Artcles

የሰላም ተምሳሌት!

By Admin

May 04, 2018

የሰላም ተምሳሌት!

ነጻነት አምሃ

የአፍርካ አህጉር ሁከት የማይለይበት ከባቢ በመሆኑ ለበርካታ ዓመታት በሰላም እጦት ህዝቦች ሲታመሱና  አስፈላጊ ላልሆነ ስቃይና እንግልት ሲዳረጉ ሲሰደዱ መኖራቸው የታሪክ ማህደራት ያስነብባሉ፡፡ ቀጠናው አሁንም ቢሆን ሰላም የሰፈነበት አይደለም፡፡ የአንዱ አገር ችግር ሲቋጭ የሌላው አጎራባች አገር እየተነሳ በቀጠናው ዘላቂ ሰላም እንዳይሰፍን ልማት እውን እንዳይሆን መሰናክል ሆኖ ኖሯል፡፡

ምንም እንኳን ሁኔታው እየተቀየረ ቢመጣም  አሁንም አስተማማኝ ነገር አለ ለማለት ይቸግራል፡፡ ዘላቂ ሰላም በማረጋገጥ ረገድ ኢትዮጵያ የማይተካ ሚና እንዳላት በርካቶች  ይናገራሉ፡፡ አንዳንዶቹ የሰላም አምባሳደር ብለው ፈርጀዋታል፡፡ በቀጠናውም ሆነ ለአህጉሪቱ ለሰላም ሲባል እየከፈለች ያለው መስዋእትነት በሁሉም ወገን ተቀባይነትን ያገኘ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት  የአፍሪካ አገራት የኢትዮጵያን ሰላም አስከባሪነትን የሚመርጡበት አጋጣሚ እያደገ መጥቷል፡፡ ይህ ደግሞ አገሪቱ ለሰላምና ለልማት ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው፡፡

ለሰላም የተሰጠው ትኩረት ከፍተኛ ነው፡፡ ይህ አገሪቱ ከድህነት ለመላቀቅ ካላት ፍላጎት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ ከድህነት ለመላቀቅ ልማትን እውን ማድረግ ልማትን ለማረጋገጥ ደግሞ ሰላምን ማረጋገጥ የግድ ይላል፡፡

ባለፉት ሃያ ሰባት ዓመታት በአገሪቱ ሰላም በመረጋገጡ አገሪቱ በትክክለኛ የእድገት ምህዋር እንድትሽከረከር አድርጓታል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የታየውን የሰላም መዋዠቅም ቢሆን ከመንግስትና ከህዝቢ ቁጥጥር ውጭ ነው ለማለት አያስደፍርም፡፡   በአገሪቱ ሰላም እደፈረሰ መጣ ሲባል የህዝብን የዕለት ተለት እንቅቅስቃሴ በሚገታ ደረጃ መድረስ አለመድረሱን መገንዘብ የግድ ይላል፡፡

ባለፉት ሃያ ሰባት ዓመታት የታየው ነገር አገራችን የውስጥ ሰላሟን በማረጋገጥ ረገድ ያደረገችው ጥረትና የቀጠናውን ሰላም በማረጋገጥ ረገድም የነበራትን ሚና ከመገንዘብ ይጀምራል፡፡  

በ1983 ዓ/ም ደርግ ስርኣት ተደምስሶ ኢሀአዴግ ወደ ስልጣን በመጣበት ወቅት አገሪቱ በቀደሙት አስራ ሰባት ኣመታት በእርስ በርስ ደም መፋሰስ ይደርስባት ከነበረው ውድቀትና ኪሳረሰ የከፋ ሁኔታ ይገጥማታል የሚል እምነት በበርካቶች ዘንድ ነበር፡፡ ትፈራርሳለች ህዝቦችዋም በጦርነት ይማገዳሉ ኢትዮጵያ የሚትባል አገር አትኖርም ሲሉ የተነበዩ ተንታኞች ቁጥር ቀላል አልነበረም፡፡

