Ethiopiaprosperous
Ethiopian News Ethiopian Daily news, Regarding political and social Issues.

የባህል ዕሴቶቻችን በመደመር ዕሳቤ ውስጥ

0 570

Get real time updates directly on you device, subscribe now.

የባህል ዕሴቶቻችን በመደመር ዕሳቤ ውስጥ

                                                                 በሞገስ ተስፋ

 

ኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአጭር ጊዜ ውስጥ እያስመዘገበችው ያለው ለውጥ የሚበረታታ እና አስደናቂ ነው፡፡ ከነዚህ ለውጦች መካከል ደግሞ አገራዊ አንድነትን በማጎልበት የለውጥ መስመር መቀየስ ስለሆነ በዚህ ዘርፍ ሠፊ ንቅናቄ በማካሄድ ህዝቡን ባሳተፈ የለውጥ እንቅስቃሴ በነዚህ አጭር ወራት ውስጥ አመርቂ ሥራ ተሠርቷል፡፡ ለዚህ የሥራ እንቅስቃሴ ዋናው መሪ ተዋናይ ዶክተር አብይ አህመድ ከበዓለ ሲመታቸው ጀምረው የአገሪቱ አንድነት እንዲጠናከር ከማድረጋቸው በላይ በዲፕሎማሲው ረገድም ከፍተኛ ስኬት እያስመዘገቡ ይገኛሉ፡፡ ለዚህም ዋነኛው ምክንያት በሀገሪቱ ያለውን የአሠራር ለውጥ በማቀናጀት ይበል የሚያሰኝ ተግባር አከናውነዋል፡፡

የምክር ቤት አመራሮቻቸውን ሥራ ቆጥረው በመስጠት በጊዜ የተወሰነ የሥራ የኮንትራት ውል በመፈራረም ለሚያስመዘግቡት ውጤት መለኪያ በማስቀመጥ ወደ ሥራ እንዲገቡ በማድረግ ረገድ ሚናቸው ከፍተኛ ነበር፡፡ ይህም የሥራ የኮንትራት ውል ባለሙያውን ወይም አመራሩን ስራውን የእኔ ባይነት ስሜት በመፍጠር በተቀናጀና አመቺ በሆነ መንገድ እንዲያከናውኑ የተቀየሰ የአሠራር ፍኖተ ካርታ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ስለሆነም ይህ የአሠራር መስመር መልካም አጋጣሚ ስለሆነ ከፌደራል እስከ ክልል ብሎም እስከታችኛው የቀበሌ መዋቅር ድረስ ወርዶ ተግባራዊ ይሆን ዘንድ የአመራር ቁርጠኝነት ስለሚጠይቅ ሁሉም በየደረጃው ያሉ አመራሮች ተሞክሮውን ወስደው ሊተገብሩት ይገባል፡፡ ነገር ግን ይህ በቂ ስላልሆነ በቀጣይ ማለትም በ2011 ዓ.ም በምክር ቤት ደረጃ የተፈጠረው ሥራን ቆጥሮ የመስጠት ሂደት ተጠናክሮ መቀጠል ይገባዋል፡፡ ምክንቱም ይህ አሠራር ተጠያቂነትን በማስፈን ረገድ ሚናው ከፍተኛ ስለሆነ  ተዋረዱን የጠበቀ የተጠያቂነት ሥርዓት እንዲሰፍን በማድረግ ሁነኛ ሚና ይጫወታል፡፡ ይህ ከሆነ ሀገሪቱ ለምታደርገው ሁለንተናዊ የለውጥ እንቅስቃሴ መልካም የንቅናቄ መፍጠሪያ ዘዴ መሆኑን መዘንጋት የለበትም፡፡

