Artcles

መውጫው ቀዳዳ

By Admin

March 27, 2018

መውጫው ቀዳዳ

ዳዊት ምትኩ

በአሁኑ ሰዓት የድርቅ ተጎጅዎች ቁጥር 7 ነጥብ 8 ሚለዩን መድረሱን መንግሥት አስታውቋል። ምንም እነኳን ይህ ቁጥር ቀላል ባይሆንም በቀውስ ውስጥ ሆነን እንኳን የልማት ስራዎቻችን ቀጥለዋል። በአሁኑ ሰዓት መንግስት ለእነዚህ በርካታ ቁጥር የድርቅ ተጎጂ ዜጎች እርዳታ እየቀረበ ነው።

ይህ የሆነው በሰላሙ ወቅት በተገነባው አቅም ነው። ቀውሱ ባይኖር ኖሮ፤ በምን ያህል ሁኔታ ልናግድ እንደምንችልም ይታወቃል። በመሆኑም ቀውስን መቅረፍ ይገባል። የድርቅ ተጋላጭነታችንን ለመቀነስ በችግር ላይ ሆነን ዘላቂ መውጫ ቀዳዳዎችን መፍትሄዎችን እያበጀን ነው።  

አዲሲቷ ኢትዮጵያ በአዲስ የልማት አስተሳሰብ መመራት ከጀመረችበት ጊዜ አንስቶ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት ድርቅ ቢፈጠርም ረሃብ ግን ሊከሰት አልቻለም። ለዚህ ሁት ጉዳዩችን ማንሳት ይቻላል። አንደኛው የአገራችን ህዝቦች የመረዳዳት ባህል ያላቸው መሆኑንና መንግስት ላለፉት 27 ዓመታት ድርቅ ወደ ረሃብነት እንዳይቀየር በመስራቱ ነው።

ትናንት ቢሆን ኖሮ እንኳን እንዲህ ያለ ድርቅ ተከስቶ ይቅርና በትንንሽ የድርቅ ሁኔታም ስንጠቃ እንኳን አገራችን በየጊዜው ለዓለም አቀፍ  እርዳታ ተጋላጭ ነበረች። ይሁንና ይህ አካሄድ አሁን ላይ ተሰብሯል። በአዲሲቷ ኢትዮጵያ ድርቅ ቢከሰትም ወደ ረሃብነት ግን መለወጥ አይችልም። በድርቅ ምክንያት ዜጎች ህይወታቸውን አያጡም። ይህ ሁኔታ የተፈጠረው በተዓምር ሳይሆን መንግስትና ህዝብ ተቀራርበው መስራት በመቻላቸው ነው። በተለይም ኢትዮጰያ ባለፉት 16 ዓመታት ተከታታይና ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ማስመዝገብ በመቻሏ ድርቁን መቋቋም ችላለች።

እንደሚታወቀው ሁሉ በአየር መዛባት ክስተት ሳቢያ በ50 ዓመት ታሪካችን ውስጥ ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ሚሊዩኖች ለድርቅ አደጋ ተጋልጠው በነበረበት ወቅት መንግስት የአንድ ነጥብ አራት ቢሊዩን ዶላር ድጋፍ ለጋሽ ሀገራትን ጠይቆ እንደነበር እናስታውሳለን። ሆኖም ከለጋሾቹ የተገኘው ድጋፍ ይህን ያህል ባለመሆኑ፤ መንግስት በራሱ አቅም ዜጎቹን ለመታደግ ችሏል። ይህም እዚህ ሀገር ውሰጥ ላለፉት ጊዜያት ሲሰሩ በመጡት ልማታዊ ተግባራት የተፈጠረውን አቅም የሚያሳይ ክስተት ሆኖ አልፏል።

በአሁኑ ወቅትም ለድርቅ አደጋ የተጋለጡ ዜጎችን ለመታደግ መንግስት ማናቸውንም ተግባራት ያከናውናል፤ እያከናወነም ነው። መንግስት የችግሩን ስፋትና ጥልቀት አስቀድሞ በመገንዘብ የተፈጠረውን ሁኔታ ለመቋቋም በዜጎችና በኢኮኖሚው ላይ ሊደርስ የሚችለውን  ጉዳት ለማስቀረት የሚያስችል አቅጣጫ ቀይሶ ተግባራዊ እያደረገ ነው።

እርግጥ በተፈጥሮ የአየር መዛባት ምክንያት በሀገራችን የድርቅ አደጋ ሲከሰት አዲስ ነገር አይደለም። ይህ ደግሞ በተፈጥሮ ችግር ምክንያት የሚከሰት ጉዳይ በመሆኑ ምንም ማድረግ አይቻልም። ሆኖም ይህ በየጊዜው ሀገራችንን የሚጎበኛት የድርቅ አደጋ ወደ ረሃብነት እንዳይቀየር መንግስት ብርቱ ጥረት አድርጓል። 7 ነጥብ 8 ሚሊዩን ዜጎች ተጋላጭ ቢሆኑም አሁንም መንገስታዊ ሃላፊቱን በብቃት እየተወጣ ነው።

እንደሚታወቀው ሁሉ ባለፉት ዓመታት የመንግስት ትኩረት ምንም ዓይነት የአየር ንብረት መዛባትና ድርቅ  ቢያጋጥምም፤ ህዝባችን የማይራብበት ሁኔታን በመፍጠር ላይ ሲረባረብ ቆመቆየቱ አይዘነጋም። የኤልኒኖ አደጋ በተከሰተበት ወቅትም አደጋውን በመቀልበስ የልማት አጋር ሀገራትን ድጋፍ እምብዛም ሳያገኝ ችግሩ ወደ ረሃብነት ሳይቀየር መቋቋሙ ይህን ጥረቱን አጉልቶ የሚያሳይ መሆኑን ከማንም የተሰወረ ጉዳይ አይደለም።

