Artcles

ከታላቁ መሪ ህልፈት በኋላም ኢሕአዴግ በስኬት ጎዳና ላይ ነው!

By Admin

August 10, 2017

ከታላቁ መሪ ህልፈት በኋላም ኢሕአዴግ በስኬት ጎዳና ላይ ነው!

ወንድይራድ  ኃብተየስ

 

በመጪው ሳምንት የታላቁ መሪ  የመለስ ዜናዊ  ህልፈት አምስተኛ ዓመት  እናከብራለን። አዎ የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄሮችና ህዝቦች እኚህ ታላቅ መሪ በተለሙት ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ  መንገድ  ተጉዘን ወዳቀድነው  የህዳሴ ማማ በመገስገስ ላይ ነን። ታላቁ መሪያችን አቶ መለስ ለአገራችን መለወጥ መሰረት ጥለው እንዳለፉ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ የሚያስማሙበት  እውነታ ነው። እኚህ ታላቅ ሰው የተሰውለት ዓላማ የታሰበለትን ግብ መምታት የሚያስችለው ትክክለኛ መንገድ ላይ ነው። ጽንፈኛ የዳያስፖራ ፖለቲከኞችና እነሱ የሚዘውሯቸው የአገር ቤት ወኪሎቻቸው ካልሆኑ በስተቀር የመለስን ታላቅነት፣ የመለስን ባለውለታነት፣ የመለስን ህዝባዊነት፣ የመለስን ጠንካራነት፣ የመለስን ምሁርነት፣ ወዘተ  የማይቀበል አንድም ኢትዮጵያዊ ያለ አይመስለኝም። የመለስን ታላቅነት አይደለም ኢትዮጵያዊ ዓለም የመሰከረው ሃቅ ነው።  እውነት እውነቱን እንነጋገር ከተባለ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ በአገር ውስጥም ያለን እንሁን በውጭ  የምንኖር ኢትዮጵያዊያን ከእኚህ ታለቅ መሪ ተጠቃሚ ያልሆነ  ማን ነው?

 

ታላቁ መሪ ህልፈትን ተከትሎ  አንዳንዶች ካለመለስ ኢህአዴግ እስትንፋስ የለውም፣ ኢህአዴግ  አበቃለት፣ ኢትዮጵያም አደጋ ላይ ነች ወዘተ ቢሉም እውነታው  ፍጹም ከዚህ የተለየ ሆኗል።  ታላቁ መሪ በአንድ ወቅት ስለኢህአዴግ እንዲህ ብለው ነበር። ለኢህአዴግ ጥንካሬ ትልቁ ነገር በድርጅቱ ውስጥ ያለው የቡድን አንድነትና የቡድን ስራ እንጂ  የኢህአዴግ ጥንካሬ በግለሰብ ላይ የተንጠለጠለ ድርጅት አይደለም ብለው ነበር። ይህ እውነታ በተጨባጭም ተረጋግጧል።   ኢህአዴግ በግለሰብ ላይ የተንጠለጠለ ድርጅት  ቢሆን ኖሮ በታላቁ መሪ ህልፈት ወቅት ድርጅቱ ይዳከም ነበር። ይሁንና ኢህአዴግ በድል ላይ ሌላ ድሎችን ማስመዝገቡን ቀጥሎበታል። የአገሪቱም የህዳሴ ጉዞ ቀጥሏል።

 

ታላቁ መሪ በኢህአዴግ ምስረታና ስኬት የአንበሳውን ድርሻ ያበርክቱ ታላቅ ስብዕና ያላቸው  ሰው  ይሁኑ  እንጂ ፓርቲው በግለሰቦች ላይ የተንጠለጠለ እንዳይሆን ተደርጎ የተዋቀረ ፓርቲ ነው። ታላቁ መሪ መለስ ለኢህአዴግ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያበረከተ ግለሰብ ነው። ይሁንና በእሳቸው ህልፈት ወቅት እንኳን ኢህአዴግ ጥንካሬውን አላጠም።   ኢህአዴግ ሺህ መለሶችን ያፈራ፣ ነገም የሚያፈራ፣ የበርካታ በለራዕዮች   ፓርቲ ነው።  በድርጅቱ የቡድን አሰራር የሚከተል፣ የድርጅት ወስጠ ዴሞክራሲያዊ አሰራር የሚተገብር ፓርቲ በመሆኑ ድርጅቱ በግለሰቦች መሄድና መምጣት የሚያጣው ወይም የሚያገኘው ነገር እጅግም  ነው።   

 

