Artcles

የመስኖ ልማትና ስራ ፈጠራው

By Admin

January 31, 2018

የመስኖ ልማትና ስራ ፈጠራው

ዳዊት ምትኩ

በአገራችን የመስኖ ልማት ከዚህ ቀደም በተሰሩት ስራዎች ወጣቶች ተጠቃሚ ሆነዋል። በተለይ አዲሱ የመስኖ ልማት ዕቅድ ከወጣ በኋላ ወጣቶች የሥራ ዕድል ማግኘት ችለዋል። በተጨማሪም በመስኖ ልማት ተጠቃሚ የሆነው አርሶ አደር እና አርብቶ አደር በህይወታቸው ላይ ተጨባጭ ለውጥ እያስመዘገቡ ነው።

የመስኖ ልማት በተለይ የተፋሰስ ስራዎች የግብርናው ዘርፍ መሰረቶች ናቸው። በአሁኑ ወቅት አርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ ኑሮው እንዲሻሻል ተገቢ ትኩረት አግኝቷል። ለዚህም በቂ ማሳያዎችንም ማቅረብ ይቻላል። መንግሥት የዘመናት ቁጭቱን አገራዊ መሠረት ባላቸው አቅጣጫዎች የመፍታት ትግሉን እያካሄደ ነው። አርሶ አደሩ ከራሱ ተርፎ ለገበያ በማምረት ተጠቃሚ የሚሆንበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ፣ ሀገሪቱም ከግብርናው ዘርፍ ማግኘት የሚገባትን ጥቅም እንድታገኝ ለማድረግ የሚያስችል የለውጥ ጎዳና ላይ መሆኗን አረጋግጧል።

በአርሶ አደሩ እጅ እንዳለ የሚታሰበው መሬት አነስተኛ ነው። ከዚህም በተጨማሪ ካለችው መሬት የሚያገኘው ምርት ዝቅተኛ ነው። ይህን መንግሥት በሚገባ በመገንዘቡ ዘርፈ ብዙ የማሻሻል ጥረቶች አድርጓል። በውጤቱም አነስተኛ ይዞታ ያላቸው አርሶ አደሮችን ይዞ ለውጥ  ማምጣት አይቻልም የሚለውን አስተሳሰብ መስበር ችሏል።

አርሶ አደሩ የለውጥ መስመሩን ተረድቶ በእምነት ወደ ሥራው በመግባቱ በዓመት ሁለቴና ከዚያም በላይ ለማምረት ችሏል። እንዲሁም በከርሰ ምድርና በገጸ -ምድር ያለውን የውኃ ሃብት የመጠቀም ሰፊ ተግባር አከናውኗል።

በውኃ ማሰባሰብና ማቆር፣ የጉድጓድ ውኃን በመጠቀም የወንዝ ውኃን ጠልፎ ጥቅም ላይ በማዋል ብዙ ርቀት ተጉዟል። በመሆኑም አርሶ አደሩ ከራሱ ፍጆታ አልፎ ለከተማው ነዋሪዎች ከፍተኛ ፍላጎት የሆኑትን ምርቶች ማቅረብ ችሏል። ከነዚህ ውስጥ የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶች በግንባር ቀደምነት ተጠቃሽ ናቸው።

ከዝናብ ጥገኝነት በተላቀቁ አመራረት የተገኙትን ምርቶች መጠቀምም እየተቻለ ነው። የመስኖ ልማት ሥራው በበጋ የበቆሎ እሸት ተመጋቢዎች እንዲሆን አስችሎናል። ባለፉት ሁለት ዓመታት ደግሞ ሥራው ከሁለት እጥፍ በላይ አድጓል።

ለአርሶ አደሩም በዚያው ልክ ገበያው ተመቻችቷል። አርሶ አደሩ በራሱ ባቋቋማቸው የአርሶ አደሮች የህብረት ሥራ አማካይነት ምርቱን ለገበያ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረበ ተጠቃሚ መሆን ጀምሯል። በዚህም ተጠቃሚነቱን እያረጋገጠ ነው።

የግብርናው ዘርፍም በአስተማማኝ ሁኔታ ገበያው ሳያሳስበው ምርትና ምርታማነቱን በማሳደግ ላይ ብቻ አተኩሮ ለልማት ለውጥ ሽግግሩ ምቹ ሁኔታ የሚፈጥርበት ደረጃ ላይ ደርሷል ማለት ይቻላል። ለዚህም በአሁኑ ወቅት በተለይ ወጣቱን ተጠቃሚ በማድረግ ላይ የሚገኘው የተፋሰስ ስራ ውጤታማነቱ ተረጋግጧል።

መንግስት በተቀናጀና በተናበበ መልኩ ጉልበት ሳይባክን ጥራቱን የጠበቀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በየደረጃው እያከናወነ ነው። ይህም አካባቢያዊ ጠቀሜታዎችን ከማረጋገጥ ባሻገር ሀገሪቱን ብሎም ዓለምን እያሰጋ ያለውን የአየር ንብረት ለውጥ ችግር ለመቋቋምና ለመላመድ የበኩሉን ድርሻ ያበረክታል።

የግብርናው ዘርፍ እየዘመነ ትርፍ አምራች አካባቢዎች በድርቅ ለተጎዱት እንዲደርሱ እንዲሁም ድርቅ የሚያጠቃቸው አካባቢዎችም አምራች እንዲሆኑ የሚያስችል ነው። በእኔ እምነት ይህ ሁኔታ በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ የመምታት ያህል ነው።