እርግጥ ይህ አቅም ዝም ብሎ የተፈጠረ አይደለም። መንግሥት ቀደም ባሉት ጊዜያት የአርሶና የአርብቶ አደሩን ህይወት ለመለወጥ ካከናወናቸው ተገቢ ተግባራት የመነጨ መሆኑ ይታወቃል። መንግሥት የአርሶና የአርብቶ አደሩ ኑሮ እንዲሻሻል ተገቢውን ትኩረት ሰጥቷል። በዚህም አርሶ አደሩ ከራሱ ተርፎ ለገበያ በማምረት ተጠቃሚ የሚሆንበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ፣ ሀገሪቱም ከግብርናው ዘርፍ ማግኘት የሚገባትን ጥቅም እንድታገኝ ለማድረግ የሚያስችል የለውጥ ጎዳና እንዲፈጠር አድርጓል። ለዚህ ስኬት በመንግስት በኩል የተወሰዱት እርምጃዎች በቂ ማሳያዎች ናቸው ማለት ይቻላል።

እንደሚታወቀው ሁሉ ኢትዮጵያ ለእርሻ የሚውል ሰፊ መሬት አላት። ሆኖም በተለያዩ ምክንያቶች በአርሶ አደሩ እጅ እንዳለ የሚታሰበው መሬት አነስተኛ ነው። ከዚህም በተጨማሪ ካለችውም መሬት ቢሆን የሚያገኘው ምርት ዝቅተኛ ነው። አመራረቱም እጅግ ኋላ ቀር ሆኖ ቆይቷል።

እውነታውን የተገነዘበው መንግሥት ዘርፈ ብዙ የማሻሻል ጥረቶች አድርጓል። በውጤቱም አነስተኛ ይዞታ ባላቸው አነስተኛ የአርሶ አደሮችን ማሳ ላይ ለውጥ ማምጣት ችሏል። በአርብቶ አደሩም አካባቢ ተመሳሳይ የፖሊሲ ማሻሻያዎችን በመቅረፅና ቀደ ተግባር እንዲገባ በማድረግ ድርቅ ሊፈጥር የሚችለውን አደጋ በአያሌው መቀነስ ተችሏል።

ጥረቶቹ የአርብቶ አደር የልማት ፓኬጆችን በመቅረፅ፤ አርብቶ አደሩ ከልማዳዊ የአኗኗር ባህል ወጥቶ ወደ ዘመናዊ ህይወት እንዲቀየር፣ ከአርብቶ አደሩ ጋር በመነጋገር ድርቅን በዘላቂነት ለመቅረፍ የሚያስችሉ የመስኖ ልማት ስራዎችን በማስፋፋት ወደ ከፊል አርሶ አደርነት እንዲሸጋገር ብሎም ምርጥ ዝርያዎችን አግኝቶ ተጠቃሚነቱን እንዲያሳድግ፣ የከርሰ ምድርና የገፀ ምድር ውሃዎችን በአግባቡ የማሰባሰብ ስራዎችን እንዲያጠናክር፣ የመሰረተ ልማትና የሌሎች የልማት ዘርፎች ተቃሚ ይሆን ዘንድ በፍፁም ፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የሰፈራ ፕሮግራምን እንዲቀበል፣ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱ እንዲጠናከርና በዚህም ብሔራዊ መግባባት እንዲፈጠር የማድረግ ስራዎችን ከማከናወን አኳያ የሚጠቀሱ ናቸው።

እነዚህ ጉዳዩች ችግሩን ለመወጣት የሚያስችሉ ጥረቶች ናቸው። እንዲሁም በመንግሥት የሚከናወኑ ሌሎች ተግባራት የችግሩ መውጫ ቀዳዳዎች ናቸው።  መንግስት በተቀናጀና በተናበበ መልኩ ጉልበት ሳይባክን ጥራቱን የጠበቀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በየደረጃው እያከናወነ ነው። ይህም አካባቢያዊ ጠቀሜታዎችን ከማረጋገጥ ባሻገር ሀገሪቱን ብሎም ዓለምን እያሰጋ ያለውን የአየር ንብረት ለውጥ ችግር ለመቋቋምና ለመላመድ የበኩሉን ድርሻ ያበረክታል።

የግብርናው ዘርፍ እየዘመነ ትርፍ አምራች አካባቢዎች በድርቅ ለተጎዱት እንዲደርሱ እንዲሁም ድርቅ የሚያጠቃቸው አካባቢዎችም አምራች እንዲሆኑ የሚያስችል ነው። በእኔ እምነት ይህ ሁኔታ በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ የመምታት ያህል ነው። በአሁኑ ሰዓት ለግብርናው ምቹ የሆኑ ሁኔታዎች እየተፈጠሩ ናቸው። በተቀናጀ የተፋሰስ ስራዎች አማካኝነት መገኘት የሚገባው ምርትና ምርታማነትም ያድጋል። እርግጥ በዚህ ረገድ ባለፉት ጊዜያት በተከናወኑት ስራዎች ብዙ ርቀት መሄድ ተችሏል። በተለይም በውኃ ማሰባሰብና ማቆር፣ የጉድጓድ ውኃን በመጠቀም የወንዝ ውኃን ጠልፎ ጥቅም ላይ በማዋል ብዙ ርቀት ተጉዟል። እነዚህ ተግባሮች ከተለመደው ቀደምት አሰራር በመውጣት ድርቅን የምንከላከልበትና የችግራችንን መውጫ ቀዳዳ የምንደፍንበት ዓይነተኛ መሳሪያ ሆነዋል።