ለውጡ ቀጣይነት ይኖረው ዘንድ የሁሉንም ዜጋ ተሳትፎ ይጠይቃል፡፡ ስለሆነም አገራችን በጀመረችው የለውጥ ሩጫ እንድትቀጥል ሁሉም ዜጋ በእኔ ባይነት ስሜት የየራሱን ድርሻ በመወጣት በምክንያታዊነት ላይ የተመሠረተ ሀሳብ በማራመድ ለእናት አገሩ ጡቡን ማስቀመጥ ይገባዋል፡፡ ምክንያቱም በሀገራችን የተጀመረውን ለውጥ የማይፈልጉ መጥፎ ጥላቻን የሚዘሩ ኃይሎችን ከለውጡ ጎን ለማሰለፍ ርብርብ የሚያደርግበት ወቅት ላይ እንገኛለን፡፡ ይህ ሲሆን ሀገር ዕድገት ይኖራታል፡፡ ሀገር አደገች ማለት ደግሞ ዜጎች በዕድገቷ ተጠቃሚ ይሆናሉ፡፡ ስለዚህ ከለውጡ በተቃራኒው ተሰልፈው የአገርን ለውጥ ለመቀልበስ ነውጥን የሚሰነዝሩ የጥፋት ኃይሎችን በሰከነ መንፈስ እንዲታረሙ ማድረግ ይገባል፡፡ ምክንያቱም እነዚህ የጥፋት ኃይሎች ለመሸጋገሪያና ለማስፈፀሚያ የሚጠቀሙት የትኩስ ኃይል ባለቤት የሆነውን ወጣት ስለሆነ ወላጆች ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ ሲያጨበጭቡ ተቀብሎ ከማጨብጨብ፣ ለማጨብጨብ የሚያስችሉ ምክንያቶችን በማንሳት አስፈላጊነቱንና ምክንያቱን በመለየት ጠቃሚ የሆነ መረጃ መያዝ ተገቢነት አለው፡፡ ይህ ሲሆን ሀገራዊ ፍቅር ያለው ዜጋ ይፈጠራል፡፡ ስለሆነም ለሀገሩ የበኩሉን አስተዋፅዖ በማድረግ ራሱ ተጠቅሞ ሀገሩን የሚጠቅምበት ሁኔታ ይፈጠራል ማለት ነው፡፡

ሥራን ቆጥሮና ተረክቦ ወደ ሥራ የመግባቱ ጉዳይ በዚህ ዓመት በመልካም ጎኑ የሚታይና በቀጣይነት ትልቅ የቤት ሥራ እንደሚሆን መንግት ማስታወቁ ይታወቃል፡፡ በመሆኑም በሚቀጥለው 2011 ዓ.ም በሰፊው መሰራት እንዳለበት በተደጋጋሚ የተገለፀ በመሆኑ በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች መሪ ተዋናይ በመሆን ፍሬያማ ተግባር በማከናወን የህዝቡን ፍላጎት ወቅቱ በሚፈቅደውና አቅም በፈቀደ መጠን ምላሽ ለመስጠት እንዲችሉ ማድረግ ነው፡፡ ይህ ከሆነ በየቀጠናው የሚገኙ ሙያተኞችን ለውጥ ለማምጣት የሚያስችላቸውን ዐቅም በመገንባት ረገድ ከፍተኛ ሥራ መሠራት አለበት፡፡ ስለሆነም በማንኛውም የኅብረተሰብ ክፍል ከለውጥ እንቅስቃሴ በተቃራኒው ቆመው እንቅፋት ለመፍጠርና ለውጡን ለመቀልበስ ሥራዬ ብለው በተሰማሩ ኃይሎችን አደብ መግዛት ይኖርባቸዋል፡፡

በመደመር፣ በይቅርታና በአንድነት መንፈስ የተጀመረውን የለውጥ እንቅስቃሴ ለማደናቀፍ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በመሠማራት የጥፋት ቀመር በመቀመር የሚንቀሳቀሱ አካላት ከዕኩይ ድርጊታቸው ርቀው ፀለምተኝነትን አስወግደው ለሰላም ቢጥሩ አትራፊዎች ይሆናሉ ፡፡ ይህንን ዕኩይ እንቅስቃሴያቸው በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ሃይማኖታዊና ብሔር ተኮር የመሰሉ ጥያቄዎችን ተላብሰው መጠነ ሰፊ የህይወት መጥፋትና የንብረት ውድመት ማስከተሉ ይታወሳል፡፡

