NEWS

የኤክስፖርት ማዕቀብ ከተነሳ በኋላ የጥጥ ምርት እየጨመረ ነው

By Admin

August 23, 2018

ዘርፉ በተለያዩ ችግሮች ተተብትቧል

በጥጥ ኤክስፖርት ላይ የተጣለው ማዕቀብ ከተነሳ በኋላ በአገር ውስጥ የሚመረተው ጥጥ መጠን እየጨመረ እንደመጣ ተጠቆመ።

በአገር ውስጥ በተፈጠረ የጥጥ እጥረትና እየጨመረ በመጣው የአገር ውስጥ የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካዎች ፍላጎት ምክንያት፣ በ2002 ዓ.ም. መንግሥትየጥጥ ምርት ወደ ውጭ እንዳይላክ አግዶ ነበር። የኢትዮጵያ ጥጥ አምራቾችና መዳመጫዎች ማኅበር ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ሐዲሽ ግርማይ ለሪፖርተርእንደተናገሩት፣ የአገር ውስጥ ጥጥ አምራቾች ለውጭ ገበያ እንዳያቀርቡ ለስድስት ዓመታት ያህል በመከልከላቸው ጥጥን የማምረት ተነሳሽነት እየተቀዛቀዘበመሄዱ አገራዊ የጥጥ ምርት እያሽቆለቆለ ሄዷል።

ጥጥ በአፋር፣ በአማራ፣ በትግራይ፣ በጋምቤላ፣ በቤንሻንጉል ጉምዝ፣ በኦሮሚያና በሶማሌ ክልሎች ይመረታል። ከስድስት ዓመት በፊት እስከ 100,000 ቶንየተዳመጠ ጥጥ ይመረት የነበረ ቢሆንም፣ ምርቱ እየቀነሰ መጥቶ 30,000 ቶን ድረስ ወርዶ እንደነበር አቶ ሐዲሽ አስረድተዋል።

ከኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ እንደሚያሳየው፣ የጥጥ ምርት ፍላጎት (የጨርቃ ጨርቅና ባህላዊ ሸማኔዎችን ጨምሮ) 70,000 ቶን ይገመታል።በጥጥ ኤክስፖርት ላይ የተጣለው ማዕቀብ ከሁለት ዓመት በፊት በመነሳቱ ተዳክሞ የነበረው የጥጥ አምራቾች ተነሳሽነት እየተነቃቃ መሆኑን የገለጹት አቶ ሐዲሽ፣ ዓመታዊ የጥጥ ምርት ከ30,000 እስከ 40,000 ቶን ወደ 60,000 ቶን ማደጉን ጠቁመዋል።

በዚህ ዓመት ከ100,000 ቶን በላይ የተዳመጠ ጥጥ ይመረታል ተብሎ እንደሚጠበቅ የገለጹት አቶ ሐዲሽ፣ የአገር ውስጥ ፍላጎት በማሟላት ለውጭ ገበያ ማቅረብ እንደሚቻል ገልጸዋል። ‹‹የጥጥ ምርት ለአገርና ለውጭ ገበያ ማቅረብ በመፍቀዱ፣ በርካታ ባለሀብቶች ወደ ጥጥ ምርት እየገቡ ነው። ነባር አምራቾችም እርሻቸውን እያሰፉ ስለሆነ ምርቱ በመጠን ካለፈው ዓመት ጀምሮ እየጨመረ ነው፤›› ያሉት አቶ ሐዲሽ፣ የጥጥ ምርት ዘርፉ በተለያዩ ችግሮች የተበተበ እንደሆነ ተናግረዋል።

በዘርፉ ከሚነሱ ችግሮች መካከል በአገር ውስጥ ያሉ የጥጥ መዳመጫዎች ውስን መሆንና አብዛኛዎቹ ዕድሜ የተጫናቸው መሆናቸው ነው። ካሉት 20 የጥጥ መዳመጫዎች አብዛኛዎቹ ዕድሜያቸው ከ50 ዓመት በላይ በመሆኑ፣ ማሽኖቻቸው እንዳረጁባቸው ገልጸዋል። ‹‹ይህም በሚያመርቱት የተዳመጠ ጥጥ ላይ የጥራት ችግር ይፈጥራል። ከፍተኛ ጥራት ያለው ምርት ለማምረት በጥጥ እርሻዎች አቅራቢያ ዘመናዊ የጥጥ መዳመጫዎች መገንባት ያስፈልጋል፤›› ያሉት አቶ ሐዲሽ፣ ጥጥ አምራቾችና የጥጥ መዳመጫ ፋብሪካዎች ከፍተኛ የፋይናንስ ችግር እንዳለባቸው አስረድተዋል። የመሬት፣ የባንክ ብድር፣ የኬሚካልና የዘር አቅርቦት ችግሮች ዘርፉን እየተፈታተኑ መሆናቸውን ገልጸዋል።

የአገር ውስጥ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካዎች በገጠሟቸው ችግሮች በዱቤ ለወሰዱት የጥጥ ምርት ክፍያ ሳይፈጽሙ በመቅረታቸው፣ ጥጥ አምራቾችን ለከፍተኛ የፋይናንስ ቀውስ እንደዳረጓቸው ተናግረዋል። ‹‹የተዘጉት የቱርክ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካዎች የብዙ ጥጥ አምራቾችን ገንዘብ በቼክ ይዘው ነው የሄዱት፤›› ብለዋል።

የኢትዮጵያ ጥጥ አምራቾችና መዳመጫዎች ማኅበር በጥጥ ዘርፍ ያሉ ማነቆዎችን በዝርዝር አስጠንቶ ለኢንዱስትሪ ሚኒስቴር አቅርቧል።

የጥጥ ዘርፍ የአገር ውስጥ የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካዎችን ፍላጎት አርክቶ ለውጭ ገበያ ማቅረብ ሲቻል ዘርፉን አንቆ የያዙትን የዘር፣ የኬሚካል፣ የቴክኖሎጂ የግብዓት፣ የባንክ የብድር፣ የመሬትና የመሠረተ ልማት ችግሮች በዝርዝር ተጠንተው ለሚኒስቴሩ መቅረባቸውን ማኅበሩ ገልጾ፣ በአምባቸው መኮንን (ዶ/ር) የሚመራው አዲሱ የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር አመራር ጥናቱን በአጽንኦት ተመልክቶ የመፍትሔ ዕርምጃዎች እንዲወስድ ጠይቋል።

‹‹ዘርፉ የአደረጃጀት ችግር አለበት። እንደ ግብዓትና ፋይናንስ ያሉ የፖሊሲ ጉዳዮች በኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ሥር ሲሆኑ፣ የቴክኖሎጂ ጉዳዮች ደግሞ የሚታዩት በግብርናና በእንስሳት ሀብት ሚኒስቴር ነው። የጥጥ ጉዳይ የሚመለከታቸው የተለያዩ መሥሪያ ቤቶች መሆናቸው በራሱ አንድ ችግር ነው፤›› ያሉት አቶ ሐዲሽ፣ ማኅበሩ የመፍትሔ ሐሳቦችን በጥናቱ አካቶ ለኢንዱስትሪ ሚኒስቴር እንዳቀረበ ገልጸዋል።