ታላቁ መሪ እጅግ ጠንካራና ዓለም ዓቀፋዊ ስብዕና የተላበሱ ግለሰብ ናቸው። በአገራችን ለተመዘገቡ ሁሉም  መልካም ነገሮች ላይ  የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር የአቶ መለስ ዜናዊ አሻራ በጉልህ የማይታይበት አንድም ነገር የለም።  ለአብነት ያህል ጥቂቶቹን ላንሳቸው እንጂ በእንዲህ ያለ ሁኔታ ሁሉንም ዘርዝሮ ማቅረብ የማይታሰብ  ነው። አገራችን ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍንባት፣ ዋስትና ያለው ዴሞክራሲያዊ  ስርዓት እንድትተገብር እንዲሁም ፈጣንና ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ  ዕድገት እንድታስመዘግብ  ታላቁ መሪ መለስ ትልቁንና የአንበሳውን ድርሻ አበርክቷል።

 

ታላቁ መሪ  የወጣትነት   ጊዜያቸውን ሁሉ ለሰላም፣ ለነጻነትና ለእኩልነት ሲሉ በዱር በገደል  ታግለውና አታግለው ለዘመናት ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ሲረገጡባት የኖረች አገራቸውንና ህዝባቸውን ነጻ አውጥተዋል። በዚህም ህገመንግስታዊ ስርዓት፣ ዋስትና ያለው ዴሞክራሲና ዘላቂ ሰላም የተረጋገጠባት  አዲሲቷን ኢትዮጵያ እውን አድርገዋል። በአዲሲቷ ኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና፣ ህዝቦች በእኩልነትና ነጻነት እንዲኖሩ መለስ ዜናዊ  ወሳኝ ሚና ነበራቸው። አቶ መለስ አገራችን የብዙሃን ፓርቲ ስርዓት እንድትከተል፣ የሃሳብ ልዩነቶች በነጻነት እንዲስተናገዱባት እንዲሁም የተለያዩ ብዝሃነቶች እንዲስተናገዱባት ከፍተኛ አስተዋጽዖ አበርክተዋል።

 

ታላቁ መሪ  ከትግል ወቅት ጀምሮ  ጠንካራ ወታደራዊ እውቀት ያላቸው ናቸው።  በመሆኑም ታላቁ መሪ መለስ ዜናዊ ኢትዮጵያ ጠንካራ፣ ታማኝና ህዝባዊ  የመከላከያ ሰራዊት እንዲኖራት  አበክረው ሰርተዋል። የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦችን እንዲመስል  ለህገመንግስቱ እና ለህገመንግስታዊው ስርዓት ብቻ የሚገዛ  ህዝባዊነትን የተላበሰ እንዲሆን አድርገዋል። ታላቁ መሪ የኢፌዴሪ መከላከያ ሰራዊት ህዝባዊነትን የተላበሰና ለህገመንግስቱ ተገዢ እንዲሆን ከማድረጋቸው ባሻገር  በጠንካራ አካላዊ ብቃት እና በወታደራዊ ዲሲፒሊን የታነጻ እንዲሆን አድርገዋል።

 

አቶ መለስ ባላቸው የዲፕሎማሲ ተቀባይነት አገራችን በአፍሪካም ሆነ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ  በሰላም ማስከበር ስራዎች ላይ ግንባር ቀደም እንድትሆን አድርገዋታል።  የአገራችን ሰራዊት ለሰላም ማስከበር ስራ በተሰማራባቸው አገሮች ሁሉ  እጅግ ስኬታማ ከተጣለበትን ግዳጅ ሁሉ በብቃት የተወጣ፣  በስነምግባር የታነጸና ለግዳጅ በተሰማራባቸው አካባቢዎች በሚኖሩ ህብረተሰቦች ሁሉ የተመሰገነና የተወደደ ነው። የአገራችን ሰላም አስከባሪ ሃይል ከወታደራዊ ተልዕኮ ባሻገር  በልማት ስራዎች ላይ በንቃት የሚሳተፍ ልማታዊ ሰራዊት ነው። ከዚህ በተጨማሪ ህዝባዊ የሆነው የሰላም አስከባሪ ሰራዊታችን ያለውን ስንቅ ለህብረተሰቡ አካፍሎ የሚሰጥ አዛኝና ሩህሩህ  ነው። ይህ አይነት ስነምግባር ዝም ተብሎ የተገኘ ነገር ሳይሆን እንደመለስ ያሉ ትላልቅ መሪዎች በሰራዊቱ ውስጥ ያሰረጹት ወታደራዊ ዲሲፒሊን  ነው።    

 