ወጣቶች ይህ ክስተት ሀገሪቱ ለጀመረችው የለውጥ መስመር “በእንቅርት ላይ ጀሮ ደግፍ” ነው ብለው ለሚያምኑ የዕኩይ ተግባር ቁማርተኞች ቀቢፀ ተስፋ መሆኑን በመረዳት ከዚህ ተግባራቸው መታቀብ አለባቸው፡፡  መንግሥትም ይህንን ዕኩይ ድርጊት የማይታገስ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በሰጡት ወቅታዊ መግለጫቸው ማሳሰባቸው ይታወሳል፡፡ አክለውም ሀገራችን ለጀመረችው ሁሉን አቀፍ እንቅስቃሴዎች ላይ እንቅፋት የሚፈጥሩ ኃይሎችን ከዚህ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ ማስጠንቀቂያ አዘል መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡ ስለሆነም ለውጡ ግለሰባዊ ወይም የተወሰኑ የኅብረተሰብ ክፍሎችን የሚዳስስ ሳይሆን ሁሉንም ዜጋ የሚያካትት መሆኑን መገንዘብ ያሻል።

ሀገሪቱን መሠረታዊ ህፀጾችን ነቅሶ በማውጣት እመርታዊ ለውጥ (radical change) ለማምጣት የተቀየሰውን የለውጥ ጉዞ  እንቅፋት ለመፍጠር ቢጥሩ በምንም ሁኔታ የማይቀለበስ መሆኑን መረዳት አለባቸው፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞም ከጥፋት ምንም ዓይነት ትርፍ እንደማይገኝ በመገንዘብ ወደ መልካም ተግባር እንዲሸጋገሩ መንግሥት በጥብቅ ያሳስባል፡፡ ስለሆነም ሁሉም ኢትዮጵያዊ ለሀገሩ ዐቅሙ በፈቀደ መጠን የድርሻውን ማበርከት አለበት፡፡

ኢትዮጵያ መጭው ዘመን ብሩህ ይሆንላት ዘንድ ጠንክራ በመሥራት ላይ ትገኛለች፡፡ በመሆኑም ህዝቦቿ በፍቅር፣ በመደመር፣ በይቅርባይነትና በመቻቻል የዳበረ ባህልና ዕሴቶች እንዲኖሯት እንዲሁም እነዚህን አኩሪ ታሪኮች ከትውልድ ትውልድ እንዲተላለፉ ለማድረግ በየጊዜው እየጎለበተ የሚሄድ ተራማጅ ባህል ያስፈልጋል፡፡ ስለሆነም መጭው አዲስ ዓመት የበለጠ የመደመር፣ የአንድነት፣ የይቅርባይነትን ባህል የበለጠ ለማዳበር ብሎም የተጀመረውን የዕድገት ግስጋሴ ግብ እንዲመታ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡ ይህንንም በተለያዩ የበዓላት ሁነቶች አማካኝነት መልካም ዕሴቶቻችን በማዳበር የአብሮነት ከስህቶቻችን በመማር ታላቅ የሆነችውን ሀገር የመገንባት ራዕያችን ዕውን እንዲሆን ጠንክረን መሥራት ያስፈልጋል፡፡ ስለሆነም በዚህ ወቅት የአረፋ፣ የቡሄ በሉ፣ የሻደይ አበባና የአሸንድዬ በዓላት እንዲሁም የዘመን መለወጫ ሀገራዊ አንድነት የማጠናከሪያ ሁነቶች መሆን ይገባቸዋል፡፡ ስለዚህ እነዚህ በዓላት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ አላቸው፡፡

