Artcles

ድርድሩና አጀንዳዎቹ

By Admin

June 29, 2017

ድርድሩና አጀንዳዎቹ

ዳዊት ምትኩ

ሰሞኑን ገዥው ፓርቲ ኢህአዴግን ጨምሮ 17 የፖለቲካ ፓርቲዎች ድርድር እያካሄዱ ነው። በድርድሩ ላይ የጋራ መግባባት የተደረሰባቸው አጀንዳዎችንም ይፋ አድርገዋል። ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች እዚህ ደረጃ ላይ ለመድረስ በርካታ ዙር ድርድርችን አካሂደዋል። እዚህ ደረጃ ላይ መድረሳቸው በራሱ ለሀገራችን የመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ከፍተኛ ፋይዳ አለው።

ይህ የፖለቲካ ፓርቲዎች ድርድር መድረክ የሀገራችንን ዴሞክራሲያዊ ስርዓት የሚያጎለብትና የፖለቲካ ምህዳሩን ይበልጥ የሚያሰፋ ነው። ውይይቱ ገና በአጀንዳ ደረጃ ያለ ቢሆንም ቅሉ፤ እዚህ ሀገር ውስጥ በመገንባት ላይ ያለውን የዴሞክራሲ ስርዓት እንዲሁም የሁሉንም ህዝቦች ውክልና የሚያጠናክር ነው። ስለሆነም ከጅምሩ ሊፈጠሩ የሚችሉ ክፍተቶችን የማጥበብና በሚያግባቡ ጉዳዩች ላይ ለሀገር ጥቅም ሲባል አንድ ላይ መስራት የግድ ይላል። ምክንያቱም ማናቸውም ዴሞክራሲያዊ ውይይቶች በመቻቻል መርህ መከናወን ስላለባቸው ነው።

የዚህ ሀገር ፖለቲካዊ አጀንዳ ህዝቡን የሚወክሉትና በሀገራችን በሰላማዊና ህጋዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጉዳይ ነው። ሌላ የማንም አይደለም።

በመሆኑም በእኔ እምነት በአንዳንድ በውጭ የሚኖሩ ፅንፈኛ ሃይሎች አማካኝነት ‘ህገ መንግስቱ ይሻሻል፣ የታሰሩ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ይፈቱ፣ ድርድሩ ውጤት አያመጣም…ወዘተ.’ የሚሉ የራሳቸው አጀንዳዎች አግባብ ያላቸው አይመስሉኝም። ምክንያቱም እነዚህ ከክርክሩና ከድርድሩ ዓላማዎች ጋር ፈፅሞ የማይሄዱት አስተሳሰቦች ጤናማ ያልሆኑና የዴሞክራሲያዊ ስርዓታችንን አንድም ስንዝር ወደፊት ፈቅ የሚያደርጉት ስላልሆኑ ነው። ርግጥ አስተሳሰቦቹ የማን እንደሆኑ የሚታወቅ ነው። ይሁንና እነዚህ አጀንዳዎች ለሀገራችን የመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ምንም ዓይነት ፋይዳ የሌላቸው መሆናቸውን ህዝቡ በሚገባ የሚገነዘበው ነው።

እንደሚታወቀው ኢህአዴግን ጨምሮ በቀጣይ ለመከራከርና ለመደራደር ውይይት እያካሄዱ ያሉት 17 የፖለቲካ ፓርቲዎች፤ ዓላማዎቻቸው ዴሞክራሲን ማስፋት፣ ሰላምን አስተማማኝ ማድረግና ብሔራዊ መግባባትን መፍጠር ናቸው።

እኔ እስከሚገባኝ ድረስ መንግስትም እንዲሆን የሚፈልገው በእነዚህ ዓላማዎች መንፈስ ነው።  ከዚህ ውጭ ፅንፈኞችና የውጭ ሃይሎች ተላላኪዎች የሚያነሷቸው አደናቃፊ ሃሳቦች አንድም ስንዝር ዕውን እንዲሆኑ የሚፈለጉ ሃሳቦችን የሚያመጡ አይደሉም።

