገልግሎቱ  በሚፈለገው ደረጃ ግልጋሎት እየሰጠ እንዳልሆነ የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ትራንዚት አገልግሎት ገልጿል፡

የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ትራንዚት አገልግሎት የህዝብ ግንኙነት ሀላፊ አቶ አወቀ ሙሉ በተለይ ለኢቢሲ እንደተናገሩት አልፎ አልፎ በቀላል ባቡር አገልግሎቱ ላይ የሚያጋጥመው የኤሌክትሪክ መቋረጥ የሚከሰተው ከብሔራዊ የኤሌክትሪክ ቋጥ በሚፈጠር ችግር ነው፡፡

በቀጣይ የኤሌክትሪክ አቅርቦቱ ታይቶ ችግሩ የማይፈታ ከሆነ ድርጅቱ ተጠባባቂ የሀይል ምንጭ የሆነው ጀነሬተር በመግዛት ይጠቀማል ብለዋል፡፡

በየባቡር ጣቢያው የአገልግሎቱን ፍጥነት ለመጨመርም በቀጣይ ተጨማሪ የባቡሮች ግዥ ከማከናወን ባለፈ በባቡር ሀዲዱ ላይ የተሽከርካሪዎች የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ ይሰራል ብለዋል አቶ አወቀ፡፡

ቀላል ባቡሩ ፍጥነቱን ጠብቆ በተፈለገው ደረጃ አገልግሎቱን እንዲሰጥ አሽከርካሪዎች የባቡር መሰረተ ልማትን ሳይጎዱ በሃላፊነት ስሜት ተጠንቅቀው እንዲያሽከረክሩ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ሀይል ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አበበ ካህሳይ በባቡር አገልግሎቱ የሚያጋጥመው የኤሌክትሪክ መቋረጥ በሀይል አገልግሎት ማሰራጫ በሚያጋጥሙ የተለያዩ ችግሮች እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡

በግዙፍ የኤሌክትሪክ ሀይል ማስተላለፊያ መስመሮችና ማከፋፈያ ጣቢያዎች በሚፈጠሩ ሰው ሰራሽና ተፈጥሮአዊ ችግሮች አልፎ አልፎ በባቡር አገልግሎቱ ላይ መስተጓጎል እየፈጠሩ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡

የቀላል ባቡር አገልግሎቱ በ1 ዓመት ከ8 ወር ገደማ ቆይታው ካሉት 41 ባቡሮች 30 የሚሆኑት መደበኛ አገልግሎት እየሰጡ ሲሆን ቀሪዎቹ ደግሞ ጥገና የሚፈልጉ ባቡሮች ሲፈጠሩ ተተኪ ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉ ተብሏል፡፡

በአሁን ወቅት በመዲናዋ የባቡር አገልግሎቱ ከ15 እስከ 20 ደቂቃ ባለ ጊዜ ውስጥ በየባቡር ጣቢያው ይደርሳል ነው የሚባለው፡፡

ሪፖርተር፦ሰለሞን አብርሃ