ያ ወቅት አንድ ወሳኝ ምዕራፍ ነበር፡፡ በዚያን ወቅት ሁለት አማራጮች ነበሩ፡፡ አንዱ ወደሁከትና ብጥብጥ መዘፈቅና መበታተን ሌላው ደግሞ ሁሉም ብሄሮች ብሄረሰቦችና ህዝቦች የሚያሳትፍ ሕገመንግስት በመንደፍ በማሳተፍ አገርን ማረጋጋት ነበር፡፡ ትበታተናለች የሚለው ሃሳብ  ሚዛን የሚደፋ የነበረ ቢሆንም አደጋው በህዝቦች አንድነት መጠናከር ተቀይሮ አይተናል፡፡

ከዚያም የአገሪቱ ልማት እየተስፋፋ የአገሪቱ ምጣን ሃብትም እያደገ መጣ፡፡ የነበረው ስጋት  ለበለጠ መስፈንጠሪያ ሆነ፡፡ ከራሷ ሰላም አልፋ የቀጠናውን ሰላም ማረጋገጥ የምትችል ሃገር ሆነች፡፡  

የውስጥ ሰላምና መረጋጋትን በማረጋገጥ በአፈሪካ ሰላምን ለማስፈን አስካሁን ድረስ እያደረገች ያለው  ጥረተና ከዚሁ ጋር ተያይዞ የተመዘገበው ስኬት የዓለም መንግስታት ድርጅት ሳይቀር እያረጋገጠ ነው፡፡አሁንም በአገር ውስጥ ያለውን ሰላምና መረጋጋት በአስገተማማኝ መንገድ ማረጋገጥ  በሚያስችልና በአህጉሪቱ ሰላም የማስፈን ጥረት የጎላ አስተዋጽኦ ማድረግ በሚያሰችላት መልክ በመንቀሳቀስ ላይ ትገኛለች፡፡

ሆኖም ግን አንዳንድ  የአገር ውስጥና የውጭ ሃይሎች የአገሪቱን ሰላም ለማደፍረስ ያልበጠሱት ቅጠል ያልፈነቀሉት ድንጋይ አልነበረም፡፡ ይህ እኩይ ምግባር በተለይ ባለፉት አራትና አምስት ዓመታት ተጠናክሮ ቀጥሎ እንደነበር ይታወቃል፡፡  ከዚያ በፊትም ቢሆን የሃይማኖት ሽፋን ይዞ በተለያዩ አካባቢዎች ሁከትና ብጥብጥ በመፍጠር የአገሪቱን ልማት ለማደናቀፍ ታቅዶ የተሰራበት ሁኔታ እነደነበር ግልጽ ነው፡፡

ሆኖም ግን ህዝብ ከመንግስት ጋር በመተባበር ሰላማቸውን ለማረጋገጥ ያላሳለሰ ጥረት ተደርጓል፡፡  ጥረቱም ፍሬ አፍሪቷል፡፡ በአገሪቱ በሰፈነው ሰላም ምክንያት የኢኮኖሚ እድገቱ ተፋጥኗል፡፡ ቀላል የማይባል ቁጥር ያላቸው ዜጎችም በየደረጃው ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡ አገሪቱ የውስጥ ሰላሟን ከማረጋገጥ ባሻገር በቀጠናው የሰላም አምባሳደር ሆና እያገለገለች መምጣቷን በተጨባጭ ታይቷል፡፡

የአፍሪካን ሰላም ለማረጋገጥ በሚታደርገው ሁለንተናዊ ጥረት በርካቶችን ታድጋለች፡፡ ሰላምን የማስከበር ተግባር የጀመረችው በሃይለስላስ መንግስት ሲሆን ከዚያን ወቅት ጀምሮ በቀጠናው ብሎም በአፈሪካ አህጉር ሰላም የማስፍን ተግባርዋን  እያጠናከረች መጥታ በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ ቀዳሚውን ስፍራ ይዛ ትገኛለች፡፡

ከዚሁ ጎን ለጎን ድህነትን ታሪክ ለማድረግና ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ የሚታደርገው ሁለንተናዊ ጥረት ከሰላም ውጭ የማይሳካ በመሆኑ ለሰላም ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ይገኛል፡፤

የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ ሃይል በተለያዩ አገራት ተሰማርቶ የፀጥታና ደህንነት ሽፋን በመስጠት ተልእኮውን ባስተማማኝ መንገድ ሲወጣ ቆይቷል፡፡ ሰላም አስከባሪ ሰራዊታችን ሰላምንና ፀጥታን ከማስጠበቅ ጎንለጎን ለህብረተሰቡ የጎላ ፋይዳ ያላቸው የልማት ተገባራትን እንደሚያከናውን በርካቶች ይመሰከሩለታል፡፡ ለአብነት ያህል በኮንጎ በሩዋንዳ በብሩንዲ እንደዚሁም በላይበሪ በመሰማራት ተልእኮውን መወጣቱ ማውሳት ይቻላል፡፡  

