HEALTH

የትግራይ ክልል ህዝብ በተሰበሰበበት ቦታ ሲጋራ እንዳይጨስ ባከናወነው ተግባር ከዓለም ጤና ድርጅት እውቅና አገኘ

By Admin

August 30, 2017

የትግራይ ክልል ሕዝብ በተሰበሰበበት ቦታ ሲጋራ እንዳይጨስ በመከላከል በኩል ላከናወነው ተግባርና ለተገኘው ውጤት በዓለም ጤና ድርጅት ዕውቅና አገኘ።

የትግራይ ክልል ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ተኽላይ ወልደማሪያም እንደገለጹት፥ ክልሉ እውቀና ያገኘው ሕዝብ በተሰበሰበባቸው ቦታዎች ላይ ሲጋራ እንዳይጨስ በተከናወኑ ተግባራትና በተገኘው ውጤት ነው።

አቶ ተኽላይ እንዳሉት በሲጋራ ምክንያት የሚከሰቱ የመተንፈሻ አካላት ጉዳት፣ የደም ብዛት፣ የልብ ሕመምና ሌሎች በሽታዎችን ለመከላከል ህዝብ በተሰበሰባቸው ቦታዎች ሲጋራ እንዳይጨስ ህግና ደንብ ወጥቷል።

ክልሉ በአውሮፓውያን አቆጣጠር ከየካቲት 2014 ጀምሮ ህዝብ በሚበዛባቸው አካባቢዎች ሲጋራ እንዳይጨስ ያጸደቀውን ህግ ሕብረተሰቡ ተቀብሎ ተግባራዊ ማድረጉና ለውጥ መምጣቱ ለሽልማት እንዲታጭ አድርጎታል።

በመጠጥ ቤቶች፣ በሥራ ቦታዎች፣ በገበያ ማዕከላትና በሌሎች ሕዝብ በሚሰበሰብባቸው የመዝናኛ ሥፍራዎች ለአጫሾች የተለየ ማጨሻ ቦታ መዘጋጀቱ ህጉን ተግባራዊ እንዲሆን ከማድረግ በላይ ውጤት እንዲመዘገብ አስችሏል” ብለዋል ።

በተጨማሪም ሕብረተሰቡ ሲጋራ ማጨስ በተከለከለባቸው አካባቢዎች አጫሾችን በመከላከልና በመገሰጽ በኩል ያደረገው ተሳትፎ የራሱን አስተዋጽኦ አድርጓል።

ከዚህ ጎን ለጎን የጤና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎችና የልማት ቡድኖች ያደረጉት ጥረትና የመጣው ለውጥ ክልሉ አውቅና እንዲያገኝ ካደረጉ መመዘኛዎች አንዱ መሆኑን አቶ ተኽላይ አስረድተዋል።

“የዓለም ጤና ድርጅት ባካሄደው የዳሰሳ ጥናት መሰረት ለትግራይ ክልል እውቅና የሰጠ ሲሆን በመጪው መስከረም 5 ቀን 2010 ዓ.ም የድርጅቱ ተወካዮች ወደ ክልሉ መጥተው የዕውቅና ሸልማት እንደሚያበረክቱም ተናግረዋል።

 

ምንጭ፦ ኢዜአ