በአሁኑ ወቅት ለግብርናው ምቹ የሆኑ ሁኔታዎች እየተፈጠሩ ናቸው። በተቀናጀ የተፋሰስ ስራዎች አማካኝነት መገኘት የሚገባው ምርትና ምርታማነትም ያድጋል። ርግጥ በዚህ ረገድ ባለፉት ጊዜያት በተከናወኑት ስራዎች ብዙ ርቀት መሄድ የተቻለ ይመስለኛል።

በተለይም በውኃ ማሰባሰብና ማቆር፣ የጉድጓድ ውኃን በመጠቀም የወንዝ ውኃን ጠልፎ ጥቅም ላይ በማዋል ብዙ ርቀት ተጉዟል። በመሆኑም አርሶ አደሩ ከራሱ ፍጆታ አልፎ ለከተማው ነዋሪዎች ከፍተኛ ፍላጎት የሆኑትን ምርቶች ማቅረብ ችሏል። ከነዚህ ውስጥ የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶች በግንባር ቀደምነት ተጠቃሽ ናቸው።

ከዝናብ ጥገኝነት በተላቀቁ አመራረት የተገኙትን ምርቶች መጠቀምም እየተቻለ ነው። የመስኖ ልማት ሥራው በበጋ የበቆሎ እሸት ተመጋቢዎች እንዲሆን አስችሎናል። ባለፉት ዓመታት ሥራው ከሁለት እጥፍ በላይ አድጓል። ወጣቶችም በተለይ በተፋሰስ ስራዎች ተጠቃሚ እየሆኑ ነው።

የአገራችን ወጣቶች ባለፉት 16 የፈጣን ዕድገት ዓመታት ውስጥ የመንግስት ልማታዊ አቅጣጫን በሚገባ ተገንዝበዋል። ማንኛውንም ጊዜያዊ ችግር መንግስት እየፈታው ነው። በአንዳንድ ክልሎች ውስጥ ማልማት ካልቻሉ ባለሃብቶች ቦታ በመቀማት ጭምር ወጣቶችን ወደ ስራ የማስገባት ተግባር እያከናወነ ነው። ውጤትም እየተገኘበት ነው። ይህ ሁኔታም መንግስት ምን ያህል ለወጣቱ ትኩረት ሰጥቶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ማሳያ ነው ማለት ይቻላል። በሌሎች ክልሎችም ተመሳሳይ ትኩረት የመስጠት ተግባሮች እውን እየሆኑ ነው።

እርግጥ አንድ መንግሥት ወይም የፖለቲካ ድርጅት በባህሪው ህዝባዊ ከሆነ፤ የሚያከናውናቸው ማናቸውም ተግባራት የህዝቡን ተጠቃሚነት ያማከሉ መሆናቸው አይቀርም። የኢትዮጵያ መንግሥትም በባህሪው ህዝባዊና ልማታዊ በመሆኑ፤ ከ26 ዓመታት በላይ በአብዛኛዎቹ መስኮች ህዝቡን በየደረጃው ተጠቃሚ አድርጓል። ዛሬ በተፋሰስ ስራዎች ወጣቶች እንዲጠቀሙ እየተደረገ ያለው ተግባር አብነታዊ አስረጅ ነው።

ቀደም ባሉት ሥርዓቶች በማንነቱም ይሁን በኑሮው አንገቱን ደፍቶ ይሄድ የነበረው ወጣት፤ ዛሬ ቀና ብሎ በአገሪቱ በመመዝገብ ላይ ከሚገኘው ፈጣንና ተከታታይ ዕድገት በኢኮኖሚው ላይ ባበረከተው አስተዋጽኦ መጠን በየደረጃው ተጠቃሚ ሆኖ ወደ አዲስ ምዕራፍ እየገሰገሰ ነው። ይህም በፌዴራላዊ ሥርዓቱ ያስገኘለት ውጤት መሆኑ አይካድም።

መንግስት ቀደም ባሉት ጊዜያት በአገሪቱ ውስጥ ድህነትን አቅም በፈቀደ መጠን በመቀነስ ህዝቡን በየደረጃው ተጠቃሚ እንደሚደርግ፤ ትምህርትን፣ ጤናን፣ የመሠረተ-ልማት አውታሮችን እንደሚያስፋፋ እንዲሁም ዴሞክራሲያዊ ስርዓቱ ስር እንዲሰድ አደርጋለሁ በማለት የገባውን የተስፋ ቃል ተፈፃሚ እያደረገ ነው። የአገሪቱ ኢኮኖሚ ዋነኛ የሆነው ግብርና ለወጣቱ ስራ እንዲፈጥርና ወጣቱም ተጠቃሚ እንዲሆን እየተደረገ ነው። ወጣቶች ይህ ተጠቃሚነታቸውን ያስገኘላቸው ሥርዓቱ መሆኑን ማወቅ ይኖርባቸዋል።

ሥርዓቱ የእርሱ እንደ መሆኑ መጠን ሊጠብቁት ይገባል። በተለያዩ ጊዜያት እያሰለሱ በየአካባቢው የሚታዩ ግጭቶች መነሻቸውና መድረሻቸው ሥርዓቱን በውል ካለመገንዘብ አሊያም ጥቅማቸውን ለማሳደድ የሚሹ ኪራይ ሰብሳቢ ሃይሎች የሚነሱ መሆናቸው ግልፅ ነው። እናም የእነዚህን ሃይሎች አሉባልታ ባለመስማት በመንግስት ወደ ተዘጋጀላቸው የተጠቃሚነት ማዕድ መጓዝ ይኖርባቸዋል። በተለይ የግብርና ተፋሰስና የመስኖ ስራዎች ጊዜ የማይገድባቸው የአገሪቱ ዋነኛ ስራዎች በመሆናቸው ወጣቶች ይህን ዕድል በመጠቀም ራሳቸውን፣ ቤተሰባቸውንና አገራቸውን መጥቀም ይኖርባቸዋል።