Artcles

ድርብርቡ ኃላፊነት

By Admin

June 19, 2018

ድርብርቡ ኃላፊነት

                                                              ደስታ ኃይሉ

ሚዲያዎች አሁን በነፃነት እየሰሩ ያለበት ሁኔታ በመፈጠሩ የህዝብ ዓይንና ጆሮ ሆነው በሃቅ ተግባራቸውን ለመወጣት ራሳቸውን ማዘጋጀት ይጠበቅባቸዋል። የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ እንዳሉት፤ ሚዲያ አራተኛው መንግስት (The Fourth Estate) በመሆን የህብረተሰቡን ችግሮች ነቅሶ እያወጣት የሚጠበቅበትን አገራዊ ሃላፊት በብቃት መወጣት አለበት።

ከዚህ በተጨማሪ ለተፎካካሪ ፓርቲዎች እኩል ሽፋን በመስጠት ተግባሩን መወጣት ይኖርበታል። በአሁኑ ወቅት ከውጭ የሚገቡ ኃይሎች ቁጥራቸው እየጨመረ የመጣው የፖለቲካ ምህዳሩ በመስፋቱ ምክንያት ስለሆነ፤ ሚዲያው ለምህዳሩ መስፋት ድርብ ድርብርብ ኃላፊነት ያለበት በመሆኑ ተግባሩን በትክክለኛነት፣ በሚዛናዊነትና በእኩልነት መንፈስ በመወጣት ለዴሞክራሲው መጎልበት የበኩሉን ሚና ማበርከት አለበት።

እንደሚታወቀው ሁሉ የየትኛውም ሀገር ልማታዊ ዴሞክራሲያዊ መንግስት ልማትን ማፋጠንና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን የመገንባት አቅጣጫን የሚከተል ነው፡፡ ለዚህም ስኬታማነት የመገናኛ ብዙሃን ሚና ከፍተኛ እንደሆነ ያምናል፡፡ ይህ እውነታም በዘፈቀደና በአሉባልታ እንደሚወራው ሳይሆን ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መንግስታት ለፕሬስ ነፃነት ያላቸው ቦታ ከፍተኛ እንደሆነ ያስረዳል፡፡

ከዚህ አኳያ የሀገራችንን ነባራዊ ሁኔታ ስንመለከት፤ የተቀናጀ የመገናኛ ብዙሃን ባለቤትነት የሚከተል፣ የመገናኛ ብዙሃኑ ሚና ደግሞ ለልማቱ መፋጠንና ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ባህል ግንባታ የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ የሚያስችል ዕድል ከመቼውም ጊዜ በላይ ተፈጥሯል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትራችን በተለያዩ ወቅቶች እንደተናገሩት በኢትዮጵያ ውስጥ ዛሬ የሚዲያ በር ክፍት ሆኗል፡፡ ይህን ምቹ ምህዳር መጠቀም የመገናኛ ብዙሃኑ ተግባር ነው፡፡

መንግስት እያደረገ ያለው በህገ መንግስተ ላይ የተቀመጠውን የፕሬስ ነፃነትን ማስፋት ነው። ህገ ምንግሰታዊ መሆንን ነው። እነደሚታወቀው ሁሉ በህገ መንግሥቱ አንቀጽ 29 ንዑስ አንቀጽ 4 ላይ የፕሬስ ነፃነትን በተመለከተ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት አስፈላጊ የሆኑ መረጃዎች፣ ሃሳቦችና አመለካከቶች በነጻ መንሸራሸራቸውን ለማረጋገጥ ሲባል፤ ፕሬስ በተቋምነቱ የአሰራር ነፃነትና የተለያዩ አስተያየቶች የማስተናገድ ችሎታ እንዲኖረው የህግ ጥበቃ ይደረግለታል፡፡

ይህም ሀገሪቱ ከምትከተለው የፈጣን ልማትን የማረጋገጥ ጥረትና ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታው መፋጠን ሚዲያዎች የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ያስችላቸዋል፡፡ በአዲሲቷ ኢትዮጵያ ውስጥ ልማትን ማረጋገጥ አገራዊ ህልውናን የማስጠበቅ ጉዳይ ነው፡፡

ከዚህ በተጨማሪ የዘመናት የህዝብ ጥያቄ የሆነው የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታን ማፋጠንም ከልማቱ ጋር አብሮ የሚታይ ህልውናን የማረጋገጥ ጉዳይ ነው፡፡

ስለሆነም የአገራችን ሚዲያዎች ሚና እና የአሰራር ፍልስፍና ከነባራዊው አገራዊ የለውጥ ፍላጎታችንና በጠንካራ አንድነት ላይ የተመሰረተ ኢትዮጵያዊነትን እውን ለማድረግ ያለመ ነው፡፡

