NEWS

የተለያዩ ሀገራት መሪዎች ኢትዮጵያና ኤርትራ የደረሱትን ስምምነት እያወደሱ ነው

By Admin

July 09, 2018

ኢትዮጵያ እና ኤርትራ ዛሬ የሰላምና የወዳጅነት ስምምነት መፈራረማቸውን ተከትሎ የተለያዩ ሀገራት እና መንግስታት መሪዎች እርምጃውን በማወደስ ላይ ይገኛሉ።

የኬንያው ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ እና የኤርትራው ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ ንግግርን መምረጣቸውን አድንቀዋል።

መሪዎቹ የወዳጅነት መንገድንም በመምረጣቸው አንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል።

የሩዋንዳው ፕሬዚዳንት እና የወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር ፖል ካጋሜ በበኩላቸው፥ መሪዎቹን “ለሁለቱ ሀገራት ህዝቦች ጥቅም የሚበጀውን ውሳኔ በመወሰናችሁ እንኳን ደስ ያላችሁ” ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሼክ አብዱላሂ ቢን ዛይድ አል ነኸያን በበኩላቸው ባወጡት መግለጫ፥ ኢትዮጵያ እና ኤርትራ የዲፕሎማቲክ ግንኙነታቸውን ለመጀመር መስማማታቸው ለሁለቱ ሀገራት ከሚያመጣው ሰላምና ፀጥታ በተጨማሪ ለአፍሪካ ቀንድ በአጠቃላይ አወንታዊ ውጤት እንደሚኖረው አንስተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ እና ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ የወሰዱትን ታሪካዊ እርምጃ በማድነቅም፥ እርምጃው የሁለቱን መሪዎች የፖለቲካ ጥበብና ጥንካሬ የሚያሳይ ነው ብለዋል።

የደረሱት ይህ ታሪካዊ ስምምነት ለሁለቱ ሀገራት በኢኮኖሚ፣ በባህልና ሌሎች ማህበራዊ ዘርፎች ትብብር እድል ይዞ መምጣቱንም ተስፋቸውን ገልፀዋል።

ሀገራቸው የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች ሁለቱ ሀገራት በትብብር ሰላምና ብልፅግናን ለማምጣት የሚያደርጉትን ጥረት እንደምታግዝም አረጋግጠዋል።