እናም በክርክሩና በድርድሩ ወቅት ሁሉምወገኖች ማሰብ ያለባቸው የሀገራችን ዴሞክራሲ እንደምን እንደሚሰፋ፣ ሀገራችን ውስጥ የተገኘውን ፈጣንና ተከታታይ ልማት እንደምን በአስተማማኝ ሰላም ማጠናከር እንደሚቻል ብሎም በአብዛኛዎቹ ሀገራዊ ጉዳዩች ዙሪያ እንደምን ብሔራዊ መግባባትን መፍጠር እንደሚቻል ነው።

እንደሚታወቀው ዴሞክራሲን ለማስፋት ጊዜን ይጠይቃል። እንኳንስ እኛ ቀርቶ ተግባሩን ዕውን ካደረጉ ከ200 ዓመት በላይ ያስቆጠሩት ያደጉት ምዕራባዊያን ሀገራትም ቢሆኑ በተሟላ የዴሞክራሲ ቁመና ላይ ነው ያሉት ማለት አይቻልም። ዴሞክራሲ ከህብረተሰብ የአስተሳሰብ ልህቀት ብሎም ጥልቅ ግንዛቤ ጋር በጊዜ ሂደት ውስጥ የሚጎለብት ነው።

ዴሞክራሲን ለማስፋት ጊዜን ይጠይቃል። በጥቂት ዓመታት ውስጥ ተጀምሮ የሚጠናቀቅ አይደለም። የሂደት ጉዳይ ነው። እንኳንስ እኛ ቀርቶ ተግባሩን ዕውን ካደረጉ ከ200 ዓመት በላይ ያስቆጠሩት ያደጉት ምዕራባዊያን ሀገራትም ቢሆኑ በተሟላ የዴሞክራሲ ቁመና ላይ ነው ያሉት ማለት አይቻልም። ዴሞክራሲ ከህብረተሰብ የአስተሳሰብ ልህቀት ብሎም ጥልቅ ግንዛቤ ጋር በጊዜ ሂደት ውስጥ የሚጎለብት ነው።

ከዚህ አኳያ በሀገራችን የዴሞክራሲ ምንነት መሰማት ከጀመረ ገና 26 ዓመታትን እልፍ  ያለ የጎልማሳ ዕድሜን ያስቆጠረ ነው። በእነዚህ ዓመታት ውስጥ የተወሰነ ርቀት መጓዝ ቢቻልም፤ ያን ያክል የሚያስመካ አይመስለኝም። ለዚህም ሁለት ምክንያቶች በተግዳሮትነት መጠቀስ ያለባቸው ይመስለኛል—ለዴሞክራሲ ጀማሪ መሆናችንና ካለፉት ስርዓቶች ሲንከባለሉ የመጡት ፀረ-ዴሞክራሲያዊ አመለካከቶች በተገቢው ሁኔታ አለመቀረፋቸው።

ሀገራችን ለዴሞክራሲ አዲስ ናት። በዚህም ሳቢያ ስለ ዴሞክራሲ ፅንሰ ሃሳቦች የሚነሱ ጉዳዩች በሁሉም ወኖች በኩል ህፀፆችን መፍጠራቸው አይቀርም። በዚህም ግልፅነትና ተጠያቂነት ብሎም መቻቻልን የመሳሰሉ የዴሞክራሲ እሴቶችን በተገቢውና በፈጠነ ሁኔታ ገቢራዊ ማድረግ ያስቸግራል። ፅንሰ ሃሳቦች አዲስ በመሆናቸውም በአስተማማኝ ሁኔታ ይተገበሩ ዘንድ ጊዜን ምርኩዝ ያደርጋሉ። ብዥታምን ሊፈጥሩ ይችላሉ። ሆኖም ለተግባራዊነታቸው ከሂደት መማር ይቻላል።