ባህል የአንድ ሀገር ህዝቦች የማንነታቸው መገለጫ፣ የአብሮነታቸው ማሳያ ከመሆኑም ባሻገር የለውጥና የዕድገት ምልክትም ጭምር ነው፡፡ እነዚህ በዓላት ሀገራችን የተለያዩ ባህሎች፣ እምነቶች፣ ቋንቋዎችና ብሔረሰቦች ደሴት እንደመሆኗ መጠን እነዚህን ሀገራዊ በዓላት ስናከብር የመማሪያና የማስተማሪያ እንዲሁም የመረዳዳትና አንዱ ለሌላው ተካፍሎ የመብላት የአጋርነት ማሳያ ሁነቶች ማሳያ የቱሪዝም መስህቦች እንዲከበሩ ዜጎች ከመንግሥት ጋር ተባብረው  ለሰላም ሊቆሙ ይገባል፡፡ በዓላቱ የአንድን ሀገር ብዙሃነትና አብሮነት የመገንባት ዕሴት ከፍ የማድረግ አቅም ያላቸው ናቸው፡፡ ስለሆነም በአግባቡና በተገቢው መንገድ ልንጠቀምባቸው የሚገቡ ዕሴቶቻችን እንደመሆናቸው መጠን ትኩረት ሊደረግባቸው ያስፈልጋል፡፡

በዓላቱ በሚከበሩበት ወቅት የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች በአብሮነት ተሰባስበው በቋንቋቸው፣ ባህሎቻቸውንና ዕሴቶቻቸውን የሚገልፁበትና የሚጫወቱበት ብሎም ጠንካራ የሆነ የባህል ትስስር በህዝቡ መካከል እንዲፈጠር ያደርጋሉ፡፡ ስለሆነም የቡሄ በሉ፣ የአረፋ፣የሻደይ አበባና የአሸንድዬ በዓለት በየዓመቱ በደማቅ ሁኔታ ይከበራሉ፡፡ ከነዚህ በዓላት ውስጥም በሙስሊሙ ማኅበረሰብ ዘንድ የሚከበረው የአረፋ በዓል አንድነትን፣መረዳዳትን የሚያጠናክር ድንቅ የሆነ በዓል ነው፡፡በዚህ ወቅትም በመረዳዳትና በመደጋገፍ አኩሪ ታሪክ ያለን ህዝቦች መሆናችን በጉልህ የምናሳይባቸው በዓላት ናቸው፡፡ እነዚህ በዓላት በመላ ሀገሪቱ የሚከበሩ ሲሆን በዋናነት ግን በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል በትግራይ ከልልና በአማራ ክልል በራያ፣ በሰቆጣና በላስታ ላሊበላ የሚከበሩት የአሸንዳ ሻደይ እና ሶለል የሚባሉት የሴቶችና የልጃገረዶች በዐል ተጠቃሽ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ይዘት ያላቸው ሆነው ባንድ ጊዜ በተለያዩ ስያሜዎች ይከበራሉ፡፡በተለይ የአሸንዳ በዓልን በተመድ የባህል የትምህርትና የሳይንስ ተቋም ለማስመዝገብ ሲደረግ የነበረው ጥረት አሁንም በሚመለከታቸው አካላት ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል።ይህም ለገፅታ ግንባታና ለብሔራዊ መግባባት ፋይዳው የጎላ ነው።

