CURRENT

የኤርትራ ወደብን መጠቀም ኢንቨስተሮችን ለመሳብ አቅም ይፈጥራል

By Admin

August 24, 2018

በኢትዮ- ኤርትራ መካከል የተደረሰው የሠላም ስምምነት አማራጭ ወደቦችን ለመጠቀም ሰፊ ዕድል የሚፈጥር በመሆኑ ኢንቨስተሮችን ለመሳብና ማኑፋክቸሪንግ ዘርፉን ለማሳደግ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡

የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዶክተር አምባቸው መኮንን በተለይም ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደገለፁት፤ በሁለቱ አገራት መካከል የተደረሰው የሠላም ስምምነት አማራጭ ወደቦችን መጠቀም የሚያስችል በመሆኑ የኢንዱስትሪን ዘርፍን ለማሳደግ የላቀ ድርሻ ይኖረዋል፡፡

ወደቦች ምርቶቻቸውን ወደ ውጭ ለመላክ ወሳኝ በመሆናቸው የአገር ውስጥም ሆኑ የውጭ ባለሀብቶች በአገሪቱ ኢንቨስትመንት ውስጥ ለመሳተፍ የወደብ አማራጭ አንዱ መስፈርታቸው ነው ያሉት ዶክተር አምባቸው፤ ወደቡን ለመጠቀም ከስምምነት ላይ መደረሱ ኢንቨስተሮች በስፋት እንዲገቡ ያደርጋል፡፡ የአሰብ ወይም የምፅዋ ወደቦች ወደ ሥራ ሲገቡም እንቅስቃሴው የተሻለ ይሆናል ብለዋል፡፡

«በተለይም ቀጣናው እንደ አንድ ገበያ መዳረሻ የሚታይ በመሆኑ ሠላም ሲሰፍን የበርካታ አገሮችን ቀልብ የሚገዛ ይሆናል፡፡ የምጣኔ ሀብት ትስስሩንም በከፍተኛ ሁኔታ ያሳድገዋል፡፡ አገሪቱን የምርትና የኢንዱስትሪ ማዕከል ለማድረግም የላቀ አስተዋፅኦ ይኖረዋል፡፡» ሲሉም ዶክተር አምባቸው ተናግረዋል፡፡

ሚኒስትሩ እንዳሉት፤ በአሁኑ ወቅት ወደ ውጭ የሚላኩና ወደ አገር ውስጥ የሚገቡ ምርቶች በጅቡቲ ወደብ ላይ ብቻ የተንጠለጠሉ ናቸው፡፡ ይህም በኢኮኖሚው ላይ ጫና ፈጥሯል፡፡ ከኤርትራ ጋር የተደረሰው ስምምነት የአሰብና የምፅዋ ወደብ መጠቀም ስለሚያስችል ችግሩን ይቀንሰዋል፡፡ በተለይ ከኤርትራ ባሻገር የሱዳን ወደብን መጠቀም ከተቻለ የተለያዩ የገበያ አማራጮችንና መዳረሻዎችን ለመመልከት ዕድል ይከፍታል፡፡

በክፍለዮሐንስ አንበርብርአዲስ ዘመን ጋዜጣ ነሐሴ 18 ቀን 2010ዓም