የውጥ ሰላሟን በአስተማማኝ መንገድ በማረጋገጥ በአፍሪካ አህጉር ያለውን ሁከትና ብጥብጥ ለማርገብ በሚደረገው ጥረት ተኪ የሌለው ተሳትፎዋን በመቀጠል አሁንም በሶማሊያና በሱዳን ሰላም የማስከበር ተግባር አጠናከራ ቀጥላለች፡፡ የሶማሊያ ህዝብ በእርስ በርስ ጦርነት በገባበትና በአገሪቱ ሰላምና መረጋጋት ጠፍቶ ሁከትና ሽብር በተንሰራፋበት ወቅት ህዝቡ የዕለት ተለት ኑሮውን ለመምራት የማይችልበት ሁኔታ በተፈጠረበት ወቅት ክፍተቱን ለመድፍን ኢትዮጵያ ተኪ የሌለው መስዋእትነት ከፍላለች፡፡  አሁንም እየከፈለች ትገኛለች፡፡

ከጎርቤት አገራት ጋር በጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ መደጋገፍና ትብብር በማድረግ ሰላማዊ  በቀጠናውም ሆነ በአህጉሪቱ የሚፈጠሩ ግጭቶችን በመፍታት ረገድ ያላሳለሰ ጥረት በማድረግ ላይ ትገኛለች፡፤ በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ ሰላምና መረጋጋት መፈጠሩ ብቻ ሳይሆን በመላው አፍሪካ ሰላምን እውን ለማድረግ ኢትዮጵያ የላቀ ሚና ያላት አገር ለመሆኗ ሁሉም የሚመሰክረው ሆኗል፡፡

የታሪክ መዛግብት እንደሚያመለክቱት እስካሁን ድረስ ከ35 ሺህ በላይ የሰላም አስከባሪ ሃይል በአህጉሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች በተከሰቱ ግጭቶችና ውጥረቶች በማሰማራት ተልዕኮዋን በሚገባ ተወጥታለች፡፡ በተለያዩ አገራት በተለያየ ጊዜ የተሰማራው የአገሪቱ የሰላም አስከባሪ ሃይል በወታደራዊ ዲስፒሊን ታንጾ የተሰጠውን ሃላፊነት በሚያኮራ መንገድ መፈጸሙን  አሁንም በተመሳሳይ መልክ እየፈጸመ መምጣቱ የሚያበረታታ ተግባር ነው፡፡

የአገሪቱ ቁመና  አሁንም በቦታው እንዳለ ነው፡፡ አገሪቱ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሰላም መደፍረስ በአንዳንድ አካባቢዎች እያጋጠሟት የመጡ ቢሆንም ችግሮችን መልክ በማስያዝ ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ በሚስችል ቁመና ላይ ትገኛለች፡፡ በያዝነው ዓመት በተደረገ ተከታታይ ግምገማ መንግስት ማስተካከያ በማድረግ አገሪቱ ሰላምና አንድነቷን ለማጠናከር የሚያስችሉ የተለያዩ ጥረቶች ተከናውነዋል፡፡ ጥረቶቹ ውጤታማ እየሆኑ መመጣታቸው መመስከር ይቻላል፡፡

በዚህ ምክንያት አገራችን የሰላም ተምሳሌት በመባል በሌሎች አገራት በአብነት ተጠቃሽ ሆናለች፡፡  አሁንም ቢሆን ቀደም ሲል በአገር ውስጥ በአንዳንድ አካባቢዎች የተፈጠሩ ችግሮችን በመቅረፍ ዘላቂ ሰላሟን በማረጋገጥ የህዝቦቿን አንድነት በማጠናከር ጎዞዋን ቀጥላለች፡፡  ለወደፊቱም በቀጠናም ሆነ በአፍሪካ ደረጃ የሰላም ተምሳሌትነትነዋን የበለጠ አጠናክራና መልካም ስሟን ጠብቃ ወደፊት እንደምትጓዝ የበርካቶች እምነት ነው፡፡