የእነዚህ በዓላት የአከባበራቸው ሁኔታ እጅግ የአድማጭ ተመልካችን ቀልብ በሚስብ መልኩ ስለሆነ  በውጭ ሀገር የሚኖሩ ዲያስፖራዎችን ጨምሮ በአገር ውስጥ የሚገኙ ዜጎች በዓሉ ወደሚከበርበት ስፍራ በማቅናት በቦታው ተገኝተው ይታደማሉ፡፡ በዚህ ወቅትም ስለ በዓሉ የአከባበር አንድምታ ታሪካዊ ደህራውን በማንሳት የበዓላቱንን ቱርፋቶች ይገነዘባሉ፡፡ አከባበሩም ልዩ ስሜትን ስለሚፈጥርባቸው በአገራቸው ላይ ያለቸው ክብርና ኩራት ከፍ ይላል፡፡ ይህ ደግሞ አገራዊ አንድነትን በመፍጠር ረገድ ቁልፍ መሳሪያ መሆኑን ሁሉም የሚስማማበት ጉዳይ ሆኖ ታይቷል፡፡ ይሁን እንጂ እነዚህ በዓላት በሚከበሩበት ወቅት መሰረት የሌላቸው ከባህላችን ትውፊቶች ያፈነገጡ ተግባራትን ለማራመድ የሚንቀሳቀሱ በከርሰ ህሊና ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ኃይሎችን በሰለጠነና ኢትዮጵያዊ በህል በተላበሰ መልኩ እንዲታረሙ የማድረግ ኃላፊነት የሁሉም ዜጋ የቤት ስራ ነው፡፡ ስለሆነም “በአዲስ አመት አዲስ መንፈስ” በሚል የይቅርታ፣ የአንድነትና የመደመር ጉዞ ላይ ዜጎች የጠራ ግንዛቤና አመለካከት ይዘው ለአገራቸው እድገት እንቅስቃሴ ቋሚ ተሰላፊ መሆን ይኖርባቸዋል፡፡ ኢትዮጵያ ለዜጎቿ የሚበቃ በቂ አቅም እንዳላት ጠቅላይ ሚኒስትሩ መናገራቸው ይታወሳል፡፡ ይህ አገላለፅ ግን በአንዳንድ የለውጥ እምቢተኞች የተሳሳተ ግንዛቤ በአንዳንድ የአገሪቱ ክፍሎች የዜጎችን በህይወት የመኖርና የመንቀሳቀስ መብት በእጅጉ የሚፈታተን ጉዳይ ስለሆነ መንግስት ሰፊ ዝክረ ሀሳቦችን አቅርቧል፡፡ ይህን በጋራ የመጠቀም እድል  በአግባቡ የማይጠቀሙ ኃይሎችን እንዲታረሙ ህገ መንግስታዊ እርምጃ እንደሚወስድ ሊገነዘቡ ይገባል፡፡ ለዚች አገር የሚበጃትና የሚጠቅማት በይቅርባይነት የተላበሰ የመደመርና የአንድነት እሳቤ እንጂ የመከፋፈልና የመለያየት ግንብ አይደለም፡፡ ስለሆነም ዜጎች መደመርና ይቅርባይነትን ከልባቸው ወስደው ከጥላቻና ከመከፋፈል ጠብ የሚል ትርፍ እንደሌለው በውል መገንዘብና የመደመርን አንድምታ በአግባቡ ልንመነዝረው የምንችልበት ዕውቀት ሊኖረን ይገባል፡፡

ለአዲስ ዓመት በውጭ አገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በኢትዮጵያ እየመጣ ያለውን ለውጥ ተከትሎ አገራቸውን ለመጎብኘት በብዛት ወደ አገራቸው ይመጣሉ፡፡ ይህን ተከትሎ መንግስት ከአየር መንገድ የ25% የዋጋ ቅናሽ በማድረግና ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎች በማዘጋጀት እንደሚቀበላቸው አስታውቋል፡፡ በመሆኑም ይህ እሳቤ ለአገራችን ዕድገት የበኩሉን አስተዋጽኦ ስለሚያበረክት በመንግስት በኩል ይሁንታን ያገኘ በመሆኑ ዜጎቻችን ለመቀበል ከፍተኛ እንቅስቃሴ እየተደረገ ይገኛል፡፡ ስለሆነም ወደ አገራቸው በሚመጡበት ወቅት በሁሉም መንገድ አገልግሎት በሚያገኙበት ሁኔታ ላይ የዋጋ እናሽ በማድረጉ ያለምንም ስጋት ወደ እናት አገራቸው የመምጣትና የመጎብኘት ፍላጎታቸው እንዲጨምር አድርጓቸዋል፡፡ ይህ በመሆኑም ሁሉም በሚባል አገራቸውን ለመጎብኘት ጊዜውን በመጠባበቅ ላይ ናቸው፡፡ ይህ ሁኔታም መጭው የአዲሰ ዓመት አከባበር ከምንጊዜውም በተለየ መልኩ በደማቅ ሁኔታ ሀገራዊ የአንድነት መንፈስ በማስፈን የሚከበር መሆኑ ልዩ ያደርገዋል፡፡

This website uses cookies to improve your experience. We'll assume you're ok with this, but you can opt-out if you wish. Accept Read More

Privacy & Cookies Policy