Artcles

ጥልቅ ተሃድሶውና የፀረ-ሙስና ትግሉ

By Admin

August 10, 2017

ጥልቅ ተሃድሶውና የፀረ-ሙስና ትግሉ

                                                            ታዬ ከበደ

አገራችን በአሁኑ ወቅት እያካሄደች ያለችው ጥልቅ ተሃድሶ የማይቋረጥ ተግባር ነው። የፀረ-ሙስና ትግሉ የጥልቅ ተሃድሶው አካል ብቻ ሳይሆን መንግስት ጥልቅ ተሃድሶው ሲጀመር ለህዝቡ የገባውን ቃል እያረጋገጠ ያለበት መንገድ ነው። የጥልቅ ተሃድሶው ተግባር የአንድ ወቅት ስራ አይደለም። ዛሬ የሚካሄደው ተሃድሶ የትናንቱ ቅጣይ ነው።

ምናልባት የዚህ ፅሑፍ አንባቢ እንደሚያስታውሰው የዛሬ 15 ዓመት ገደማ ድርጅቱን ወደ ተሳሳተ አቅጣጫ ሊያመሩ የሚችሉ የኪራይ ሰብሳቢነት፣ የትምክህትና የጠባብነት የዝቅጠት አደጋዎችን በተካሄደው ተሃድሶ ችግሩን መቅረፍ ችሏል። የህዝቡን ሁለንተናዊ ዕድገት ሊያሳልጡ የሚችሉ ዙሪያ መለስ ስትራቴጂዎችም በመንደፍም ዛሬ ለምንገኝበት አስተማማኝ ሰላም፣ ዘላቂ ልማትና ስር የሚሰድ ዴሞክራሲ ዕውን እንዲሆን ተደርጓል።

በእኔ እምነት ይህ የድርጅቱ ተሃድሶ ሀገራችንን አሁን ላለችበት የዕድገት ጎዳና ያበቃት ነው። በወቅቱ በአንድ በኩል ስልጣንን የኢኮኖሚያዊ ሃብትና የብልፅግና መሳሪያ በማድረግ ፀረ-ዴክራሲያዊ ስርዓትን ለመገንባት በሚሹ ወገኖች፤ በሌላ በኩል ደግሞ ስልጣን የሃብት ምንጭ እንዳይሆን፣ ዴሞክራሲያዊ ስርዓቱ እንዲያብብና እንዲዳብር ብሎም የጥገኝነት አስተሳሰብ የበላይነት እንዳያገኝ በሚተጉ ኃይሎች መካከል ከፍተኛ ግምገማና የመድረክ ትግል መካሄዱን እናስታውሳለን።

ታዲያ በድርጅቱ ውስጥ ተፈጥረው በነበሩት በእነዚህ ሁለት ፅንፍ አመለካከቶች ዙሪያ በተካሄዱ ግምገማዊ የሃሳብ ፍጭት፤ ስልጣን የጥቂቶች የሃብት ማካበቻ እንዳይሆን እንዲሁም ዴሞክራሲና ዴክራሲያዊ አንድነት እንዲጎለብት ብሎም የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብ በህብረተሰቡ ውስጥ የበላይነት እንዳያገኝ የታገለው ወገን ነጥሮ በመውጣት ተሃድሶው ግቡን መትቷል፤ ውጤትም አምጥቷል።

እንደ እውነቱ ከሆነ በወቅቱ እንዲህ ዓይነቱ የተሃድሶ ርምጃ በድርጅቱ ውስጥ ባይካሄድ ኖሮ ሀገራችን የምትመራባቸው የሰላም፣ የልማትና የዴሞክራሲ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች እንዲሁም ስልቶች ባልተነደፉ ነበር። በድርጅቱ ውስጥ አቆጥቁጦ የነበረው ፀረ-ዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብም በወቅቱ ከነበረው ሁኔታ ጋር አብሮ ባልከደሰመ ነበር።

ይህ ማለት ግን የፀረ-ሙስና ትግሉ ቆሟል ማለት አይደለም። ሁሌም ባለፉት 15 ዓመታት በህጋዊና አስተዳደራዊ ሁኔታዎች ትግሉ ሲካሄድ ነበር። አሁንም መንግስት በጥልቅ ተሃድሶ ሂደቱ ለህዝቡ በገባው ቃል መሰረት ኪራይ ሰብሳቢነትንና ሙስናን ለመዋጋት ባለስልጣናቱን ሳይቀር ህግ ፊት እያቆመ ነው።

መንግስት ትናንትም ይሁን ዛሬ ያከናወናቸውና የሚያከናውናቸው ተሃድሶዎች ተጨባጭ ውጤቶችን ያመጡ ናቸው። ገዥው ፓርቲ በአሁኑ ወቅት እየተካሄደ ያለው የተሃድሶ ሂደት የመንግስት መዋቅሮችን የህዝቡን እርካታ በሚፈጥሩ መንገድ እያከናወነ ነው።

ይህ ሁኔታም ከዚህ ቀደም በነበሩ የተሃድሶ መንገዶች የተከናወኑ ተግባራትን የሚያጠናክርና ይበልጥ የሚያሰርፅ ነው። መንግስት ለያዘው ቁርጠኛና ውጤት ሊያመጣ የሚችለው ጥልቅ ተሃድሶ ሁሉም የበኩሉን ጠጠር ቢወረውር የሚፈለገው ለውጥ ሊመጣ ይችላል።