በሌላ በኩልም ያለፉት ስርዓቶች በሀገራችን ህዝቦች መካከል ፈጥረውት ያለፉት ፀረ-ዴሞክራሲያዊ አስተሳሰቦች በቀላሉ የሚሽሩ አይደሉም። ፀረ-ዴሞክራሲያዊ እሳቤዎችን በዴሞክራሲያዊነት ለመቀየርም አስተሳሰብንና ስለ ዴሞክራሲ ያለንን አመለካከት መለወጥ ይገባል። በህዝቦች ውስጥ ለዘመናት ሲፈጠሩ የነበሩትን የተዛቡ ግንኙነቶች በጥቂት ዓመታት ውስጥ መቀየርም አይቻልም። ቀደም ሲል እንዳልኩት ጊዜንና የአስተሳሰብ ልህቀትን ይጠይቃል። ይህ ሁኔታም ምናምባትም ችግሮችን በዴሞክራሲያዊ ማዕቀፍ ውስጥ ለመፍታት የሚደረጉ ጥረቶችን ሊያሰናክል ይችላል። እናም ዴሞክራሲው እንዲሰፋ እነዚህን ሁለት ተግዳሮቶች መፍታት ይገባል። ይህን ዕውን ለማድረግም የህዝቡ ወኪሎች የሆኑት ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች የበኩላቸውን አስተዋፅኦ ሊያበረክቱ ይገባል። በመሆኑም ፓርቲዎቹ በክርክሩና በድርድሩ ሂደት ውስጥ ‘እነዚህን የዴሞክራሲ ተግዳሮቶች ለመፍታት ከእኔ ምን ይጠበቃል?’ ብለው ራሳቸውን መጠየቅ ይገባቸዋል። ይህን ሲያደርጉም ለሀገራቸው ዴሞክራሲ መስፋት የበኩላቸውን ሚና ይጫወታሉ።

ፓርቲዎቹ ሌላው ሊያነሱት የሚገባው ጉዳይ ክርክሩና ድርድሩ ሰላምን ከማረጋገጥ አኳያ ሊኖረው የሚገባውን ፋይዳ ነው። እንደሚታወቀው የዛሬ ሁለት ዓመት ገደማ በሀገራችን አንዳንድ አካባቢዎች ሁከት ተፈጥሮ ነበር። የሁከቱ አነሳሽ ምክንያት ምንም ይሁን ምን፤ ፓርቲዎች እንዲያ ያለው ሁከት ዳግም እንዳይፈጠር መስራት ይኖርባቸዋል።

ማንኛውም ዴሞክራሲያዊ ክርክርና ድርድር መቋጫው ጥርጣሬንና ግጭትን በማስወገድ ሰላምን ማምጣት ነው። ሰላም ካለ ሁሉም ነገር አለ። ያለ ሰላም ልማትን ማሰብ አይቻልም። ዴሞክራሲያዊ ስርዓቱንም ስር እንዲሰድ ማድረግ አይቻልም። ዴሞክራሲ ስር ባልሰደደበት ሀገር ውስጥ ደግሞ የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደ ልባቸው ሃሳባቸውን ለህዝባቸው ሊያስተዋውቁና በህዝቡ ይሁንታ በሚካሄድ ምርጫ ሀገር ሊመሩ አይችሉም።

እናም ከክርክርጨሩና ከድርድሩ ዴሞክራሲንና የፖለቲካ ምህዳሩን በማስፋት የራሳቸውን ህልውና ጭምር የሚያረጋግጡ መሆናቸውም ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች ሊገነዘቡት የሚገባ ይመስለኛል። አጀንዳቸውንም ከዚሁ በመመልከት በቀጣይ የሚያደርጉትን ድርድር ለሀገራችን የመድብለ ስርዓት ስርዓት እመርታ አኳያ መመዘን ይኖርባቸዋል።