ሚዲያዎች እንደ አራተኛው የመንግስት አካል ተደርገው የሚታዩ ስለሆኑ በሀገራችን ውስጥ የሚታዩትን የመልካም አስተዳደርና የሙስና ችግሮችን በምርመራ ጋዜጠኝነት የአዘጋገብ ስልት በመጠቀም ለአገራቸው ሙያዊ ድጋፋቸውን መወጣት ይኖርባቸዋል፡፡ እንዳልነለወጥ የሚሹ ሌቦችንና የቀን ጅቦችን ማጋለጥ ይኖርባቸዋል፡፡  

በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ ህዝብ ፍላጎቱ በአንድነት መንፈስ ህዳሴውን ለማሳለጥ የሰላም፣ የልማትና የዴሞክራሲ ባህል ግንባታን እያከናወነ ነው፡፡ ብሔራዊ መግባባት በመፈጠሩም በዶክተር አብይ መሪነት በአዲስ መንገድ እየተጓዘ ነው፡፡

ታዲያ ይህን ተግባር እንዲወጡ ተጠሪነታቸው ለገለልተኛ አካል የሆኑ የብዙሃን መገናኛዎች ባለሙያቸው በሙያቸው እንዲደረጁ፣ ካላስፈላጊ ውሰጣዊ አተካራ እንዲወጡ፣ መጎልበት የሚገባቸውን አገራዊ ጉዳዩችን እንዲያበረታቱ፣ ችግሮችን በተጨባጭ ማስረጃዎች ላይ ተመርኩዘው እንዲያጋልጡ የህዝቡ ዓይንና ጆሮ መሆን አለባቸው፡፡

በህዝብ ገንዘብ የተቋቋሙ ሚዲያዎችም ቢሆኑ ለተፎካካሪ ፓርቲዎች ሙሉ ሽፋን መስጠት ይኖርባቸዋል። ምክንያቱም ፓርቲዎቹን የሚደግፍ ህዝብ ጭምር በሚከፍለው ታክስ የሚንቀሳቀሱ በመሆናቸው ነው።

የግሉ ሚዲያዎችም ቢሆኑ የህዝብን በገሃድ የሚታዩ ችግሮች በመንቀስና ጥልቅ ምርመራ በማካሄድ ከህዝቡ የተሰበሰበው ታክስ በምን ዓይነት ሁኔታ ጥቅም ላይ እንደዋለ መልሰው ለህዝቡ የማሳወቅ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ ታዲያ እነዚህን ኃላፊነቶች በህዝብ ፍላጎት ላይ ተመስርተው በመወጣት ለአገራችን ዴሞክራሲያዊ ስርዓት የድርሻቸውን መወጣት አለባቸው፡፡   

ሚዲያዎች በሚያከናውኗቸው ዘገባዎች ውስጥ ሁሉ የሀገራችንን ህዝቦች ሁለንተናዊ ጥረቶችንና ተስፋዎችን ታሳቢ ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡ አገራችን ለዘመናት አንገቷን ሲያስደፋት የነበረውንና የድህነት አዙሪት ቀለበት ለመቀልበስ የምታደርገውን ጥረት በግንባር ቀደምትነት ሊደግፉ ይገባል፡፡  

ህዝብን ከድህነትና ከኋላ ቀርነት ለማላቀቅ፣ ህዝቡ ፈጣን ሀገራዊ ለውጥን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ትክክለኛ የልማት ሃሳቦችን እንዲገነዘባቸው የሚያደርጉ፣ መልሶ ከራሱ ልማታዊ ተግባሮች እንዲማር የሚያነሳሱ፣ በትግበራቸው ላይም በንቃት እንዲሳተፍ የማነቃቃት ይገባል።

ይህም አዎንታዊ የልማትና የዴሞክራሲ የለውጥ እሴቶችን የማስተጋባት ሚናን መወጣት ይገባቸዋል። ዛሬ ማንም በሃላፊነት ስሜት የፈለገውን እንዲፅፍ ተፈቅዷል። ይህም ሀገራችን የተያያዘችውን የለውጥና የህዳሴ ጉዞ ለማካናወን ዕድል የሚሰጥ ነው።

ሚዲያዎች በአገራችን የሰላም፣ የልማትና የዴሞክራሲ ስራዎች ውስጥ የሚስተዋሉ እንደ መልካም አስተዳደርና የሙስና ዓይነት ችግሮችን እየነቀሱ ማውጣት አለባቸው። በአገሪቱ ውስጥ የሚታዩ ህፀፆችን በተጨባጭ ማስረጃዎችና መረጃዎች ላይ ተመርኩዘው በማጋለጥ የህዝቡን ሁለንተናዊ ፍለጎቶች በመሳካት የድርሻቸውን ያበረክታሉ።

ሚዲያዎች ተግባራቸው ከጥላቻና ከውዳሴ ነፃ በመሆን፤ ትክክለኛ፣ ሚዛናዊ፣ ተዓማኒ ምልከታዎችን በማስተናገድ ለኢትዮጵያችን መልካም መስራት ይኖርባቸዋል። ይህን ድርብ ድርብርብ ሃላፊነት ለህዝባቸውና ለአገራችው ማበርከት ይኖርባቸዋል። ይህም አራተኛው የመንግስት አካል እንዲሆኑ ያደርጋቸዋል።