NEWS

ክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከብሪታኒያ የአፍሪካ ጉዳዮች ሚኒስትር ስቴዋርት ጋር ተወያዩ

By Admin

August 22, 2017

የኢፌዲሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የብሪታኒያ የአፍሪካ ጉዳዮች ሚኒስትር ሮሪ ሰቴዋርትን በፅህፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ።

በኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ጊዜ ስለሚከሰተው የድርቅ አደጋና ችግሩን ለመፍታት መንግስት እያደረገ በሚገኘው የሰብዓዊ ድጋፍ ዙሪያ ተወያይተዋል።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ መንግስት የድርቁን አደጋ ለመመከት በተቀናጀ መልኩ ምላሽ እየሰጠ መሆኑን አብራርተዋል።

መንግስት በአሁኑ ጊዜ አስቸኳይ የምግብ ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ወገኖች አስፈላጊውን ሁሉ ለማድረግ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ እንደሚገኝ ነው የገለፁት።

አቶ ደመቀ በአስቸጋሪ ወቅቶች የብሪታኒያ መንግስት ድጋፍና አጋርነት ወሳኝ መሆኑንም ጠቁመዋል።

የብሪታኒያ የአፍሪካ ጉዳዮች ሚኒስትሩ ሮሪ ስቴዋርት ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ችግር ምክንያት የሚገጥማትን ተከታታይ የድርቅ አደጋ ተቋቁማ ልማቷን ለማስቀጠል የምታደርገው ርብርብ የሚደነቅና ሊደገፍ የሚገባው ነው ብለዋል።

በተለይ የድርቁ አደጋ በጎዳቸው አካባቢዎች ለሚኖሩ ዜጎች በመንግስት በኩል ሰብዓዊ ድጋፍና ጠንካራ አመራር እየተሰጠ መሆኑን በጉብኝታቸው ወቅት ማረጋገጣቸውን ነው የተናገሩት።

ሚኒስትሩ የብሪታኒያ መንግስት ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።

ኢትዮጵያና ብሪታኒያ ሁሉን አቀፍ የሁለትዮሽ ትብብራቸውን አጠናክሮ ለማስቀጠል በጋራ እንደሚሰሩ መግባባት ላይ መደረሱን የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት አስታውቋል።FBC