እርግጥ በየትኛውም ዴክራሲያዊ ሀገር ውስጥ የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰብና ተግባር ነባራዊ ክስተት ነው። ምንም እንኳን በሀገራችንም መንግሥትና ህዝብ በመገንባት ላይ የሚገኙት ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ገና ለጋ ቢሆንም፤ እንደ ጀማሪ ዴሞክራሲያዊ ሀገር ከዚህ ነባራዊ ክስተት የፀዳንና ጉድለቶች የሉብንም ብሎ ለመናገር አይቻልም።

ለነገሩ የኢፌዴሪ መንግስትና እርሱን የሚመራው ገዥው ፓርቲ ኢህአዴግ ከህዝቡ ጋር በመሆን በየጊዜው በሚወስዷቸው በርካታ ርምጃዎች የኪራይ ሰብሳቢነት አስተሳሰቦች በመጠኑም ቢሆን እየቀረፉ ቢሆኑም፤ የሚፈለገው የአስተሳሰብ ለውጥ ተገኝቷል ማለት አይቻልም።

እንዲያውም አስተሳሰቦቹ እየገነገኑ ጫፍ ላይ እየወጡ ይመስላሉ። በአመዛኙ ኪራይ ሰብሳቢነትንና ሙስናን የሚፀየፍና እንደ ነውር የሚያይ የመንግስት ስራ አስፈፃሚን ብሎም ህዝብን በተሟላ ሁኔታ መፍጠር አልተቻለም።

በሰጪም ይሁን በተቀባይ መካከል ያለው አስተሳሰብ አንድና ተመሳሳይ ነው ማለት ይቻላል። ይህ የሆነውም ካለፉት ስርዓቶች ይዘናቸው የመጣናቸው ፀረ-ዴሞክራሲያዊ ቅሪት አስተሳሰቦች ብሎም ልማቱ የፈጠራቸው አንዳንድ ሁኔታዎች አስተዋፅኦ ያደረጉ ይመስለኛል።

ባለፉት የጥልቅ ጊዜያት ወቅቶች በተካሄዱት ጥልቅ የተሃድሶ መድረኮች አማካኝነት በተሰብሳቢዎቹ አማካኝነት በተገኙት ግብዓቶች ሳቢያ በየደረጃው የተወሰዱት እርምጃዎችም የመንግስትን ቁርጠኝነት አመላካቾች ናቸው። በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ውስጥ በሚገኙ የመንግስት ስራ ፈፃሚዎች ላይ የተወሰዱት የአስተዳደራዊና ህጋዊ እርምጃዎች መንግስት በፀረ-ሙሰና ትግሉ ላይ ምን ያህል ቁርጠኛ አቋም እንዳለው የሚያሳዩ ናቸው።

ይህ የመንግስት ቁርጠኛ አቋም መንግስት ዛሬም እንደ ትናንቱ ቃሉን የማያጥፍና ሁሌም የሚያካሂደው ተሃድሶ በውጤት የሚታጀብ መሆኑን ያሳየ ነው። መንግስት ትናንትም ይሁን ዛሬ ያከናወናቸውና የሚያከናውናቸው ተሃድሶዎች ተጨባጭ ውጤቶችን ያመጡ ናቸው።

መንግስት በአሁኑ ወቅት እየተካሄደ ያለው የተሃድሶ ሂደት የመንግስት መዋቅሮችን የህዝቡን እርካታ በሚፈጥሩ መንገድ እያከናወነ ነው። ይህ ሁኔታም ከዚህ ቀደም በነበሩ የተሃድሶ መንገዶች የተከናወኑ ተግባራትን የሚያጠናክርና ይበልጥ የሚያሰርፅ ነው።

ይህ የመንግስት የተሃድሶ ቁርጠኛ አቋም በህዝቡ ሁለንተናዊ ተሳትፎ መጎልበት አለበት። ኪራይ ሰብሳቢዎችንና መዝባሪ ሙሰኞችን ህዝቡ በሚገባ ያውቃቸዋል። ከህዝብ ዓይን የሚሰወር ምንም ዓይነት ተግባር ባለመኖሩ መንግስት እያካሄደ ላለው ቁርጠኛ አቋም ህዝብ የማይተካ ሚና አለው።

ህዝቡ በኪራይ ሰብሳቢነትና በሙስና ላይ የሚሳተፉ አካላትን በሚገባ ያውቃቸዋል። እነማን ከማን ጋር ግንኙነት እንዳላቸው፣ የትስስር ሰንሰለታቸው እስከየት ድረስ እንደሆነ፣ በምን ዓይነት ቁርኝት እንደሚጠቃቀሙ ከእርሱ የሚሰወር አይደለም።

እናም የኪራይ ሰብሳቢነትንና የሙስናን አደጋ በመገንዘብ የተለመደውን ትብብር ማድረግ ይኖርበታል። የኪራይ ሰብሳቢነትና የሙስና ችግር ግለሰብን፣ ቤተሰብን፣ አካባቢን እንዲሁም አገርን በከፍተኛ ደረጃ የሚጎዳ ነው። ህዝቦች በልማቱ ላይ ባደረጉት አስተዋፅኦ ልክ ተጠቃሚ እንዳይሆኑ በማድረግ የጥቂቶች ሲሳይ ተመልካች እንዲሆኑ ያደርጋል።

ሰው በአገሩ ሰርቶ እንዳይኖር እንቅፋትም ይሆናል። ይህን እንቅፋት ከመንገድ ላይ ዞር ማድረግ ያስፈልጋል። እናም መንገስት ባቀጣጠለው የፀረ-ሙስና ትግል ውስጥ በንቃት በመሳተፍ የጥልቅ ተሃድሶውን ሂደት እውን ማድረግ ይገባል።