NEWS

የቀድሞው የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት ዋና ዳይሬክተር የነበሩት አቶ ጌታቸው አሰፋ የት ናቸው? የእስር ትዕዛዝ ወጥቶባቸዋል?

By Admin

August 24, 2018

 

የቀድሞው የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት ዋና ዳይሬክተር የነበሩት አቶ ጌታቸው አሰፋ የእስር ማዘዣ እንደወጣባቸው እና ከአገር እንደሸሹ አንዳንድ የመገናኛ ብዙኃን በስፋት ሲዘግቡት ሰንብተዋል።

የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) ጽሕፈት ቤት ኃላፊ የሆኑትን ወ/ሮ ፈትለወርቅ ገ/እግዚያብሔርን ስለጉዳዩ ጠይቀናቸዋል።

ወ/ሮ ፈትለወርቅ ”እንደ ድርጅት በዚህ ደረጃ የምናውቀው ነገር የለም። ለድርጅት የክስ መጥሪያ አይመጣም” ይላሉ።

• የደኅንነት መሥሪያ ቤቱ ኃላፊ ከሥልጣናቸው ተነሱ

• አቶ አብዲ ስለተናገሩት ጉዳይ እንደማያውቅ ኢህአዴግ ገለፀ

• መከላከያ የኢህአዴግ የመጨረሻ ምሽግ?

በአንድ የማእከላዊ ኮሚቴ አባል ላይ ድርጅቱ ሳያውቀው ክስ ሊመሠረት ይችላል ወይ ተብለው የተጠየቁት የድርጅቱ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ፤ ”ውይይት የሚያስፈልገው ነገር ካለ ፖለቲካዊ ግምገማና ይደረጋል እንጂ ክስን በተመለከተ የመንግሥት ሥራ ነው የሚሆነው” ሲሉ መልሰዋል።

ኾኖም የአቶ ጌታቸው ጉዳይ በግምገማም እንዳልተነሳ ወ/ሮ ፈትለወርቅ ተናግረዋል።

የኢህአዴግና የሕወሓት የሥራ አስፈጻሚ አባል የሆኑት አቶ ጌታቸው አሁን በተካሄደው የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ እንዳልተገኙ ወ/ሮ ፈትለወርቅ ጠቁመዋል።

የአቶ ጌታቸው በስብሰባው ያለመገኘት ጉዳይ “የእስር ማዘዣ ወጥቶባቸዋል ከሚለው ዜና ጋር የሚያያዝ ነው ወይ?” ተብለው የተጠየቁት ወይዘሮ ፈትለወርቅ ”አንድ ሰው ሰብሰባ ላይ በግል ጉዳይ ላይገኝ ይችላል። በስብሰባዎች ላይ ሁሉም ሰው ይገኛል ማለት አይደለም። የእሱ ከስብሰባ መቅረት ከዚህ ጋር ይገኛል ማለት ላይሆን ይችላል። በሥራ ጉዳይም ላይገኙ ይችላሉ” ይላሉ ወ/ሮ ፈትለወርቅ።

ለመጨረሻ ጊዜ አቶ ጌታቸውን መቼ እንዳይዋቸው ከቢቢሲ የተጠየቁት ወይዘሮ ፈትለወርቅ በቅርቡ ከሁለት ሳምንት በፊት ገደማ መቀሌ እንዳገኟቸው አረጋግጠዋል።

በሌላ በኩል የፌዴራል አቃቢ ሕግ በአቶ ጌታቸው አሰፋ ጉዳይ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥቧል።

BBc