ታላቁ መሪ መለስ ዜናዊ አገራችን በዲፕሎማሲው መስክ ጠንካራ እንድትሆን አድርገዋታል። አቶ መለስ አንደበተ ርዕቱ ማንንም ተናገረው ማሳመን የሚችሉ፣ በተገኙበት መድረክ ሁሉ በበሳል ንግግራቸው የሚታወቁ ምሁር ናቸው። አገራችን በአፍሪካም ሆነ በዓለም ዓቀፍ ደረጃ  የዲፕሎማሲ  የበላይነት እንድትይዝ አድርገዋታል። አገራችን በምትከተለው ትክክለኛ የውጭና የውስጥ ፖሊሲ ሳቢያ በአገራችን በሰፈነው ሰላም መንግስትና ህዝብ አትኩሮታቸውን ወደ ልማት ማድረግ በመቻላቸው  በዓለም ፈጣንና ቀጣይነት ያለው የኤኮኖሚ እድገት እንድታስመዘግብ አድርገዋል። በእኚህ ታላቅ ሰው ምክንያት ዓለም ዛሬ  አገራችንን  የሚያይበት መነጽር ተለውጧል። አገራችን ባለፉት 14 ዓመታት ፈጣንና ቀጣይነት ባለው የኤኮኖሚ እድገት  እንድታስመዘግብ መለስ ወሳኝ ሚና ነበራቸው።

 

በኢትዮጵያ እየተመዘገበ ካለው የኤኮኖሚ እድገት  ሁሉም ዜጋ በየደረጃው ይነስም ይብዛም ተጠቃሚ የሚሆንበት ስርዓት መዘርጋት መቻሉ ነው።  የኢፌዴሪ መንግስት እየተመዘገበ ካለው እድገት ለህዝብ አገልግሎት የሚውሉ መሰረተ ልማቶችን ፍተሃዊ በሆነ መልኩ በመገንባት ላይ ይገኛል። ዛሬ በአገራችን ከአንድ ሶስተኛ አካባቢ የሆነው ህዝባችን ትምህርት ቤት እንዲገኝ ያደረገው በቂ ትምህርት ቤቶች መገንባት በመቻሉ ነው። ፍተሃዊ የሃብት ክፍፍል መኖሩን ከሚያሳዩ ነገሮች መካከል ይህ አንዱ ነው። ከዚህም ባሻገር በከተሞች የስራ እድል እንዲፈጠር እንዲሁም ለአነስተኛና መካከለኛ ገቢ ላላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች በአነስተኛ ወጪ የመኖሪያ ቤት እንዲያገኙ መንግስት በርካታ ስራዎችን በማከናወን ላይ ነው። በዚህም  ታላቁ መሪ  መለስ በአገሪቱ ድህነትን  በግማሽ አካባቢ መቀነስ ተችሏል።

 

ታላቁ መሪ የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ራሳቸውን  በራሳቸው ማስተዳደር እንዲችሉና አገሪቱ የፌዴራል ስርዓት እንድትከተል በማድግ ህዝቦች ቋንቋቸውን፣ ባህልና ወጋቸውን ማሳደግ እንዲችሉ  ትልቅ አስተዋጽዖም አበርክተዋል።  ታላቁ መሪ አዲሲቷ ኢትዮጵያ  በህዝቦች አንድነትና መፈቃቀድ ላይ የተመሰረተች  አንድነቷም በጠንካራ መሰረት ላይ  እንዲጸና  አድርገዋል። እኚህ ታላቅ ሰው በበሳልና በሰከነ አመራራቸው አገሪቱን ከመበታተን  አደጋ ታድገዋታል። አዲሲቷ ኢትዮጵያ  የብሄር፣ የሃይማኖት፣ የፖለቲካ አስተሳሰብ፣ ወዘተ ብዝሃነትን ማስተናገድ እንድትችል ሆና  የተገነባች እንድትሆን ታላቁ ሰው የበኩላቸውን ተወጥተዋል።

 

ታላቁ መሪ በአገሪቱ ሁለንተናዊ የሰላም፣ የልማትና ዴሞክራሲ ፖሊሲዎችና የመተግበሪያ ስልቶች ዙሪያ ቁልፍ ሚና እንደነበራቸው መረዳት አይከብድም።  ታላቁ መሪ  በኢህአዴግ ውስጥ በርካታ መለሶችን በርካታ በለራዕዮችን  በማብቃታቸው  ፓርቲያቸውም ሆነ የታገሉለት ዓላማ በስኬት ላይ ስኬት በመደራረብ ወደፊት በመገስገስ ላይ ነው። ኢህአዴግ በግለሰብ ላይ የተንጠለጠለ ፓርቲ እንዳይሆን ታላቁ መሪ  የራሳቸውን ሚና በመጫወታቸውም ፓርቲው ማንም ሄደ ወይም ማንም መጣ ከዓላማው የሚገታው አንድም ነገር አይኖርም። ይህ ነው የጠንካራ መሪ መልካም ስብዕና።